ፖምፔዎ ቫይረሱ ከቻይና ቤተ ሙከራ ስለመምጣቱ 'በርካታ ማስረጃዎች' አሉን አሉ

የኮሮናቫይረስን ለመከላከል ክትባትም ሆነ ለማከም የሚውል መድኃኒት እስካሁን አልተገኘም። ነገር ግን በየአገራቱ ያሉ ባለሙያዎች ሌት ተቀን ጥረት እያደረጉ መሆናቸው እየተነገረ ነው። መቼ ውጤት ላይ ሊደርሱ እንደሚችሉ ግን በእርግጠኝነት መናገር አይቻልም። ስለዚህ በእጃችን ላይ ያሉትን የመከላከያ መንገዶች በመጠቀም እራስን ከበሽታው መጠበቅ ብቸኛው መንገድ ነው። ለዚህ ደግሞ አካላዊ ርቀታችንን እንጠብቅ፤ እጃችንን በተደጋጋሚ በሳሙናና በውሃ እንታጠብ። ስለወረርሽኙ የሚቀርቡ የቀጥታ ዘገባዎችንና መረጃዎችን ከዚህ ገጽ ይከታተሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ፖምፔዎ ቫይረሱ ከቻይና ቤተ-ሙከራ ስለመምጣቱ 'በርካታ ማስረጃዎች' አሉን አሉ

    Mike pompeo

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ የውጪ ጉዳይ ሚንስትር ማይክ ፖምፔዮ በቴሌቭዥን ቃለ መጠይቅ ላይ ኮሮናቫይረስ ዉሃን ከተማ ከሚገኝ ቤተ-ሙከራ ስለመምጣቱ 'በርካታ ማስረጃዎች' አሉን ብለዋል።

    የቀድሞ የሲአይኤ አለቃ ለዚህ ክሳቸው ምንም አይነት ማረጋገጫ አላቀረቡም።

    የዓለም ጤና ድርጅት በበኩሉ ቫይረሱ መነሻው 'ከእንስሳት' እንጂ በቤተ-ሙከራ የተፈበረከ አይደለም ይላል።

    ከአሜሪካው የውጪ ጉዳይ ሚንስትር በተጨማሪ ፕሬዝድንት ዶናልድ ትራምፕም በተመሳሳይ ቫይረሱ መነሻው ከቻይና ቤተ-ሙከራ መሆኑን በተደጋጋሚ ተናግረዋል።

  2. እንደምን አደራችሁ ውድ የቢቢሲ አማርኛ ተከታታዮች

    ላሊበላ ከተማ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ላሊበላ ከተማ

    እንደምን አደራችሁ ውድ የቢቢሲ አማርኛ ተከታታዮች

    ከአሁን ሰዓት ጀምሮ በቀጥታ ዘገባችን ከቫይረሱ ስርጭት ጋር የተያያዙ መረጃዎችን እናቀርብላችኋለን።

    አብራችሁን ቆዩ።

  3. በአፍጋኒስታን የቫይረሱ ሥርጭት መጨመሩ በህጻናት ላይ የረሃብ አደጋ ደቅኗል

    ዳቦ የያዘች ህጻን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ከአፍጋኒስታን የማህበረሰብ ጤና ሚኒስቴር የወጡ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ባለፉት 24 ሰዓታት 179 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል፡፡ ይህም አጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 2ሺህ 469 አድርሶታል፡፡ እስካሁን 72 ሰዎች በቫይረሱ ሕይወታቸውን አጥተዋል፡፡

    ምንም እንኳን ከሌሎች አገራት ጋር ሲነጻጸር ቁጥሩ አነስተኛ ቢሆንም አፍጋኒስታን የመመርመር አቅሟ ውስን በመሆኑ እንደሆነ ተገልጿል፡፡

    የጤና ሥርዓቷም ቢሆን ለአስርት ዓመታት በነበረው ግጭት ምክንያት ከፍተኛ ተግዳሮት ገጥሞታል፡፡

    በመሆኑም በወረርሽኙ ሳቢያ የምግብ ዋጋ ንረት በመከሰቱ ከ7 ሚሊዮን የሚበልጡ ህጻናት የረሃብ አደጋ እንደተደቀነባቸው ግብረ ሰናይ ድርጅቶች አሳስበዋል፡፡

  4. በሩሲያ በአንድ ቀን 10ሺህ ሰዎች ኮሮናቫይረስ ተገኘባቸው

    በሩሲያ ጭምብል ያጠለቁ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በተለያዩ ሃገራት በኮሮናቫይረስ የሚያዙ ሰዎች እንዲሁም የሟቾች ቁጥር ቢቀንስም በአንዳንድ ሃገራት ግን ጭማሬን እያሳየ ነው።

    በሩሲያ ወረርሽኙ ከተነሳበት ጀምሮ ከፍተኛውን ቁጥር የመዘገበች ሲሆን በአንድ ቀን ብቻ አስር ሺህ ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ተረጋግጧል።

    የሩስያ ባለስልጣናት ከፍተኛ ቁጥር የተመዘገበው አገሪቷ የመርመር አቅሟን በመጨመር በሞስኮ ከተማ ብቻ አርባ ሺህ ሰዎችን በመመርመሯ መሆኑን አሳውቀዋል።

    ቫይረሱ ከተገኘባቸው ሰዎች መካከል ግማሾቹ ምንም ምልክት ያልታየባቸው እንደሆኑም አመላክተዋል።

    የኮሮናቫይረስ ህክምና መስጫ እንዲሆኑ ጊዜያዊ ማዕከላትን የከፈተችው ሩሲያ የሟቾች ቁጥር ኬሎች አገራት ጋር ሲነፃፀር ዝቅተኛ የሚባል ነው። እስካሁንም ባለው 1ሺህ 280 ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል።

    የሩሲያው ጠቅላይ ሚኒስትር ሚክሃይል ሚሹስቲን በኮሮናቫይረስ ታመው ሆስፒታል በህክምና ላይ የሚገኙ ሲሆን፤ ከሆስፒታልም ሆነው ስራቸውን እየሰሩ ነው ተብሏል።

    ከጆንስ ሆፕኪንስ በተገኘው መረጃ መሰረት እስካሁን በሩሲያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 134 ሺህ 687 ደርሷል።

  5. ቦሪስ ጆንሰን በኮሮናቫይረስ ታመው በነበረበት ወቅት ስለተደረገላቸው ህክምና ተናገሩ

    ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን በኮሮናቫይረስ በጠና ታመው በነበሩበት ወቅት በሆስፒታል ስለተደረገላቸውን ህክምና ተናገሩ፡፡

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዘ ሰን ጋዜጣ ጋር እሁድ ዕለት ባደረጉት ቃለምልልስ ሕይወታቸውን ለማትረፍ "በርካታ ሊትር ኦክስጅን እወስድ ነበር" ብለዋል፡፡

    ቦሪስ በለንደን ቅዱስ ቶማስ ሆስፒታል ያሳለፉት አንድ ሳምንት ጊዜ ሌሎች በዚህ ወረርሽኝ እንዳይሰቃዩ ወረርሽኙን መግታት እና አገራቸው ቀድማ ወደነበረችበት ሁኔታ እንድትመለስ የማድረግ ፍላጎት አሳድሮባቸዋል፡፡

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከጋዜጣው ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ "በጣም አስቸጋሪ ጊዜ ነበር፤ ልክድ አልፈልግም!" ሲሉ እንዴት ከሆስፒታል እንደሚወጡ ራሳቸውን ሲጠይቁ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡

    ቦሪስ ቫይረሱ እንደተገኘባቸው የተረጋገጠው በጎርጎሮሳዊያኑ መጋቢት 26 ሲሆን ከአስር ቀናት በኋላ ሆስፒታል እንዲገቡ ተደርገዋል፡፡ ከዚያም ወደ ጽኑ ሕሙማን ክፍል ያመሩት በሁለተኛው ቀን ነበር፡፡

    "በጥቂት ቀናት ውስጥ ጤንነቴ በዚህ ደረጃ መቃወሱን ለማመን አስቸጋሪ ነበር" ብለዋል ቦሪስ በቃለ ምልልሳቸው፡፡

    ዶክተሮቹም የከፋ ነገር ከመጣ ማድረግ ስላለባቸው ነገር ከፍተኛ ዝግጁነት ነበራቸው ብለዋል፡፡

    ቦሪስ በርካቶች በበሽታው እየተሰቃዩ እንደነበር ገልጸው፤ "በመዳኔ እድለኛ እንደሆንኩ ነበር የተሰማኝ" ይላሉ፡ ይህም የሌሎችን ስቃይ ለማቆም ከፍተኛ ፍላጎት እንዳሳደረባቸው ገልጸዋል፡፡

    "አገራችንን ቀድሞ ወደነበረችበት ሁኔታ፣ ጤና ለመመለስ ፍላጎት አሳድሮብኛል፤ በእርግጥም እዚያ እንደምንደርስ እርግጠኛ ነኝ" ብለዋል ቦሪስ፡፡

    ቦሪስ ጆንሰን ከበሽታው ድነው ወደ ሥራ የተመለሱት ባለፈው ዕሁድ ሲሆን ባሳለፍነው ሳምንትም የወንድ ልጅ አባት ሆነዋል፡፡

    እጮኛቸው ካሬ ሲመንድስ አዲስ የተወለደው ልጃቸው ዊልፍሬድ ላውሬ ኒኮላስ ጆንሰን እንደተባለ አስታውቀው ነበር፡፡

    የልጃቸው ስምም ለአያቶቻቸው እና ቦሪስን ላከሟቸው ለሁለት ዶክተሮች ማስታወሻነት እንዲሆን የተሰየመ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

    ሲሞንድ በኢንስታግራም ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ ልጃቸው የተወለደው ቦሪስ የኮሮና ሕክምናቸውን አጠናቀው ከሆስፒታል ከወጡ ከሳምንታት በኋላ ነበር፡፡

    በዩናይትድ ኪንግደም እስካሁን 183ሺህ 500 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን 28ሺህ 131 ሰዎች ሕይወታቸው ማለፉን የጆንስ ሆፕኪንስ መረጃ ያሳያል፡፡

  6. በኢራን መስጊዶች ሊከፈቱ ነው

    በኢራን የሚገኝ መስጊድ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኮሮናቫይረስን መዛመት ለመግታት ከወር በላይ ተዘግተው የነበሩ የኢራን መስጊዶች ሊከፈቱ ነው።

    በእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ ቅዱስ ተብሎ በሚጠራው የረመዳን ፆም ወቅት የሚደረጉ አገልግሎቶችንም ህዝቡ ራቅ ብሎ መከታተል ይችላል ተብሏል።

    በዚህ ወቅት ሁሉም ሳይሆኑ የተወሰኑ መስጊዶች እንደሚከፈቱ የተናገሩት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሃሰን ሩሃኒ በተለይም በወረርሽኙ ከፍተኛ ስጋት የሌላቸው ተብለው በተለዩ ከተሞች ከነገ ጀምሮ የሚከፈቱ ይሆናል።

    "የአርብ ፀሎትም የሚከናወን ሲሆን ይህ ሁሉ ግን የተሰጠውን መመሪያዎችን በመከተልም የሚካሄድ ይሆናል" ብለዋል ፕሬዚዳንቱ።

    ከዚህም በተጨማሪ ከሁለት ሳምንታት በኋላም ትምህርት ቤቶችንም ለመክፈት እቅድ እንደተያዘ ፕሬዚዳንቱ አስረድተዋል።

    በኮሮና ክፉኛ በተጠቃችው ኢራን 96 ሺህ 448 ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን 6ሺህ 156 ሰዎችም ህይወታቸውን አጥተዋል።

  7. በአፍሪካ ያለው የኮሮናቫይረስ ምርመራ ምን ይመስላል?

  8. በኢትዮጵያ የጉዞ ታሪክ የሌላቸው ሁለት ግለሰቦች ኮሮናቫይረስ ተገኘባቸው

    ጭምብል ያጠለቀች ሴትዮ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኢትዮጵያ ባለፉት ሃያ አራት ሰዓታት ውስጥ ባደረገችው 1560 የላብራቶሪ ምርመራ የጉዞ ታሪክ የሌላቸው ሁለት ግለሰቦች ኮሮናቫይረስ ተገኝቶባቸዋል።

    አንደኛው ግለሰብ የባቱ/ ዝዋይ ነዋሪ ሲሆን እድሜው 49 መሆኑን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴርና የማህበረሰብ ጤና ተቋም በዛሬው ዕለት ባወጡት መግለጫ ተጠቅሷል። ግለሰቡ የጉዞ ታሪክ እንዲሁም በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር ግንኙነት የሌለው ሲሆን በጤና ተቋም ተኝተው ከሚታከሙ ህሙማን ከተወሰደ ናሙና የተገኘ መሆኑንም መግለጫው አመላክቷል።

    ሌላኛዋ ግለሰብ እንዲሁ የውጭ ሃገር የጉዞ ታሪክ የሌላት ሲሆን የስልጤ ወረዳ ነዋሪና የ45 ዓመት ጎልማሳ ናት። መግለጫው እንደጠቀሰው ግለሰቧ በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር ግንኙነት የሌላትና በቤት ለቤት ቅኝትና አሰሳ የተለየችም ናት ብሏል።

    በኢትዮጵያ እስካሁን 22 ሺህ 330 የላብራቶሪ ምርመራዎች የተከናወኑ ሲሆን፤ ከእነዚህም 135ቱ በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል። በዛሬው ዕለት ተጨማሪ ስድስት ሰዎች ማገገማቸውን ተከትሎ ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 75 ደርሷል።

    አሁን ላይ 55 ሰዎች በህክምና ላይ የሚገኙ ሲሆን፤ ከዚህ ቀደም የሦስት ሰዎች ሕይወት ማለፉንና ሁለቱ ደግሞ ወደ አገራቸው መመለሳቸውን መግለጫው አስታውሷል።

    መግለጫ

    የፎቶው ባለመብት, Ethiopian Ministry of Health

  9. በቬንዙዌላ እስር ቤት በተፈጠረ ግጭት ከ40 በላይ ሰዎች ሞቱ

    አምቡላንስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በቬንዙዌላ እስር ቤት በተፈጠረ ግጭት ከ40 በላይ ሰዎች መሞታቸው ተገለጸ፡፡

    የእስር ቤቶችን ሁኔታ የሚከታተለው ድርጅት 'ቬንዙዌላ ፕሪዝን ኦብዘርቫቶሪ' እንዳስታወቀው በምዕራባዊቷ ጉዋናሬ ከተማ በሎስ ልላኖስ እስር ቤት የሚገኙ ታራሚዎች ቀደም ብሎ በምግብ እና ውሃ እጥረት ምክንያት ተቆጥተው ነበር፡፡

    በመሆኑም ባለሥልጣናት ግጭቱ የተፈጠረው እስረኞቹ ሊያመልጡ ሲሉ ነው ማለታቸውን ጥርጣሬ የፈጠረበት ድርጅቱ ምርመራ እንዲካሄድ ጥሪ አቅርቧል፡፡

    እንደ ድርጅቱ ከሆነ 46 እስረኞች የሞቱ ሲሆን በአካባቢው የሚገኝ ሆስፒታል ጉዳት በደረሰባቸው ሰዎች ተጨናንቋል፡፡

    በግጭቱ አስተዳዳሪውን ጨምሮ የእስር ቤቱ ሠራተኞች ላይ ጉዳት ደርሷል፡፡

    የማረሚያ ቤቶች ሚኒስትር የሆኑት ኢሪስ ቫሬላ ለቬንዙዌላ ጋዜጣ በእስር ቤቱ ውስጥ ግጭት እንደነበረ ገልጸው የሞቱትን ሰዎች ቁጥር ግን አልተናገሩም፡፡

    በሪፖርቱ ላይ ግጭቱ ለማምለጥ በተደረገ ሙከራ የተፈጠረ እንደሆነ ተገልጿል፡፡

    በላቲን አሜሪካ በሚገኙ እስር ቤቶች መንግሥት የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመግታት የተለያዩ እርምጃዎችን እየወሰደ ቢሆንም ንፅህናቸው ባልተጠበቀና በተጨናነቁት እስር ቤቶች የሚፈጠሩ ግጭቶች እየተበራከቱ ነው፡፡

    ቬንዙዌላ ከኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በተጨማሪ ሁለት አማጺ ፖለቲከኞች በሚያደርጉት የሥልጣን ሽኩቻ ቀውስ አጋጥሟታል፡፡

    በፕሬዚደንት ኒኮላስ ማዱሮ ዘመን የአገሪቷ ኢኮኖሚ ሙሉ በሙሉ በመውደቁ የመሰረታዊ ሸቀጦች እጥረት ተባብሷል፡፡ በዚህም ምክንያት በሚሊየን የሚቆጠሩ ሰዎች ወደ ጎረቤት አገራት ተሰደዋል፡፡

  10. "ካህናት የሚያቆርቡት የፊት ጭምብል አድርገው ነው" የጀርመን ቤተ-ክርስቲያናት

    አንድ የሚያቆርቡ ካህን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኮሮናቫይረስን መዛመት ለመግታት ተዘግተው የነበሩት የጀርመን ቤተ- ክርስቲያናት ለአማኞቻቸው በሮቻቸውን ቢከፍቱም አገልግሎቱ እንደ ቀድሞው አይሆንም ተብሏል።

    ቤተክርስቲያናቱ ከጀርመን ባለስልጣናት ለሳምንታት ባደረጉት ውይይቶች አሁንም ቢሆን ቫይረሱ ሊዛመት ስለሚችል አስገዳጅ የሆኑ መመሪያዎችን ለማስተላለፍ ከውሳኔ ላይ ተደርሷል።

    በዚህም መሰረት ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚመጡ የምዕመናኑን ቁጥር ከመገደብ በተጨማሪ አካላዊ ርቀታቸው በሁለት ሜትር መለያየቱን ማረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል።

    ባለስልጣናቱ እንደሚሉት በዝማሬ ወቅት (በሚደረጉ የትንፋሽ ልውውጦች) ቫይረሱን ሊተላለፍ ስለሚችል የተከለከለ ሲሆን የሚያቆርቡ ካህናትም የፊት ጭምብል ማድረግ ይጠበቅባቸዋል።

    የይሁዲና የሙስሊም እምነት መሪዎችም በምኩራቦቻቸውና በመስጊዶቻቸው አዳዲስ መመሪያዎችን በማስተዋወቅ ላይ ናቸው።

    የተለያዩ የእምነት መሪዎች ጀርመን የኮሮናቫይረስን ወረርሽኝ ለመከላከል እንቅስቃሴ መገደቧን እንዲሁም አስገዳጅ የቤት ውስጥ መቀመጥና ሌሎችም መመሪያዎችን የደገፉ ቢሆንም የተለያዩ የንግድ ቦታዎች የሚከፈቱ ከሆነ ለምን የአምልኮ ቦታዎች አይከፈቱም እያሉ ሲጠይቁ ነበር።

    ሆኖም የአምልኮ ቦታዎች በመከፈታቸው ደስተኛ ናቸው በተለይም አለም በስጋት ባለበት ወቅት ሰዎች የአምላካቸውን ድጋፍ እንዲሁም እምነታቸውን የሚሽቱበት ወቅት እንደሆነም አንድ የይሁዲ እምነት መሪ ተናግረዋል።

  11. የዋረን ቡፌት ኩባንያ በአሜሪካ አየር መንገዶች ያለውን ድርሻ ሸጠ

    ደልታ አየር መንገድ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ የጉዞ ኢንድስትሪ በኮሮናቫይረስ ምክንያት ውድቀት አጋጥሞታል

    ቢሊየነሩ ዋረን ቡፌት ኩባንያቸው፣ በርክሻየር ሃዛወይ በአሜሪካ አራት ግዙፍ አየር መንገዶች ያለውን ድርሻ በሙሉ መሸጡን አስታወቁ፡፡

    ባለሃብቱ በባለድርሻዎች አመታዊ ስብሰባ ላይ ዓለም በኮሮናቫይረስ ምክንያት እንደተለወጠች ገልጸው፤ በአየር መንገድ ዘርፍ ላይ መዋዕለ ንዋያቸውን ማፍሰሳቸው ስህተት እንደነበ ተናግረዋል፡፡

    የባለሃብቱ ዋረን አስተያየት የተሰማው ድርጅታቸው በርክሻየር ሃዛወይ በመጀመሪያው ሩብ ዓመት 50 ሚሊየን ዶላር ኪሳራ እንዳጋጠመው ካስታወቀ በኋላ መሆኑን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል፡፡

    በተለያዩ የቢዝነስ ዘርፎች ላይ የተሰማራው ኩባንያቸው፤ በዓመታዊ ሪፖርቱ እንዳስታወቀው በደልታ አየር መንገድ 11 በመቶ፣ በአሜሪካ አየር መንገድ 10 በመቶ፣ በሳውዝዌስት አየር መንገድ 10 በመቶ እና በዩናይትድ አየር መንገድ 9 በመቶ ድርሻ ነበረው፡፡

    ድርጅቱ የአቪየሽን ኢንዱስትሪውን እርግፍ አድርጎ ለዓመታት ከተው በኋላ በአራት አየር መንገዶች ላይ መዋዕለ ንዋዩን ማፍሰስ የጀመረው በጎርጎሮሳዊያኑ 2016 ነው፡፡

  12. ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ስለ ኮቪድ-19 ለመወያየት ወደ ኢትዮጵያ አመሩ

    ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ከባለሥልጣናት ጋር

    የፎቶው ባለመብት, Yemane Gebremeskel Twitter Page

    ከሰሞኑ ከሕዝብ እይታ ጠፍተው የነበሩት የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ ጋር የሁለት ቀናት ጉባኤ ለማካሄድ ወደ ኢትዮጵያ ማምራታቸውን የማስታወቂያ ሚኒስትሩ የማነ ገብረ መስቀል በትዊተር ገፃቸው ላይ አስፍረዋል።

    ሁለቱ መሪዎች የአለም ስጋት የሆነውን ኮቪድ-19፣ የአንበጣ ወረራና ቀጠናዊ ጉዳዮች ላይ አተኩረው ይወያያሉ ተብሏል።

    ከፕሬዚዳንቱም ጋር የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ኦስማን ሳልህ፣ የፕሬዚዳንቱ አማካሪ የማነ ገብረ አብ አብረዋቸው እንዳሉ ከትዊተር ገፃቸው መረዳት ተችሏል።

  13. ስፔን በሕዝብ ትራንስፖርት ማስክ ማድረግን ግዴታ አደረገች

    የፊት ጭምብል ያጠለቁ ሴትዮ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በስፔን ከነገ ጀምሮ በሕዝብ ትራንስፖርት ውስጥ የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ (ማስክ) ማድረግ ግድ መሆኑን አስታወቀች፡፡

    አገሪቷ በኮሮናቫይረስ ሳቢያ የጣለቻቸውን ጥብቅ ገደቦች ቀስ በቀስ እያላላች ነው፡፡

    ጠቅላይ ሚኒስትር ፔድሮ ሳንቼዝ መንግሥት 6 ሚሊዮን የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ (ማስክ) እንደሚያሰራጭ አስታውቀዋል፡፡ ይህ በዋናነት በትራንስፖርት ቦታዎች የሚከፋፈል ሲሆን ሌላ ተጨማሪ 7 ሚሊየን ማስክ ለባለሥልጣናት እንደሚሰጥ ተናግረዋል፡፡

    በስፔን የሚገኙ አዋቂዎች ከሰባት ሳምንታት በኋላ እሁድ ዕለት ለመጀመሪያ ጊዜ ከቤት በመውጣት አካላዊ እንቅስቃሴ አድርገዋል፡፡

    ከ14 ዓመት በታች ላሉ ህጻናት በቤት ውስጥ የመቀመጥ ገደቡ የላላው ከሳምንት በፊት ነበር፡፡

    በሌሎች የአውሮፓ አገራትም በቤት ውስጥ የመቀመጥ ገደቡ ቀስ በቀስ እየለዘበ መጥቷል፡፡ ነገር ግን አካላዊ ርቀትን መጠበቅ ግድ ነው፡፡ አንዳንድ አገራትም የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ (ማስክ) በሱቆችና በሕዝብ ትራንስፖርት ላይ ማድረግን ይጠይቃሉ፡፡

    ስፔን በቫይረሱ ክፉኛ ከተጠቁ የአውሮፓ አገራት በሦስተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡

    ከአውሮፓ፤ ጣሊያን በቫይረሱ ሳቢያ ከፍተኛ የሞት ቁጥር የተመዘገበባት ሲሆን ዩናይትድ ኪንግደምም በተቀራራቢ መልኩ ተከትላታለች፡፡

    በዩናይትድ ኪንግደም ያለው መረጃ እንደሚያሳየው በየቀኑ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በቫይረሱ የሚያዙ ሲሆን ቅዳሜ ዕለት ተጨማሪ 621 ሰዎች መሞታቸው ተነግሯል፡፡

    ፈረንሳይና ጣሊያን ግን ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ የመዘገቡት በቫይረሱ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከ200 ያነሰ ነው፡፡

    ነገር ግን ጣሊያን ቅዳሜ ዕለት 474 ሞት የመዘገበች ሲሆን በቅርብ ቀናት ውስጥ የተመዘገበ ከፍተኛው ቁጥር ነው ተብሏል፡፡

    ላ ሪፐብሊካ የተሰኘው ጋዜጣ በጣሊያን በሳለፍነው የፈረንጆቹ ሚያዚያ ወር ከሆስፒታል ውጭ 282 ሰዎች የሞቱ ሲሆን ቁጥሩ ግን ከዚህ በፊት ከነበረው ቁጥር ጋር አልተካተተም ብሏል፡፡

  14. በኮሮናቫይረስ እንዳንያዝ የተፈጥሮ በሽታን የመከላከያ ሥርዓታችን መገንባት

  15. እንደምን አደራችሁ?

    ጭምብል የለበሰ ግለሰብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ለሰው ልጅ ስጋት በሆነው የኮሮናቫይረስ ከ3.4 ሚሊዮን በላይ የሆነው የአለማችን ህዝብ ተይዟል።

    ከዚሀም ውስጥ 244 ሺህ የሚሆኑት ህይወታቸውን አጥተዋል፤ 1.1 ሚሊዮን ህዝብ ደግሞ አገግሟል።

    በኢትዮጵያ ውስጥም በቫይረሱ የተያዙት ሰዎች ቁጥር 133 የደረሰ ሲሆን፣ ሶስት ሰዎች ሲሞቱ፣ 66ቱ ደግሞ አገግመዋል።

    የኮሮናቫይረስ የአለምን ህዝብ አኗኗር ወግ፣ ባህል፣ ልምድ፣ ዘዬ ቀያይሮታል። ከዚህም በተጨማሪ የወደፊቱ ምን ሊሆን ይችላል የሚለውንም ጥያቄ ውስጥ ከትቶታል ።

    በአሁኑ ሰአት ቀዳሚው ነገር ነገን ለማየት በህይወት መቆየት እንደመሆኑ መጠን በተቻለ መጠን መደረግ የሚገባቸውን ጥንቃቄዎች በማድረግ ራሳችንን ከቫይረሱ እንድንከላከልም ይመከራል።

    እጃችንን በተደጋጋሚ መታጠብ፣ አካላዊ ርቀትን መጠበቅ እንዲሁም የፊት ጭምብሎችን ማድረግ ከሚመከሩት መከላከያ ዘዴዎች መካከል ናቸው።

    ቫይረሱ ከተነሳባት እለት ጀምሮ ከቢቢሲ አማርኛ እንደምናደርገው አገራት እየወሰዷቸው ስላሉ እርምጃዎች፣ ስላገገሙ ሰዎች ታሪክ፣ በቫይረሱ እየተደረጉ ስላሉ የክትባት ሙከራዎችና አዳዲስ መረጃዎችንን በቀጥታ ዘገባችን ማግኘት ይችላሉ። መልካም እሁድ እንዲሁም የእረፍት ቀን እንዲሆንላችሁ ተመኘን

  16. "የሚሞቱ ህሙማን የመጨረሻ ጊዜያቸውን የሚያሳልፉት ከእኔ ጋር ነው"

  17. ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን የልጃቸውን ስም ላከሟቸው ዶክተሮች ማስታወሻ አደረጉ

    ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰንና ባለቤታቸው ካሪ ሲመንድስ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የብሪታኒያው ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰንና ባለቤታቸው ካሪ ሲመንድስ በቅርቡ የተወለደውን ልጃቸውን ዊልፍሬድ ላውሪ ኒኮላስ ጆንሰን በማለት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በኮሮናቫይረስ በታመሙበት ጊዜ ላከሟቸው ሐኪሞች ማስታወሻ አድርገውታል።

    የጠቅላይ ሚኒስትሩ ባለቤት በኢንስታግራም ገጻቸው ላይ እንዳሉት የልጃቸው ስም አያቶቻቸውንና አባቱ ቦሪስ ጆንሰን በኮሮናቫይረስ ተይዘው ሆስፒታል በገቡበት ጊዜ ህክምና በማድረግ ለረዷቸው ዶክተሮች መታሰቢያ እንዲሆን አስበው እንዳወጡት ገልጸዋል።

    በህጻኑ ስም ውስጥ ያለው "ኒኮላስ" የሚለው መካከለኛ ስም ጠቅላይ ሚኒስትሩን በቅርበት ሲከታተሉና ሲያክሙ የነበሩትን ዶክትር ኒክ ፕራይስ እና ኒክ ሃርትን የሚያመለክት እንደሆነ ተገልጿል።

    ህጻኑ የተወለደው ባለፈው ረቡዕ ሲሆን፤ ይህም አባቱ ጠቅላይ ቦሪስ ጆንሰን ከጽኑ ህሙማን ክፍል አገግመው ከወጡ ከጥቂት ሳምንታት በኋላ ነበር።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን ለቀናት በቤታቸው ሆነው እረፍት ካደረጉ በኋላ ባለፈው ሰኞ ነበር ወደ ቢሯቸው በመመለስ መደበኛ ሥራቸውን የጀመሩት። ልጃቸውም የተወለደው ሥራ በጀመሩ በሦስተኛው ቀን ነው።

  18. ማሌዢያ ‘የወረርሽኙን መስፋፋት ለማስቆም’ በሚል ስደተኞችን ማሰር ጀመረች

    የተያዘ ስደተኛ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የማሌዢያ ባለስልጣናት የኮሮናቫይረስ መስፋፋትን ለመግታት በሚል ፈቃድ የሌላቸውን ስደተኞች እያፈሱ መሆናቸውን አንድ የፖሊስ ኃላፊ አስታወቁ።

    "የሚኖሩበትን ቦታ ለይቶ ለማወቅ አስቸጋሪ በመሆኑ፤ እንደ ልባቸው እንዲንቀሳቀሱ መፍቀድ አንችልም” ሲሉ የፖሊስ ኃላፊው አብዱል ሐሚድ ባዶር ተናግረዋል።

    በዋና ከተማዋ ኳላ ላምፑር ማዕከላዊ ክፍል ውስጥ በሚገኙ አካባቢዎች አርብ ዕለት በተደረገው አሰሳ ታዳጊዎችንና ከሚያናማር የመጡ የሮኒሂጊያ ስደተኞችን ጨምሮ ከ700 በላይ ስደተኞች ተይዘዋል ሲሉ የመብት ቡድኖች አስታውቀዋል።

    ይህን እርምጃ መወሰድ የተጀመረው በዜጎች ዘንድ ስደተኞችን በተለይ ደግሞ የሮሂንጊያ ስደተኞች መብዛትና ለቫይረሱ መስፋፋት ምክንያት ናቸው በሚል የተቀሰቀሰን ቁጣን ተከትሎ ነው።

    ማሌዢያ በዛሬ [ቅዳሜ] እንዳስታወቀችው 105 አዲስ የኮሮናቫይረስ ህሙማንን ያገኘች ሲሆን፤ በአገሪቱ ያለው አጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 6,176 ደርሷል።

    እስካሁንም በወረርሽኙ 103 ሰዎች መሞታቸው ተመዝግበወል።

  19. በርካቶች ኮሮናቫይረስን ለማከም በሚደረገው ሙከራ ለመሳተፍ ፈቃደኛ ሆኑ

  20. የትራምፕ ጽህፈት ቤት በፕሬዝዳንቱ የኮቪድ-19 አያያዝ ላይ ምስክርነት እንዳይሰጥ አገደ

    ዶ/ር አንተኒ ፋውቺ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዋይት ሐውስ፤ የአሜሪካ መንግሥት ጤና አማካሪ የሆኑት ዶክተር አንቶኒ ፋውቺ ምክር ቤት ቀርበው እንዳይመሰክሩ አገደ።

    ዶክተር ፋውቺ፤ ትራምፕ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን የመከቱበት መንገድ ትክክል ነው ወይስ አይደለም በሚለው ላይ ነበር እንዲመሰክሩ የታሰበው።

    በዲሞክራቶች የበላይነት የተያዘው የሕዝብ እንደራሴዎች ምከር ቤት ዶ/ር ፋውቺ ቀጣዩ ረቡዕ ቀርበው በትራምፕ ኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ አያያዝ ጉዳይ ምስክርነት ይስጡ እያሉ ነው።

    ዴሞክራቶች ፕሬዝደንት ትራምፕ ወረርሽኙን የመከቱበት መንገድ ትክክል አይደለም ይላሉ።

    ወረርሽኙ በአሜሪካ እስካሁን 65 ሺህ ሰዎችን ገድሏል።

    የዋይት ሐውስ ቃል አቀባይ በኮሮናቫይረስ ላይ የሚሳተፉ ሰዎች ምስክርነት መስጠታቸው አግባብ አይደለም ይላሉ።

    ቢሆንም ሪፐብሊካኖች በሚበዙበት የሴኔት ስብሰባ ላይ ግን ዶክተሩ ይገኛሉ ተብሏል።

    ዶ/ር ፋውቺ በኮሮናቫይረስ ዙሪያ በሚሰጡ ዕለታዊ ጋዜጣዊ መግለጫዎች ላይ ጎልተው የሚታዩ ሰው ናቸው። ከሰሞኑ ግን ከጥቂት ቀናት ውጪ ብዙ እየታዩ አይደለም።