ፖምፔዎ ቫይረሱ ከቻይና ቤተ ሙከራ ስለመምጣቱ 'በርካታ ማስረጃዎች' አሉን አሉ

የኮሮናቫይረስን ለመከላከል ክትባትም ሆነ ለማከም የሚውል መድኃኒት እስካሁን አልተገኘም። ነገር ግን በየአገራቱ ያሉ ባለሙያዎች ሌት ተቀን ጥረት እያደረጉ መሆናቸው እየተነገረ ነው። መቼ ውጤት ላይ ሊደርሱ እንደሚችሉ ግን በእርግጠኝነት መናገር አይቻልም። ስለዚህ በእጃችን ላይ ያሉትን የመከላከያ መንገዶች በመጠቀም እራስን ከበሽታው መጠበቅ ብቸኛው መንገድ ነው። ለዚህ ደግሞ አካላዊ ርቀታችንን እንጠብቅ፤ እጃችንን በተደጋጋሚ በሳሙናና በውሃ እንታጠብ። ስለወረርሽኙ የሚቀርቡ የቀጥታ ዘገባዎችንና መረጃዎችን ከዚህ ገጽ ይከታተሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በሩሲያ ለሁለተኛ ቀን ከ10ሺህ በላይ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋገጠ

    ማስክ ያደረጉ ግለሰብ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በሩሲያ ተጨማሪ 10ሺህ 581 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው መረጋገጡን የአገሪቷ ባለሥልጣናት አስታወቁ፡፡ ይህም አጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 145ሺህ 268 አድርሶታል፡፡

    አገሪቷ ከ10ሺህ ሰዎች በላይ በቫይረሱ መያዛቸውን ስታረጋግጥ ይህ ሁለተኛ ቀኗ ነው፡፡ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥርም ከቻይና፣ ቱርክ እና ኢራን በልጧል፡፡

    ባለፈው ሳምንት ጠቅላይ ሚኒስትር ሚካሃይል ሚሽስቲን በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ተረጋግጧል፡፡

    ይህንንም ተከትሎ ፕሬዚደንት ፑቲን በአገር አቀፍ ደረጃ ሥራ ዝግ ሆኖ የሚቆይበትን ጊዜ እስከ ፈረንጆቹ ግንቦት 11 ድረስ አራዝመዋል፡፡ በዋና መዲናዋ ሞስኮም የእንቅስቃሴ ገደቡ ባለበት ይቆያል ብለዋል፡፡

    ባለሥልጣናት ሕዝቡ በየቤቱ እንዲቀመጥ እያሳሰቡ ነው፡፡ በሩሲያ በተያዘው ወር የሚከበሩ ሕዝባዊ በዓላትን ለማክበርም የተጣሉትን የእንቅስቃሴ ገደቦች ለመጣስ መሞከርም እንደማይቻል ባለሥልጣናቱ አስጠንቅቀዋል፡፡

  2. ፖሊስ በመምሰል በፈረንሳይ ሲያጭበረብሩ የነበሩ ኢራናውያን ተያዙ

  3. ኮሮናቫይረስ፡ "ሁኔታዎች በዚህ ከቀጠሉ በርሃብ ልናልቅ ነው"

  4. ባለፉት 24 ሰዓታት ተጨማሪ 5 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተነገረ

    GETTY

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓታት ተጨማሪ 5 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተነገረ።

    የጤና ሚንስቴር እና የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በሚያወጡት ዕለታዊ መግለጫ ላይ እንዳስታወቁት ባለፉት 24 ሰዓታት ለ1758 ሰዎች ምርመራ ተደርጎ 5 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል።

    ይህም በአገሪቱ በቫይረሱ ተይዘው የተገኙ ሰዎችን ቁጥር 140 አደርሶታል።

    ከአምስቱ ሰዎች መካከል 3ቱ ከፑንትላንድ የተመለሱ እና በጅግጅጋ ለይቶ ማቆያ የነበሩ ናቸው ተብሏል።

    አንዱ ደግሞ የባህር ዳር ነዋሪ እና በበሽታው መያዙ ከተረጋገጠ ሰው ጋር ግንኙነት የነበረው ነው ተብሏል። የመጨረሻው ግለሰብ ደግሞ ትውልደ ኢትዮጵያዊ የስዊድን ዜጋ እንደሆነ እና ከስዊድን ተመልሶ በአዲስ አበባ በአስገዳጅ ለይቶ ማቆያ የነበረ ነው ተብሏል።

  5. በላባደሮች ቀን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ቻይናውያን ለጉብኝት ተጉዘዋል ተባለ

    ቻይና

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በቻይና የላባደሮችን ቀን ተከትሎ የአምስት ቀናት እረፍት ይሰጣል። ይህንንም አስታከው በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ቻይናውያን ከአንዱ የአገሪቱ ክፍል ወደ ሌላኛው ተጉዘዋል ተብሏል።

    ይህም በቻይና ኑሮ በፍጥነት ወደ ቀደመ መልኩ ለመመለሱ ከዚህ የተሻለ ማሳያ አያስፈልግም አስብሏል።

    የቻይና ብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ የአገሪቱን የባህል እና ቱሪዝም ሚንስትር ጠቅሶ እንደዘገበው በቻይና ባለፉት ሶስት ቀናት ብቻ 85 ሚሊዮን ዜጎች ከአንዱ ወደ ሌላኛው ግዛት ተንቀሳቅሰዋል።

    1.67 ሚሊዮን የሚሆኑ ቻይናውያን በዋና መዲናዋ ቤጂንግ የሚገኙ 1030 ፓርኮችን መጎብኘታቸውን የሲጂቲኤን ዘገባ ጠቁሟል።

  6. በጂቡቲ የኮቪድ-19 መጨመር ለአፋር ክልል ስጋት መሆኑ ተነገረ

  7. ''ቻይና ወረርሽኙን በመደበቅ ለራሷ መድሃኒቶችን ስትገዛ ነበር'' የሚል መረጃ ወጣ

    የቻይናው ፕሬዝዳንት ሺ ዢን ፒንግ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የአሜሪካ ባለስልጣናት ቻይና የወረርሽኙነን አስከፊነት ሆን ብላ መደበቋን የሚያመላክት መረጃ ከአገር ውስጥ ደህንነት ክፍል ማግኘቱን ኤፒ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የትራምፕ አስተዳደር ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በቻይና ላይ ከፍተኛ ትችቶችን ሲሰነዝር ቆይቷል።

    ከአሜሪካው አገር ውስጥ ደህንነት ክፍል ተገኘ የተባለው መረጃ ቻይና ወደ አገር ውስጥ የምታስገባቸውን መድሃኒቶች በከፍተኛ ሁኔታ በመጨመር ኤክስፖርት የምታደርጋቸውን ቀንሳለች።

    ወረርሽኙን ለመከላከልም ስትዘጋጅ ነበር፤ መረጃውም የሚያሳየው ይህንኑ ነው ብለዋል ባለስልጣናቱ።

    አክለውም ቻይና ቀደም ብላ የዓለም ጤና ድርጅትን አላስጠነቀቀችም ብለዋል።

    በዚህም ምክንያት ከድርጅቱ በመቅደም ከተለያዩ አገራት መድሃኒቶችን እንድትገዛ አግዟታል ብለው ያምናሉ የአሜሪካ ባለስልጣናት።

  8. የአውሮፕላን ጉዞ በቀጠዮቹ ወራት የተለየ ይሆናል

  9. አገራት ለኮሮናቫይረስ ክትባት ለማግኘት በህብረት ገንዘብ እያሰባሰቡ ነው

    ምርምር

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የአውሮፓ አገራትና የሌሎች አገራት መሪዎች ለኮሮናቫይረስ ክትባት ለማግኘት የሚረዳ 8.3 ቢልየን ዶላር ለማሰባሰብ ቃል ገብተዋል።

    በዚሁ ቫይረስ ምክንያት ለሶስተ ቀናት ከፍተኛ ክትትል ክፍል ውስጥ የቆዩት የዩኬው ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን የምርምር ስራውን ለመደገፍ 388 ሚሊየን ዩሮ ቃል እንደሚገቡ ይጠበቃል።

    መሪዎች ከያሉበት አገር ሆነው ለዚሁ ጉዳይ ላይ ውይይት የሚያደርጉ ሲሆን ዩናይትድ ኪንግደም፣ ካናዳ፣ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ጣልያን፣ ጃፓን፣ ኖርዌይ፣ ሳኡዲ አረቢያና የአውሮፓ ኮሚሽን እንደሚሳተፉ ይጠበቃል።

  10. የኮሮናቫይረስ ክትባት መቼ ዝግጁ ይሆናል?

    ክትባት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለቫይረሱ የሚሆን ክትባት በያዝነው የፈረንጆቹ ዓመት መጨረሻ ይደርሳል ብለዋል። ነገር ግን ይህ ምን ያክል እርግጥ ነው?

    በአሜሪካዋ ሲያትል ከተማ በሰዎች ላይ የክትባት ሙከራው መደረግ ከተጀመረ አንድ ወር አልፎታል።

    አሁንም ቢሆን ግን ገና የሚቀሩ በርካታ ነገሮች አሉ። ምንም እንኳን የመጀመሪያ ዙር የሙከራ ክትባቱ በጥሩ ሁኔታ ቢጠናቀቅም በሰዎች ላይ በአግባቡ መሞከር አለበት፣ የመድሃኒት ተቆጣጣሪዎች ደህንነቱን ማረጋገጥ አለባቸው፣ እንዲሁም መድሃኒት አምራቾች እንዴት በብዛት ማከፋፈል እንደሚችሉ ማወቅ አለባቸው።

    እነዚህ ነገሮች በሙሉ ቀላል የማይባል ጊዜ ይፈጃሉ። ለዚህም ነው ክትባቶችን ለመስራትና ለማዘጋጀት በርካታ ዓመታት የሚወስደው።

    በርካታ የዘርፉ ባለሙያዎች እንደሚሉት የኮሮናቫይረስ ክትባት በፈረንጆቹ 2021 አጋማሽ ወይም መጨረሻ አካባቢ ዝግጁ ሊሆን እንደሚችል ተንብየዋል።

  11. ሕንዳውያን የጽዳት ሠራተኞች እና አብሳዮች ወደ ሥራ እየተመለሱ ነው

    ሕንድ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ሕንድ ሶስተኛ ደረጃ ነው የተባለለትን የእንቅስቃሴ ገደብ ማላላት ጀምራለች።

    ከዛሬ ጀምሮ የግል ቢሮዎች 33 በመቶ ሠራተኞችን ይዘው በሮቻቸውን መክፈት ይችላሉ ተብሏል። አንድ ሻጭ ብቻ ያላቸው ሱቆችም ደንበኞቻቸውን ማስተናገድ ይችላሉ ተብሏል።

    የገበያ ማዕከላት እና የገበያ ስፍራዎች ግን አሁንም ዝግ ሆነው ይቀጥላሉ።

    በግላቸው የጽዳት ሥራ የሚሰሩ፣ አብሳዮች እና የቧንቧ ሠራተኞችም ከዛሬ ጀምሮ ወደ ሥራ መመለስ ይችላሉ።

    የቫይረሱ ስርጭት በተስፋፋባቸው አከባቢዎች የእንቅስቃሴ ገደቡ ተጠብቆ ይቆያል ተብሏል። ከዚህ በተጨማሪም የህዝብ ትራንስፖርት አግልግሎት አይኖርም።

  12. በአሜሪካ 100 ሺህ ሰው በቫይረሱ ሊሞት ይችላሉ ሲሉ ትራምፕ አስጠነቀቁ

  13. ኬንያውያን ለኮሮናቫይረስ ምርመራ አንወጣም አሉ

    የኮሮና ምርመራ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የኬንያ ጤና ሚኒስቴር ዜጎች የኮሮናቫይረስ ምርመራ እንዲያደርጉ ጥሪ ቢያቀርብም እጅግ አነስተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎች ብቻ መገኘታቸው ተዘግቧል።

    መንግሥት በአንዴ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎቼ ላይ ምርመራ አደርጋለሁ ብሎ ሲሰራ ቢቆይም ለምርመራው የመጡት ግን በመቶዎች ብቻ የሚቆጠሩ ነበሩ።

    ለአገር ውስጥ መገናኛ ብዙሀን ሀሳባቸውን የሰጡ አንዳንድ ዜጎች እንዳሉት ምናልባት በምርመራው ቦታ ላይ ምልክቶችን ቢያሳዩ በራሳቸው ወጪ ወደሚቆዩባቸው ለይቶ ማቆያዎች መወሰድ አይፈልጉም።

    በዚህም ምክንያት ነው የመንግስትን ጥሪ ችላ ብለው የቀሩት።

    የጤና ሚኒስትሩ በበኩላቸው ምርመራው በነጻ ነው የሚካሄደው፤ ምልክት ያሳዩ ሰዎችም ቫይረሱ አለባቸው ማለት አይደለም ብለዋል።

  14. ፈረንሳይ፣ ስፔን እና ጣሊያን ከሳምንታት በኋላ ዝቅተኛ የሞተ መጠን አስመዘገቡ

    AFP

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    ተጥሎ የሚገኘውን የእንቅስቃሴ ገደብ ለማላላት የተለያዩ እርምጃዎችን እየወሰዱ የሚገኙት ፈረንሳይ፣ ስፔን እና ጣሊያን፤ ከሳምንታት በኋላ ዝቅተኛውን የሞት መጠን አስመዝግበዋል።

    ባለፉት 24 ሰዓታት ፈረንሳይ 135፣ ስፔን ደግሞ 164 ሟቾችን ያስመዘገቡ ሲሆን ይህም ከ7 ሳምንታት በኋላ ዝቅተኛው ነው ተብሏል።

    ጣሊያን በበኩሏ 174 ሞት በማስተናገድ ለሁለት ተከታታይ ወራት ዝቅተኛ የሟቾች ቁጥር ሆኖ ተመዝግቦላታል።

  15. በታንዛኒያ በጨለማ ቀብር ሲፈጸም የሚያሳየው ምስል ውዝግብ አስነሳ

    ማስክ ያደረገች ሴት

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    በታንዛኒያ በርካታ ሰዎች በድቅድቅ ጨለማ ሲቀበሩ የሚያሳዩ ተንቀሳቃሽ ምስሎች በአገሪቱ መንግሥት ላይ ጥያቄዎችን እያስነሱ ነው።

    ምንም እንኳን መንግሥት በቫይረሱ የሚያዙና ሕይወታቸው የሚያልፍ ሰዎች ቁጥር ዝቅተኛ ነው ቢልም በድብቅ ሲቀበሩ የሚታዩት ሰዎች ተንቀሳቃሽ ምስል ግን ቁጥሩ ከሚባለው በላይ ከፍተኛ መሆኑን ማሳያ ነው ተብሏል።

    የተቃዋሚ ፖለቲከኞች እንደሚሉት ደግሞ መንግሥት ሆን ብሎ በየዕለቱ መረጃ ባለመስጠት የቫይረሱን ስርጭት መጠን እየደበቀ ነው።

    ከሌሎች የአፍሪካ አገራት በተለየ መልኩ ታንዛኒያ የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት ጠበቅ ያለ እርምጃ ከመውሰድ ተቆጥባለች።

    ምንም እንኳን ሰዎች ለሰርግም ሆነ ለቀብር እንዳይሰባቡ ብታግድም ፕሬዝዳንቱ ዜጎች በቤተ እምነቶች በመሄድ ጸሎት እንዲያደርጉ ጠይቀው ነበር።

  16. በኮሮናቫይረስ ከተቀጠፉ ኢትዮጵያውያን መካከል ጥቂቶቹ

  17. ትራምፕ በዚህ ዓመት ክትባት ዝግጁ ይደረጋል አሉ

    Trump

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አሜሪካ ይህ የፈረንጆቹ ዓመት ከመጠናቀቁ በፊት ለኮቪድ-19 ክትባት ዝግጁ ታደርጋለች አሉ።

    "በዚህ ዓመት መጨረሻ ላይ ክትባት እንደሚኖረን እርግጠኛ ነን" ሲሉ ትራምፕ ለፎክስ ኒውስ ተናግረዋል።

    ምንም እንኳ በመላው ዓለም የሚገኙ ተመራማሪዎች ለኮቪድ-19 የሚሆን ክትባት ለማግኘት ከፍተኛ ጥረት እያደረጉ ቢሆንም፤ የዘርፉ ባለሙያዎች ግን ክትባቱን ለሰፊው ህዝብ ማቅረብ የሚቻለው በቀጣዩ የፈረንጆቹ ዓመት ሊሆን እንደሚችል ግምታቸውን አስቀምጠዋል።

    የአውሮፓውያን ዓመት ሊጠናቀቅ ገና 7 ወራት ይቀሩታል።

  18. በዓለማችን በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 3.5 ሚሊዮን ተሻገረ

    reuters

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዛሬ ላይ በመላው ዓለም በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 3,505,761 ላይ ደርሷል።

    ከእነዚህም መካከል 2.4 ሚሊዮን የሚሆኑት በቫይረሱ እየተሰቃዩ ይገኛሉ።

    በርካታ ዜጎቻቸው በኮቪድ-19 የተያዙባቸው አራት አገራት የሚከተሉት ናቸው፡

    • አሜሪካ፡ በጠቅላላው በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 1,157,945፤ በአሁን ወቅት በቫይረሱ እየማቀቁ ያሉ 939,758 እንዲሁም 67,680 ደግሞ ህይወታቸውን አጥተዋል።
    • ስፔን፡ 217,466 በቫይረሱ ተይዘዋል። 73,300 አሁን በበሽታው እየተሰቃዩ ነው። 25,264 ደግሞ ህይወታቸውን አጥተዋል።
    • ጣሊያን፡ 210,717 በአጠቃላይ ቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ናቸው። 100,179 አሁንም ኮቪድ-19 በውስጣቸው የሚገኝባቸው ናቸው። 28,884 በቫይረሱ ህይወታቸውን አጥተዋል።
    • ዩናትድ ኪንግድም፡ 187,842 ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል። 158,421 አሁንም በቫይረሱ የሚሰቃዩ ናቸው። 28,520 ደግሞ ህይወታቸውን አጥተዋል።
  19. ተጓዦች ማስክ እንዲያደርጉ በአየር መንገዶች ታዘዙ

    Air Port

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ከዚህ ሳምንት ጀምሮ ግዙፍ አየር መንገዶች የቫይረሱን ስርጭት ለመቆጣጠር ተጓዦች የፊት እና አፍ መሸፈኛ ማስክ እንዲያደርጉ ማስገደድ ይጀምራሉ ተባለ።

    በርካታ የአሜሪካ አየር መንገዶች በበኩላቸው ከተሳፋሪዎች በተጨማሪ የበረራ አስተናጋጆች እና አብራሪዎች የአፍ እና አፍንጫ መሸፈኛ እንዲያደርጉ አዘዋል።

    ከበረራ በፊት አውሮፕላኖች በጸረ-ተዋሲያን የሚጸዱ ሲሆን ተጉዦችም ወደ አየር ማረፊያ ሲሄዱ የሚኖራቸውን ንክኪ እንዲቀንሱ ምክረ ሃሳብ ተለግሷል።

  20. የታንዛኒያው ፕሬዝዳንት የማደጋስካሩን ባህላዊ መድሃኒት ወደ አገራቸው ሊያስገቡ ነው

    ባህላዊ መድሃኒቱ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የታንዛኒያው ፕሬዝዳንት ጆን ማጉፉሊ ማደጋስካር እጸዋትን በመጠቀም አግንቼዋለሁ ያለችውን የኮሮናቫይረስ ባህላዊ መድሃኒት ወደ አገራቸው ለማስገባት አውሮፕላን ሊልኩ መሆኑን ገልጸዋል።

    ምንም እንኳን የዓለም ጤና ድርጅት መድሃኒቱ ሙሉ በሙሉ ከቫይረሱ ስለማዳኑ ምንም ማረጋጋጫ የለም ቢልም ፕሬዝዳንቱ ግን መልእክቱን ችላ ያሉት ይመስላል።

    በተመሳሳይ የኮንጎ ብራዛቪል ፕሬዝዳንትም በፈሳሽ መልክ የተሰራውን የማደጋስካር ባህላዊ መድሃኒት ወደ አገራቸው ማስገባት እንደሚፈልጉ አስታውቀዋል።

    የወባ መድሃኒት ለመስራት ጥቅም ላይ ከሚውለው ‘አርትሚዝያ’ ተክል የተሰራው ይህ ባህላዊ መድሃኒትን ጨምሮ ሌሎችም ባህላዊ መድሃኒቶች ምን አይነት ጥቅምና ጉዳት እንዳላቸው ባለመረጋገጡ የዓለም ጤና ድርጅት ሰዎች እንዳይጠቀሟቸው በተደጋጋሚ ሲያሳስብ ነበር።