ትራምፕ የኢራንን ጥቃት በመስጋት በምግብ ማጓጓዣ መኪና ተሳፍረው አውሮፕላን መቀየራቸው ተዘገበ

ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

የፎቶው ባለመብት, Reuters

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 3 ደቂቃ

በኢራን ሊሰነዘር የሚችል ጥቃትን ያሰጋቸው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፣ ባለፈው ወር ቱርክ ውስጥ ከተካሄደው የኔቶ ጉባኤ የተመለሱት የሚጓዙበትን አውሮፕላን በምሥጢር ቀይረው እንደሆነ የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ዘግቡ።

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት በቴሌቪዥን ካሜራዎች በተቀረጸ ምሥል ላይ ወደ ፕሬዝዳንታዊው 'ኤር ፎርስ ዋን' አውሮፕላን ሲገቡ ታይተዋል። ኋላ ላይ ግን በአየር ማረፊያው ምግብ ማጓጓዣ መኪና አማካኝት ከአውሮፕላኑ ወርደው ወደ ወታደራዊ አውሮፕላን መዛወራቸውን ዋሽንግተን ፖስት ዘግቧል።

ትራምፕ አውሮፕላን የቀየሩት 'ኤር ፎርስ ዋን' ውስጥ ተሳፍረው የነበሩ ጋዜጠኞች እና የተወሰኑ የዋይት ሐውስ ሠራተኞች ሳያውቁ እንደሆነም ዘገባው ያስረዳል።

በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ያነጋራቸው ባለሥልጣናት በበኩላቸው፣ ኢራን አውሮፕላኑ ላይ ሚሳዔል ልትተኩስ እንደምትችል ተጨባጭ ስጋት ለዋሽንግተን ደርሶ እንደነበር ገልጸዋል። ዋይት ሐውስ ፕሬዝዳንቱ አውሮፕላን መቀየራቸውን አላረጋገጠም።

ትራምፕ፣ አንካራ ውስጥ በተካሄደው ጉባኤ ወቅት የኢራን "ቁጥር አንድ ዒላማ" እንደነበሩ ከዚህ ቀደም ተናግረዋል።

ይህ ምሥጢራዊ እርምጃ የተወሰደው፣ ዋሽንግተን እና ቴህራን ጦርነቱን ለመቋጨት የሚያደርጉት ድርድር መክሸፉን ተከትሎ አሜሪካ እንደገና በኢራን ላይ ወታደራዊ ጥቃቷን ከከፈተች አንድ ቀን በኋላ ነው።

ትራምፕ ከአንካራ ከመነሳታቸው በፊት በድሮው ኤር ፎርስ ዋን አውሮፕላን አጠገብ የምግብ ማጓጓዣ ተሽከርካሪ ታይቷል

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የምስሉ መግለጫ, ትራምፕ ከአንካራ ከመነሳታቸው በፊት በድሮው ኤር ፎርስ ዋን አውሮፕላን አጠገብ የምግብ ማጓጓዣ ተሽከርካሪ ታይቷል

ትራምፕ ወደ ቱርክ የደረሱት በኳታር በተሰጣቸውን አዲስ ቦይንግ 747-8 አውሮፕላን ነበር። ከጉባኤው በኋላ የሚመለሱት ድሮው ኤር ፎርስ ዋን አውሮፕላን እንደሚሆን ተናግረው ነበር።

ሐምሌ 1/2018 ዓ.ም. የተቀረጸ ቪዲዮ ላይ ትራምፕ በአንካራ አየር ማረፊያ ወደ ፕሬዚዳንታዊው አውሮፕላን ሲሳፈሩ ይታያል።

የዋሽንግተን ፖስት ዘገባ እንደሚያሳየው ግን፣ ከዚህ ቀረጻ በኋላ ከተሳፈሩበት ተቃራኒው በሆነው የአውሮፕላኑ ክፍል በኩል ቆሞ በነበረ የምግብ ማጓጓዣ መኪና አማካኝነት በሚስጥር ወደ ሌላ ወታደራዊ አውሮፕላን ተዛውረዋል።

ትራምፕ የተጫኑበት C-32A ወታደራዊ አውሮፕላን ቦይንግ 757 ላይ ማሻሻያ ተደርጉ የተሰራ ሲሆን፣ ብዙውን ጊዜ የሚጓዙበትም ምክትል ፕሬዝዳንቱ ናቸው።

በC-32A አውሮፕላን የሚደረገው ጉዞ መደበኛ በረራ እንደሆነ ለማስመሰል ሲባልም የመከላከያ ሚኒስትሩ ፒት ሄግሴት ብቻቸውን በደረጃ ወጥተው አውሮፕላኑ ውስጥ መግባታቸውን ጋዜጣው ዘግቧል።

ዘገባው እንደሚያመለክተው፣ በኤር ፎርስ ዋን አውሮፕላኑ ውስጥ የነበሩ ጋዜጠኞች እና የዋይት ሀውስ ሰራተኞች መስኮቱን እንዲዘገቡ ተነግሯቸው ስለነበረ፣ ፕሬዝዳንቱ አብረዋቸው እንዳልተጓዙ አላወቁም።

ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኤር ፎርስ ዋን አውሮፕላን ውስጥ ጋዜጠኞችን ሲያነጋግሩ

የፎቶው ባለመብት, Reuters

ትራምፕ በሁለተኛው አውሮፕላን ተጭነው ወደ አሜሪካ ጉዞ ከጀመሩ በኋላ ዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ አርፈው ወደ ድሮው ኤር ፎርስ ዋን አውሮፕላን ተዛውረዋል። በዩናይትድ ኪንግደም 'ሮያል ኤር ፎርስ ሚልደንሃል' ወታደራዊ አየር ማረፊያ ከደረሰ በኋላ ከድሮው ኤር ፎርስ ዋን አውሮፕላን ሲወርዱ ታይተዋል።

ፕሬዝዳንቱ እንዴት ከC-32A አውሮፕላን ወደ ኤር ፎርስ ዋን እንደተዘዋወሩ አልታወቀም።

መጨረሻ ላይ ወደ ዋሽንግተን የተመለሱት ደግሞ በኳታር በተሰጣቸው አዲስ ኤር ፎርስ ዋን አውሮፕላን እንደሆኑ ተገልጿል።

ትራምፕ በበረራው ወቅት በአውሮፕላኑ ውስጥ የነበሩ ጋዜጠኞችን አነጋግረዋል። በወቅቱ ኢራን የጋረጠችውን ስጋት ቢያነሱም፣ አውሮፕላን መቀየራቸውን አልጠቀሱም።

አውሮፕላኑ ከቱርክ በተነሳበት ወቅት ጋዜጠኞች ለምን መስኮታቸውን እንዲሸፍኑ እንደተደረገ የተጠየቁት ትራምፕ፣ "በምንጋፈጣቸው ቆሻሾች ምክንያት አደገኛ በረራ ላይ ልትሆኑ ስለምትችሉ ነው" የሚል ምላሽ ሰጥተዋል።

"ሁል ጊዜም" በሕይወታቸው ላይ "ስጋት" እንዳለ በማንሳትም በኢራን የዒላማዎች "ዝርዝር ቁጥር አንድ" ላይ መቀመጣቸውን ተናግረዋል።

"እኔ ከሄድኩ፣ እናንተም ትሄዳላችሁ" ብለዋል። "ምናልባት ሆነ ቀን ሙያችሁን መቀየር ያስፈልጋችኋል" ሲሉም አክለዋል።