ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ የምትፈጽማቸው ጥቃቶች መቀጠላቸው ተገለፀ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚፈፅማቸው ጥቃቶች መቀጠላቸውን የብሪታንያ የባህር ላይ ንግድ ስራዎች ድርጅት አስታወቀ።
በሆርሙዝ ወሽመጥ በሚንቀሳቀሱ የንግድ መርከቦች ላይ የሚደረጉ ጥቃቶች በመቀጠላቸው፥ በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው የስጋት መጠን "ከባድ" እንደሆነ መቀጠሉን ድርጅቱ አስታውቋል።
ድርጅቱ እንደገለፀው፣ ባለፈው ቅዳሜ አንድ የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች የነዳጅ መርከብ በውሃ መተላለፊያው ላይ ዒላማ የተደረገ ሲሆን፥ በወሽመጡ በኩል የሚደረገው የንግድ እንቅስቃሴ በጥቂት መርከቦች ብቻ ተወስኖ በ"ዝቅተኛ" ደረጃ ላይ ይገኛል።
“ለልየታ የሚረዱ የራዲዮ ግንኙነቶችን ማድረግ፣ ድሮኖችን ማብረር እና የንግድ መርከቦችን ዒላማ ያደረገ ክትትልን ጨምሮ የአብዮታዊ ዘቡ ጥቃቶች እና የትንኮሳ እርምጃዎች ቀጥለዋል” ሲል ድርጅቱ ባወጣው የቅርብ ጊዜ ወርሃዊ ሪፖርቱ ገልጿል።
ሪፖርቱ አክሎም “እነዚህ ድርጊቶች ኢራን ቁልፍ በሆኑ የባህር ላይ ማጓጓዣ መስመሮች ላይ ያላትን ተጽዕኖ የማጠናከር እና በመስመሮቹ በሚያልፉ መርከቦች ላይ ግፊት የማድረግ ፍላጎት እንዳላት የሚያመለክቱ ሆነው ቀጥለዋል” ብሏል። በመርከቦች አቅራቢያ የሚደረጉ የሚሳዔል ጥቃቶች እና ፍንዳታዎችን ጨምሮ ቀጥተኛ ወታደራዊ እንቅስቃሴዎችም ወደ ኦማን በሚወስዱት ደቡባዊ መስመሮች (በሊማ-ኻሳብ-ኩምዛር አካባቢ) መቀጠላቸው ተጠቅሷል።
የብሪታንያ የባህር ላይ ንግድ ስራዎች ድርጅት፣ ያልተመዘገቡ እና ያልፈነዱ ፈንጂዎች የሚያደርሷቸው አደጋዎችም በሆርሙዝ ወሽመጥ ሊቀጥሉ እንደሚችሉ አስጠንቅቋል።


