ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ታዋቂው የምጣኔ ሃብት ባለሙያ ለሱዳን የሽግግር መንግሥት ጠቅላይ ሚንስትነት ታጩ
ታዋቂው የምጣኔ ኃብት ባለሙያ የሱዳን የሽግግር መንግሥት ጠቅላይ ሚንስትር ለመሆን ታጩ።
የሱዳን ዋነኛው ተቃዋሚ፤ የቀድሞው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ከፍተኛ ኃላፊ አብደላ ሃምዶክ (ዶ/ር) ፤ ለሦስት ዓመታት ጠቅላይ ሚንስትር ሆነው ሱዳንን እንዲመሩ እጩ አድርጎ አቅርቧል።
አብደላ ሃምዶክ (ዶ/ር) የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚነታቸውን የለቀቁት ባለፈው ዓመት ነበር።
ወታደራዊ ምክር ቤቱና የነጻነትና የለውጥ ኃይሎች ጥምረት የአገሪቱን የሽግግር መንግሥት ለመጀመር በሚቀጥለው ቅዳሜ ይፈራረማሉ ተብሎ ይጠበቃል።
ሉዓላዊ ምክር ቤቱ ስድስት ሲቪሎችንና አምስት ጀኔራሎችን የያዘ ሲሆን፤ ነገ የሽግግር መንግሥቱን እንዲመሩ ይደረጋል። ከዚያ ቀጥሎም ጠቅላይ ሚንስትሩ የሚሾሙ ይሆናል።
የአጃንስ ፍራንስ ፕረስ ዘገባ እንደሚያመለክተው፤ የቀድሞው ፕሬዝዳንት ኦማር አልበሽር ባለፈው ዓመት ዶ/ር አብደላ ሃምዶክን የገንዘብ ሚንስትር አድርገው ቢሾሟቸውም ሳይቀበሉት ቀርተዋል።
ባለፈው ታህሳስ ወር በአገሪቱ በኑሮ ውድነት ሳቢያ ሰፊ ተቃውሞ ተቀስቅሶ ነበር።
ለረጅም ጊዜ የወታደሩን መቀመጫ አካባቢ ዋና መገናኛ በማድረግ የዘለቀው ተቃውሞ ፕሬዝዳንት አልበሽርን ከሥልጣን እንዲወርዱ አድርጓቸዋል።
ሮይተርስ፤ ተቃውሞውን ያቀጣጠለው የሱዳን ባለሙያዎች ማኅበርን ጠቅሶ "በሱዳን ታሪክ ለሱዳንና ለሕዝቦቿ አስቸጋሪ በሚባለው ዘመን የመጡት ዶ/ር አብደላ ሃምዶክ ይቅናቸው። ለውጥ ያመጡት ሱዳናውያን ተስፈኛ የሆኑበት ወቅት ነው" ሲል ዘግቧል።
አንድ የምጣኔ ኃብት ባለሙያ ለሮይተርስ እንደተናገሩት፤ እጩው ጠቅላይ ሚንስትር ከአፍሪካ ኅብረትና ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጋር ጥሩ ቅርርብ ስላላቸው፤ አሜሪካ ሽብርተኝነትን ይደግፋሉ ብላ ከመደበቻቸው አገራት ተርታ ሱዳን እንድትሰርዝና ብድር እንድታገኝ የማስቻል እድል ይኖራቸዋል።
አሚን ሃሰን አህመድ ሰይድ አህመድ የተባሉ ሱዳናዊ "ከሌሎች በተሻለ እንዴት ሁኔታዋችን ማለፍ እንዳለባቸው ያውቃሉ ብዬ አስባለሁ" ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
ዶ/ር አብደላ ሃምዶክ በምጣኔ ኃብት ተንታኝነት ከ30 ዓመት በላይ ልምድ አላቸው። ከካርቱም ዩንቨርሲቲና ከታወቁ የእንግሊዝ ተቋሞችም ዲግሪ አግኝተዋል።