ከስምምነቱ በኋላ የኢራን ነዳጅ ጫኝ መርከቦች የአሜሪካን እገዳ ማለፋቸውን መረጃዎች አመለከቱ
በዚህ ሳምንት ዋሺንግተን እና ቴህራን ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ካሳወቁ በኋላ ቢያንስ ሦስት የኢራን ነዳጅ ጫኝ መርከቦች የአሜሪካን እግድ አልፈው ወደ ኦማን ባሕረ ሰላጤ መሄዳቸውን መረጃዎች አሳዩ።
የመርከቦቹ እንቅስቃሴ ኢራን ወደ ውጪ የምትልከውኘ ነዳጅ ቀስ በቀስ መጀመሯን ያሳያል ተብሏል።
ግዙፍ የነዳጅ ጫኝ የሆኑት ሄሮ II እና ዲዮና እያንዳንዳቸው 2 ሚሊዮን በርሜል ነዳጅ ጭነው የኦማን ባሕረ ሰላጤን አልፈው ወደ ምሥራቅ መቅዘፋቸውን የመርከቦችን መረጃ የሚከታተሉ ሁለት ድርጅቶች ይፋ አድርገዋል።
ሴዌዝማክስ ሶኒያ I የተባለችው እና 1 ሚሊዮን በርሜል ነዳጅ የጫነች መርከብ እንዲሁ የአሜሪካ ባሕር ኃይል እገዳን አልፋ ወደ ሲንጋፖር ማምራቷን መረጃዎቹ ጠቁመዋል።
ሄሮ II ነዳጁን የጫነችው በመጋቢት የመጨረሻ ሳምንት ሲሆን፣ ዲዮና እና ሶኒያ I ደግሞ በሚያዚያ ወር መጀመርያ ሳምንት ላይ መጫናቸውን የኬፕለር መረጃ ያሳያል።
የአሜሪካ ባሕር ኃይል ወደ ኢራን ወደቦች የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦች ላይ ክልከላ በማድረጉ ቴህራን ወደ ውጭ የምትልከውን ነዳጅ በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሶ ቆይቷል።
ኢራን በግንቦት ወር ወደ ውጭ የላከችው ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት ከባለፉት ስድስት ዓመታት አንጻር ሲተይ በጣም ዝቅተኛ ነው።
በግንቦት ወር በየቀኑ 260,000 በርሜል ነዳጅ ብቻ ትልክ እንደነበር ኬፕለር ይፋ አድርጓል።
አሜሪካ እና ኢራን ጦርነቱን ለማቆም ሲስማሙ እገዳው እንደሚነሳ እና የነዳጅ ምርቷን ወደ ውጪ ለመላክ እንደምትችል መግባባታቸውን አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን ማክሰኞ ዕለት ለሮይተርስ ተናግረዋል።
የኢራን ጦርነት ከተቀሰቀሰ ወዲህ የሆርሙዝ ወሽመጥ በመዘጋቱ የዓለም የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ አሳይቷል።