በፈረንሳይ የኦርቶዶክስ ቄስ በጥይት ተመቱ

የፎቶው ባለመብት, REUTERS
የግሪክ ኦርቶዶክስ ቄስ በፈረንሳይ ሊዮን ከተማ በተተኮሰባቸው ጥይት ቆስለው ለሕይወት አስጊ የሆነ ጉዳት እንደደረሰባቸው የአገሪቱ ባለስልጣናት አስታወቁ።
ጥቃት አድራሹ ጥቃቱን ካደረሰ በኋላ ከስፍራው ቢሰወርም ፖሊስ ከዓይን እማኞች ያገኘውን መረጃ ላይ በመመስረት አንድ ተጠርጣሪ በቁጥጥር ሥር አውሏል።
ጥቃት አድራሹ ጥቃቱን ለማድረስ ምን እንዳነሳሳው እስካሁን ግልጽ ባይሆንም ፖሊስ ጉዳዩን የግድያ ሙከራ በማለት ምርመራውን ጀምሯል።
ፖሊስ የግድያ ሙከራ ያለው ጥቃት የተከሰተው በፈረንሳይ ኒስ ከተማ ሶስት ሰዎች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በስለት በደረሰባቸው ጥቃት መገደላቸውን ተከትሎ ነው።
ይህን ጥቃት የፈረንሳይ ፕሬዝደንት ኢማኑኤል ማክሮን “እስላማዊ የሽብር ጥቃት” ሲሉ መጥራታቸው ይታወሳል።
ፕሬዝደንቱ በሺዎች የሚቆጠሩ የፖሊስ አባላትን በትምህርት እና የእምነት ተቋማት ስፍራ ጥበቃ እንዲያደርጉ አሰማርተዋል።
በሊዮን ከተማ በቄሱ ላይ ጥቃቱ የተፈጸመው የእመነት አባቱ አገልግሎታቸውን ጨርሰው የቤተ ክርስቲያን በር እየዘጉ ሳሉ ነበር ብሏል ፖሊስ።
የከተማዋ ከንቲባ ግሪጎሪ ዳውሴት በበኩላቸው ጥቃት አድራሹ በቄሱ ላይ ጉዳት ለማድረስ ምን እንዳነሳሳው ግልጽ አይደለም፤ በቁጥጥር ሥር የዋለው ግለሰብን ማንነት ለመለየትም ምርመራ እየተካሄደ ነው ብለዋል።
ሁለት ጊዜ በጥይት የተመቱት ቄስ ግን ኒኮላስ ካካቬላኪስ እንደሚባሉ እና ለሕይወታቸው አስጊ የሆነ ጉዳት እንደደረሰባቸው ተገልጿል።












