ስዊትዘርላንድ የሕዝብ ቁጥሯ ከ10 ሚሊዮን እንዳይበልጥ በቀረበው ዕቅድ ላይ ድምጽ ልትሰጥ ነው

የፎቶው ባለመብት, Reuters
አንድ አገር የሕዝብ ቁጥሩ እንዳያድግ ቁጥሮችን ማስቀመጥ እና መወሰን ይቻላል?
ይህንን ለመመለስ ስዊትዘርላንድ የአገሪቱን ሕዝብ ቁጥር ከ10 ሚሊዮን እንዳይበለጥ የቀረበው ዕቅድ ላይ እሁድ ድምጽ ትሰጣለች።
ዕቅዱን ቀኝ ዘመሙ የስዊስ ሕዝብ ፓርቲ (ኤስቪፒ) ደግፎታል። ፓርቲው ዕቅዱ በመኖሪያ ቤት፣ በሕዝብ አገልግሎቶች እንዲሁም በአካባቢ ላይ ያለውን ጫና ይቀንሳል "የዘላቂነት" ጥያቄ ነው ሲል ደግፎታል።
ወደ ስዊትዘርላንድ የሚመጡ ስደተኞችን ቁጥር የመቀነስ ዓላማ ያለው ይህ የፓርቲው ሃሳብ ሕዝቡን እና አንዳንድ ተቋማትን ለሁለት ጎራ ከፍሏቸዋል።
የስዊስ መንግሥት እንዲሁም ሁሉም ትልልቅ ፓርቲዎች፣ የንግድ ድርጅት ኃላፊዎች እና የንግድ ማኅበራት በበኩላቸው "ቀውስን የሚጋብዝ" ዕቅድ ነው ሲሉ ተቃውመውታል።
ሆቴሎች እና ሆስፒታሎችን የመሳሰሉ አገልግሎት መስጫ ተቋማት አስፈላጊ የሆነ የሰው ኃይል እጥረት እንዲገጥማቸው ያደርጋል ሲሉ ተከራክረዋል።
አክለውም አገሪቱ ከአውሮፓ ኅበረት ጋር ያላትን ግንኙነት አደጋ ላይ እንደሚጥለው እና ከኅብረቱ መውጣት ደግሞ በዚህ አደጋ በሞላበት ዓለም ስዊዘርላንድን እንድትገለል እንደሚያደርግ አስረድተዋል።
የስዊትዘርላንድ ሕዝብ ቁጥር እአአ ከ2002 ጀምሮ በከፍተኛ መጠን እያደገ ሲሆን 7.3 ሚሊዮን ከነበረበት አሁን 9.1 ሚሊዮን ደርሷል። ከእነዚህም መካከል 27 በመቶ ያህሉ የውጭ ዜጎች ናቸው።
በርካታ መራጮች በሕዘብ በተጨናነቁ የባቡር ትራንስፖርት፣ እየተወደዱ በመጡ አፓርትመንቶች እና እየጨመረ በመጣው የጤና ወጪ የተነሳ ስጋት ገብቷቸዋል።
በቅርብ የተሰበሰቡ የሕዘብ አስተያየቶች ምርጫው በጠባብ ልዩነት የሚጠናቀቅ መሆኑን ያሳያሉ።
የሕዘብ ብዛቱ ላይ ገደብ ማስቀመጡን በሚደግፉ እና በሚቃወሙ መካከል 45 እና 52 በመቶ የሆነ ጠባብ ልዩነት መኖሩን ከሕዝብ አስተያየት መስጫዎች የተገኙ ቁጥሮች ያሳያሉ።
በዚህ መካከል ቀላል ቁጥር የሌላቸው መራጮች ገና ከውሳኔ ላይ አልደረሱም።
የትኛውን መደገፍ እንዳለባቸው ያልወሰኑ መራጮች በአእምሯቸው የሚመላለሰው ወሳኝ ጥያቄ የሕዝብ ቁጥር ላይ ገደብ ማስቀመጡ የሚሠራው እንዴት ነው የሚለው ነው።
የሕዘብ ቁጥርን ለመወሰን በሕግ የደነገጉ አገራት ከዚህ በፊት አልታዩም። ቻይና የሕዝብ ቁጥሯን ለመወሰን የአንድ ልጅ ፖሊሲ የነበራት ቢሆንም አሁን ትተዋለች።
የስዊስ ዕቅድ ከ2050 በፊት የአገሪቱ አጠቃላይ ሕዝብ ቁጥር ከ10 ሚሊዮን መብለጥ የለበትም የሚል ነው። እንዲሁም የሕዝብ ቁጥሩ 9.5 ሚሊዮን ከደረሰ መንግሥት እርምጃ እንዲወስድ ያዝዛል።
ይህም በስዊዘርላንድ ለመኖር የጥገኝነት ጥያቄያቸውን ተቀባይነት የሚያገኝ ሰዎችን ቁጥር መወሰን እንዲሁም ለውጭ አገር ሠራተኞች ከቤተሰብ ጋር የመቀላቀል መብቶችን ማቆምን ያካትታል።
የሕዝብ ቁጥሩን 10 ሚሊዮን እንዲሆን የሚወስነው ዕቅድ በአብላጫ ድምጽ የሚጸድቅ ከሆነ ስዊትዘርላንድ የፈረመቻቸው ዓለም አቀፍ ሕጎች፣ የአውሮፓ ኅብረት የሰዎች በነጻነት የመንቀሳቀስ መብትን ጨምሮ የሚያቋርጥ ይሆናል።
ይህ ደግሞ ለስዊትዘርላንድ ቢዝነስ ማኅበር ኢኮኖሚስዊስ (Economiesuisse) ስጋትን ፈጥሯል።
ስዊትዘርላንድ የአውሮፓ ኅብረት አባል አገር ባትሆንም አገሪቱ ከአውሮፓውያኑ 2008 አንስቶ በአባል አገራት የሰዎችን ነፃ ዝውውር የሚፈቅደው የሸንገን ስምምነት አባል ናት።
ዋና ኢኮኖሚስት የሆኑት ሩዶልፍ ሚንሽ ዕቅዱ የሚጸድቅ ከሆነ ስዊትዘርላንድ "ከአውሮፓ ኅብረት ጋር ያላት ግንኙነቶች ተግዳሮት ሊገጥማቸው ይችላል" ሲሉ ተናግረዋል።
ምክንያቱም ብራሰልስ የአውሮፓ ኅብረት አባል ያልሆኑ አገራት የኅብረቱን ነጠላ ገበያ ጥቅሞችን መምረጥ እና እንደ ነፃ የሰዎች ዝውውር ያሉ ወሳኝ መርሆዎችን ማስቀረት እንደማይችሉ ሲያስጠነቅቅ ቆይቷል።
"የአውሮፓ ኅብረት አሁንም ለስዊትዘርላንድ በጣም አስፈላጊው የንግድ አጋር ነው" የሚሉት ሚንሽ "ከዋናው የንግድ አጋራችን ጋር የተረጋጋ እና ግልጽ ግንኙነት እንዲኖረን ይጠቅመናል" ሲሉ አስረድተዋል።
የአውሮፓ የሰለጠነ የሰው ኃይልን በስፋት ሲጠቀሙ የነበሩት ስዊስ ቀጣሪዎችም እንዲሁ የሠራተኛ እጥረት ሊገጥመን ይችላል ሲሉ ሰግተዋል።
በስዊትዘርላንድ ሆቴሎች ውስጥ ከሚሰሩት ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ስደተኞች ናቸው። ሆስፒታሎችም ሆኑ የእንክብካቤ ማዕከላት የሰው ኃይላቸውን የሚያገኙት ከሌላ አገር ከመጡ ዜጎች መካከል ነው።
ስዊትዘርላንድ የባህር በር የሌላት ማዕከላዊ ምዕራብና ደቡብ አውሮጳን የምታገናኝ፣ ከአምስት የአውሮፓ አገራት ጋር የምትዋሰን ናት።
በሰሜን ጀርመን፣ በምዕራብ ፈረንሳይ፣ በምሥራቅ ኦስትርያ እና ሊሽተንስታይን፣ በስተደቡብ ደግሞ ጣሊያን ታዋስናታለች።















