ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ጉዳፍ ፀጋይ ለሕክምና በወሰደችው መድኃኒት ምክንያት ከውድድር ታገደች

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የቀድሞዋ የሁለት ጊዜ የዓለም ሻምፒዮኗ ኢትዮጵያዊቷ ጉዳፍ ፀጋይ ከውድድር በፊት እና በኋላ በተደረገ ምርመራ የተከለከለ ንጥረ ነገር እንደተገኘባት ካመነች በኋላ የአራት ወራት እገዳ ተጣለባት።
የ29 ዓመቷ ኢትዮጵያዊት በአውሮፓውያኑ 2020 የቶኪዮ ኦሊምፒክ በአጭር ርቀት የነሐስ ሜዳሊያ ካሸነፈች በኋላ በ2022 የሴቶችን የ5,000 ሜትር የዓለም አሸናፊ ስትሆን በ2023 ደግሞ በ10,000 ሜትር ውድድር ድል ተቀዳጅታለች።
ጉዳፍ ባለፈው ታኅሣሥ በዓለም አቀፍ የፀረ-አበረታች ንጥረ ነገሮች ኤጀንሲ (ዋዳ) የተከለከለ ዝርዝር ውስጥ የሚገኘው ንጥረ ነገር ምርመራ ተደርጎ ተገኝቶባታል።
በጉዳፍ ውስጥ ተገኝቶባታል የተባለው መድኃኒት በሰውነት ውስጥ የኢስትሮጅን ንጥረ ነገር መጠንን ለመቀነስ የሚረዳ እና የጡት ካንሰርንም ለማከም ይውላል።
ጉዳፍ በጥር ወር መጨረሻ ላይ በአትሌቲክስ የምርመራው ውጤት ከተገለጸላት ከአንድ ቀን በኋላ ያጋጠማትን የጤና እክል ለማከም መድኃኒቱ እንደታዘዘላት በመግለጽ እና ደጋፊ የሕክምና ሰነዶችን እና ማስረጃዎችን አቅርባለች።
በየካቲት ወር፣ ጉዳፍ ለዓለም አትሌቲክስ ፌዴሬሽን መድኃኒቱን እንድትጠቀም እንዲፈቀድላት ማመልከቻ አቅርባ ነበር፣ ይህም በኋላ ላይ ሕክምናዋ የአበረታች መድኃኒት ተቆጣጣሪ አካሉን ዓለም አቀፍ መስፈርቶች ማሟላቷን አረጋግጦ ነበር።
ነገር ግን የመድኃኒት አጠቃቀሟ በልዩ ሁኔታ ወደ ኋላ ተመልሶ ፈቃድ እንዲያገኝ ያቀረበችው ጥያቄ በተቆጣጣሪው አካል ውድቅ ተደርጓል።
የአትሌቲክስ ስፖርትን ተአማኒነት የሚከታተለው ኤኤዩ በመግለጫ እንዳመለከተው አትሌቷ ምንም ዓይነት ጥፋት ወይም ቸልተኝነትን አለመፈጸሟን በመገንዘብ በደንቡ መሠረት የተጣለባት የአራት ወራት ዕገዳ "ተገቢ እንደሆነ ይቆጠራል" ብሏል።
የቅጣቱ የጊዜ ርዝመት የሚመሠረተው የጉዳፍ የጥፋተኝነት ደረጃ፣ ጥፋቱን ወዲያውኑ በመቀበልዋ፣ ቀደም ብላ ለሚመለከተው አካል ስለመድነኒቱ አሳውቃ ቢሆን ኖሮ ሊፈቀድላት የሚችልበት ዕድል መኖሩ ከግምት ውስጥ ገብቶ ነው።
በታዋቂዋ ኢትዮጵያዊት የረጅም ርቀት አትሌት ጉዳፍ ፀጋይ ላይ የተጣለው የውድድር ዕገዳ ከሰኔ እስከ ቀጣዩ ዓመት መስከረም ማብቂያ ድረስ የሚቆይ ነው።














