ግማሽ ቢሊዮን ብር የዘረፉት ባለሥልጣን ጥፋተኛ ተባሉ

በሙስና የተጠረጠሩት የናይጄሪያ ባለሥልጣን

የፎቶው ባለመብት, BBC

ታትሟል

ሙስና በተንሰራፋባት ናይጄሪያ የገዢው ፓርቲ የፓርላማ ተጠሪ የሆኑት የሕዝብ እንደራሴ ኦሪጂ ካሉ 20 ሚሊዮን ዶላር የሚጠጋ ገንዘብ መዝብረዋል በሚል ፍርድ ቤት ጥፋተኛ ብሏቸዋል። ይህ ገንዘብ በወቅቱ ምንዛሬ ሲሰላ ግማሽ ቢሊዮን ብር ያልፋል።

ኦሪጂ ካሉ የገዢው የሙሐመድ ቡሃሪ ፓርቲ አባል ከመሆናቸውም ባሻገር በአገሪቱ ሸንጎ ውስጥ የፓርቲው ተጠሪ ሚኒስትር ነበሩ።

የሙስና ክሱ በፈረንጆች 2007 የተጀመረ ሲሆን በስማቸው በሚገኘው ኩባንያ በኩል አንዳች አሻጥር ሰርተው የመንግሥትንና የሕዝብ ገንዘብ ወደ ኪሳቸው ዶለዋል በሚል ነበር የተጠረጠሩት።

ገንዘቡ ተመዝብሯል የተባለው እርሳቸው የደቡብ ምሥራቅ አቢየ ግዛትን በሚያስተዳድሩበት ወቅት ነበር።

ካሉ ፍርድ ቤት ጥፋተኛ ሲላቸው ሰውነታቸው ይንዘፈዘፍ ነበር ሲል ጽፏል፤ አንድ የአገሬው ጋዜጣ። ፖሊሶችንም "እባካችሁ እጀ ሙቅ አታጥልቁብኝ" ብለው ሲማጠኑ ነበር።

የናይጄሪያው ፕሬዚዳንት ቡሃሪ ለ2ኛ ጊዜ ሲመረጡ ሙስናን ከስሩ ለመመንገል ቃል ገብተው ነበር።