ፕሬዝደንት ዜሌንስኪ የዩክሬን ጦር ዋና አዛዥን አባረሩ

ፕሬዝዳንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ እና ከስልጣን የተሻሩት ጄነራል ቫላሪ ዛአሉዚኒን ፕሬዝዳንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ እና ከስልጣን የተሻሩት ጄነራል ቫላሪ ዛአሉዚኒን

የፎቶው ባለመብት, VOLODYMYR ZELENSKY/X

የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ እና ከስልጣን የተሻሩት ጄነራል ቫላሪ ዛአሉዚኒን
ታትሟል

የዩክሬኑ ፕሬዝደንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ የሀገራቸው ጦር ኃይል ዋና አዛዥ የሆኑትን ጄነራል ቫላሪ ዛሉዢኒ ከስልጣን ሽረዋል።

ይህ የፕሬዝደንቱ ውሳኔ ከመሰማቱ አስቀድሞ በዜሌንስኪ እና በጄኔራል ዛሉዢኒ መካከል የተካረረ ልዩነት ተፈጥሯል የሚሉ ‘ወሬዎች’ ሲናፈሱ ነበር።

በውጊያ ሜዳ የካበተ ልምድ እንዳላቸው የተነገረላቸው ጄነራል ኦሌክሳንደር ሲሪሲክ የተባበረሩትን ጄነራል መተካታቸው በፕሬዝደንታዊ አዋጅ ይፋ ሆኗል።

በ2014 ዓ.ም የካቲት ወር ሩስያ ዩክሬን ላይ ወረራ ከከፈተች በኋላ ይህ ዓይነቱ ከፍተኛ ወታደራዊ ሹም ሽር አልተካሄደም ነበር።

ከፍተኛው ዕዝ “መታደስ” አለበት ያሉት ፕሬዝደንት ዜሌንስኪ የተሻሩት ጄነራል “በቡድኑ ውስጥ እንደሚቆዩም” ገልጸዋል።

ፕሬዝደንቱ ትላንት ሀሙስ “ካዛሬ ጀምሮ፣ አዲስ የአመራር ቡድን የዩክሬንን ጦር ኃይሎች ስልጣን ይረከባል” ብለዋል።

ከስልጣናቸው የተነሱት ጄኔራል ዛሉዢኒ በዩክሬን ወታደሮች እና ህዝብ እምነት የሚጣልባቸው ሲሆን ልክ እንደ ብሄራዊ ጀግናም ይታያሉ።

በቅርቡ በተሰበሰበ የህዝብ አስተያየት ለተሰናባቹ ጄነራል የተሰጠው ደረጃ ከፕሬዝደንት ዜሌንስኪ የሚልቅ ነው።

ዜሌንስኪ ከጄነራሉ ጋር ሰራዊት ውስጥ ለውጥ እንደሚያስፈልግ “ግልጽ ንግግር” አድርገናል ያሉ ሲሆን ላበረከቱት አስተዋጾም አመስግነዋቸዋል።

ፕሬዝደንቱ ጨምረውም አዲሱ የጦር አዛዥ ጄነራል ሲሪስኪ በጦር ሜዳ በማጥቃትም በመከላከልም በቂ ልምድ አላቸው ብለዋል።

ጄነራል ኦሌክሳንደር ሲሪሲክ አዲሱ የዩክሬን ጦር አዛዥ ሆነዋል

የፎቶው ባለመብት, VALENTYN OGIRENKO

የምስሉ መግለጫ, ጄነራል ኦሌክሳንደር ሲሪሲክ አዲሱ የዩክሬን ጦር አዛዥ ሆነዋል

ሰውዬው ሩስያ ጦርነት ስትጀምር የዩክሬን ዋና ከተማ ኪዬቭን የሚከላከለውን ጦር መርተዋል።

ቀጥሎም የዩክሬን በካሪቪ የተፈጸሙ ድንገተኛ እና ውጤታማ የመልሶ ማጥቃት ውጊያን መርተዋል። ከዚያ በኋላ የምስራቃዊ ዩክሬን የኦፕሬሽን ኋላፊ ነበሩ።

ይህንን ዓመት “ወሳኝ ማድረግ አለበን” ያሉት ዜሌንስኪ “ወሳኝ የምናደርገው የዩክሬን የቶርነት ግብ በማሳካት ነው” ሲሉ ተደምጠዋል።

የተደረገው ለውጥ ፖለቲካዊ አይደለምም ሲሉ አክለዋል።

ጨምረውም በዚህ ዓመት ከሩስያ ጋር ያለውን ጦርነት ዕውነታ የሚያሳይ ዝርዝር የጦርነት ዕቅድ እንደሚጠብቁ ጠቅሰው በጦር ሜዳ አመራር፣ በክተት ዝግጀት እና በወታደር ምለመላ ላይ የተለየ መንገድ መኖር አለበት ብለዋል።

ውሳኔው ባለፈው ዓመት ዩክሬን መልሶ ለማጥቃት የተጠቀመችብትን ዘዴ እንደሚገመግም የፕሬዝዳንቱ ቢሮ ገልጿል።