ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
አሜሪካ 21 የሳዑዲ አረቢያ የባሕር ኃይል መኮንኖችን አባረረች
አሜሪካ 21 የሳዑዲ አረቢያ የባህር ኃይል መኮንኖችን አባረረች።
ባለፈው ወር አንድ ዜግነቱ የሳዑዲ አረቢያ የሆነ የባሕር ኃይል መኮንን በአየር ኃይል አባላት ላይ የፈጸመውን ተኩስ ተከትሎ አሜሪካ 21 የሳዑዲ የባሕር ኃይል መኮንኖችን አሰናብታለች።
በነበረው ምርመራ እነዚህ 21 የሳዑዲ የባሕር ኃይል መኮንኖች ሊያስባርር የሚችል ምንም አይነት መረጃ አልተገኘባቸውም ቢባልም የአሜሪካ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ዊሊያም ባር ግን በጂሃዲስትነት የሚያስፈርጅ ቁሳቁስ ተገኝቶባቸዋል በማለት ስንብታቸውን አጽንተውባቸዋል።
ባለፈው ህዳር ወር አንድ የሳዑዲ በአሜሪካ የባህር ኃይል መኮንኖች ላይ በፈጸመው ጥቃት ሦስት መርከበኞች ሲገደሉ ስምንት ግለሰቦች ደግሞ ቆስለዋል።
ጠቅላይ አቃቤ ሕጉ የተፈጸመው ጥቃት "ሽብር" ስለመሆኑ በርካታ መረጃዎችን አግኝተናል ብለዋል።
ከተባረሩት መኮንኖች መካከል 17ቱ በኢንተርኔት የሽብር መረጃዎችን ይመለከቱ ነበር ብለዋል ጠቅላይ አቃቤ ሕጉ።
በዚህም መሰረት ከኤፍ ቢ አይ ጋር በመተባበር 21ዱ የሳዑዲ የባሕር ኃይል መኮንኖች በቂ ምርመራ ተደርጎባቸው እንዲባረሩ መደረጉ ታውቋል።
በውሳኔው የሳዑዲ መንግሥት ከስምምነት መድረሱም ተነግሯል።
ምርመራው እንደሚያሳየው ግድያውን የፈጸመው ምክትል መቶ አለቃ ሞሃመድ አልሻምራኒ ጥቃቱን ከመፈጸሙ በፊት በነበረው የእራት ስነ ስርዓት ለጓደኞቹ ጥቃት ሲፈጸም የሚያሳይ ተንቀሳቃሽ ምስል ያሰያቸው ነበር።
የፔንሳኮላ ማሰልጠኛ ለውጭ አገር የመከላከያ አባላት ማሰልጠኛ ሆኖ ለረጅም ጊዜ ሲያገለግል ቆይቷል። የሳዑዲ የመከላከያ ኃይልም ከጣሊያንና ከጀርመን ጋር በመሆን ከ1995 (እ.አ.አ.) ጀምሮ አባላቶቹን በዚህ ማሰልጠኛ ማዕከል ሲያሰለጥን ቆይቷል።
በአሁኑ ወቅትም በአሜሪካ ከ850 በላይ የሳዑዲ የባሕር ኃይል መኮንኖች እየሰለጠኑ ይገኛሉ።