የኢራንና የአሜሪካ ቅራኔ የማይፈታባቸው አምስቱ አበይት ምክንያቶች

የአሜሪካና የኢራን ተቃርኖ
የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካና የኢራን ተቃርኖ
ታትሟል

አሜሪካ የኢራንን ከፍተኛ የወታደራዊ ሹም ቃሲም ሶሊማኒን መግደሏ ጦርነቱን ወደ ለየለት ውጊያ አላስገባውም። ነገር ግን ሁለቱን አገራት ወደ ጦርነት ሊያስገቡ ይችላሉ ከተባሉት መካከል አንዱም እልባት አላገኘም።

ቅራኔው የማይቋጭባቸው ምክንያቶች ደግሞ እነዚህ ናቸው።

1 - የጦርነቱ መርገብ ጊዜያዊነት

አንዳንድ ተንታኞች የጦርነቱ መርገብ ከሁለቱ አገራት መሰረታዊ ተቃርኖ ጋር ሊገናኝ አይችልም፤ የኢራን ሹማምንት በሶሊማኒ ግድያ ድንጋጤ ውስጥ ስለገቡ በአጸፋው ምን ማድረግ እንዳለባቸው ግራ ተጋብተዋል ይላሉ። ኢራን የአሜሪካ የጦር መንደርን ኢላማ አድርጋ ለማጥቃት ሙከራ አድርጋለች። ይሁን እንጂ የተጠቀመችው ሚሳኤል በራሷ ግዛት ብቻ የሚሰራ ነበር።

የወሰደችው እርምጃም ተግባራዊና ፖለቲካዊ ድክመት ነበረበት። ነገሮችን በፍጥነት ማድረግ ፈለገች እንጂ ሚዛኑን የጠበቀ አልነበረም። በመሆኑም ወደ ለየለት ጦርነት መግባት አልፈለገችም። እናም ይህ ምዕራፍ እንዳልተዘጋ በርካታ የኢራን ጉዳይ ያገባናል የሚሉ ሰዎች ግልጽ እየሆነ መምጣቱን ይናገራሉ።

የዩክሬንን የመንገደኞች አውሮፕላን መምታቷን ማመኗም ሌላኛው የጦርነቱ ማርገቢያ መንገድ ነው፤ ግን ስህተት ነበር።

ኢራን በባህሪያዋ ምንም ነገር አድርጌያለሁ ብላ አታምንም። ነገር ግን የአሜሪካ የመረጃ ባለሙያዎች አውሮፕላኑን ኢራን መትታ እንደጣለችው በቂ መረጃ አለን ማለታቸውን ተከትሎ ኢራን ለመካድ የሚያበቃ ምክንያት አልነበራትም፤ እናም አመነች።

ኢራን አውሮፕላኑን መምታቷን ካመነች ወዲህ ተቃውሞው ተጧጡፏል። ይህ ደግሞ ሌላኛው የጦርነቱ አለመርገብና በጊዜ ሂደት የሚያገረሽ መሆኑን ማሳያ ያደርጉታል። ይህም ስህተት የመጣውና ህዝቡንም ለተቃውሞ ሹማምንቶቹንም ለማሸማቀቅ የዳረጋቸው አሜሪካ ባመጣችው ጣጣ ነው ተብሎ ስለሚታሰብ።

ኢራን የመታችው የዩክሬን አውሮፕላን
የምስሉ መግለጫ, ኢራን የመታችው የዩክሬን አውሮፕላን

2 - ለምን አሜሪካ ሶሊማኒን መግደል ፈለገች?

አሜሪካ ሶሊማኒን የገደለችው የአሜሪካን ጥቅም ለመጠበቅ በሚል እሳቤ ነው። ይህ ግን በርካታ ተንታኞችን አያስማማም። ጥቃቱ በአንጻሩ በሁለቱ አገራት መካከል የኃይል ልዩነት እንዳለ ለማስገንዘብ የታሰበ መሆኑን ይገልጻሉ።

በርግጥ ለአጭር ጊዜ ይሰራል። ነገር ግን ኢራን ቀጣይ የቤት ሥራዋን በአግባቡ እንድትሰራ የሶሊማኒ መገደል ጠንከር ያለ ትምህርት በመስጠት ከፍ ላለ ጦርነት ዝግጁ ያደርጋታል። በሌላ በኩል ደግሞ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኢራንን አስፈራርተው በቀጠናው ሌላም አደብ ማስገዛት የሚፈልጉት ኃይል መኖሩን ጠቆም አድርገዋል። በመሆኑም ለየትኛውም ግጭት ይህ መልዕክታቸው የአሜሪካን ዝግጁነት የሚያሳይ ነው።

አሜሪካ የኢራንን ኢኮኖሚ ማድቀቋን ትቀጥላለች። ወደ ድርድር ጠረጴዛ አታመጣትም። በአንጻሩ በራሷ ጉዳይ ተወጥራ እንድትቀርና ኢራን የቤት ሥራዋ የበዛባት አገር እንድትሆን ልታደርጋት ትችላለች የሚሉ ትንተናዎች በብዛት ይስተዋላሉ።

3 - የኢራን ስትራቴጂክ ግብ ተመሳሳይ ነው

የኢራን ኢኮኖሚ በመዳከሙ በርካታ ኢራናዊያን ደስተኛ አይደሉም። ነገር ግን የኢራን መንግሥት "አብዮታዊ ስርዓት ነው"። በቀላሉ የሚንገራገጭ አይደለም። የኢራን ስትራቴጂክ ግብ አሜሪካን ከቀጠናው ማስወጣት ነው፤ ቢያንስ ከኢራቅ።

በመሆኑም አሁን ሶሊማኒ ከሞተ በኋላ ይህ እየተሳካ ያለ ይመስላል። ከኢራን ሹማምንቶች አንጻር የኢራን ፖሊሲ በጣም ውጤታማ እየሆነ ነው። የባሽር አል-አሳድ መንግሥት ከሶሪያ እንዳይፈርስ በመታደግ ለእስራዔል ተጨማሪ ኃይል ኢራናዊያን አሰባስበዋል። በኢራቅ ላይም ያለው ተጽዕኖ ቀላል አይደለም። ከትራምፕ ጋር ወዳጅ የነበሩ አገራትም በሶሊማኒ ላይ በተወሰደው ርምጃ በመስጋት ራሳቸውን ወደመቻል እያዘነበሉ ነው።

ሳዑዲ የነበራትን የሻከረ ግንኙነት ማለዘብ ጀምራለች፤ ቱርክ ከሩሲያ ጋር አዲስ የወዳጅነት ምዕራፍ ከፍታለች። አሁን የሶሊማኒ ግድያን በበጎ የምትመለከተው እስራኤል ብቻ ነች።

ኢራናዊያንም በግድያው ተበሳጭተው ሊሆን ይችላል። የውስጥ ግፊትና የኢኮኖሚው ሁኔታ በአሜሪካ ላይ ጫና እንዲያሳድሩ ይገፋፋቸዋል። ግድያውን ተከትሎም ያደረገቻቸው ሁለት የበቀል ርምጃዎች በቀጣይ አሻሽላ ለማጥቃት ትምህርት የሚሰጡ ናቸው። ይህም ሌላኛው የጦርነቱ ጉዳይ ያልተቋጨ መሆኑን ማሳያ አድርገው ይወስዱታል።

4 - በኢራቅ አቋም ላይ ተቃርኖ አለ

አሁን ከኢራቅ የሚወጣው የአሜሪካ ወታደር የሚያሳየው ነገር ግልጽ ነው። የኢራቅ ጊዜያዊ መንግሥት በውስጣዊ ተቃውሞ እየተናጠ ነው። ብዙ ሰዎች በአሜሪካ ጣልቃ ገብነትም ሆነ በኢራን ጫና ደስተኞች አይደሉም።

የኢራቅ የፓርላማ የማይቀለበስ ውሳኔ አሳልፏል። የአሜሪካ የጦር ኃይል ከኢራቅ ይውጣልኝ ብሏል። እርግጥ የአሜሪካ ወታደሮች ነገ ከኢራቅ ይወጣሉ ማለት አይደለም። ነገር ግን የተወሰነ ጊዜም ቢሆን እዚያው ለማቆየት ዲፕሎማሲያዊ ድርድር ያስፈልጋል። በአንጻሩ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራቃዊያንን ማስፈራራትንና ያወጣነውን ወጪ ትመልሳላችሁ ማለትን መርጠዋል።

የአሜሪካ በኢራቅ ጣልቃ ገብነት ወሳኝ ነው። የአይ ኤስ ጦር ጥቃት ማድረሱን እስከቀጠለ ድረስ የአሜሪካ በቀጠናው መኖር አስፈላጊ ነው። ከቀጠናው እንዲወጡ ከተደረጉ ግን የአይ ኤስ ታጣቂዎችን ለማጥቃት የሚያስችል ምቹ ሁኔታ ለአሜሪካ ሊኖር አይችልም።

በርግጥ የአሜሪካ ወታደር ከኢራቅ በመውጣቱ ጉዳይ ላይ የመረጨሻ ውሳኔ ላይ አልተደረሰም፤ ነገር ግን አሜሪካ ወታደሮቿን የምታስወጣ ከሆነ ኢራን ታሸንፋለች። የሚቆዩ ከሆነ ግን የተገላቢጦሽ ይሆናል። ይህም የውጥረቱ ማጠንከሪያ ይሆናል ተብሎ ይገመታል።

የአሜሪካ ወታደር በኢራን
የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ ወታደር በኢራን

5 - የኒውክሌር ስምምነቱ ዋነኛው የተቃርኖ ግንድ ነው

አሁን የተጀመረው ቀውስ የሚጀምረው ፕሬዝዳንት ትራምፕ በ2018 የኢራንን የኒውክሌር መርሃ ግብር ካስቆሙበት ጊዜ ነው። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ አሜሪካ በኢራን ላይ ማዕቀቦችን እየጣለች የኢራንን ኢኮኖሚ በማዳከም በአንጻሩ ኢራን ደግሞ የቀጠናውን አጋሮቿን በማግባባት የተጣለባትን ማዕቀብ ስትወጣ ቆይታለች።

የኒውክሌር ስምምነቱ እንዲቆይ የፕሬዝዳንት ትራምፕ መልካም ፈቃድ አስፈላጊ ነው። የሆነ ነገር ከተቀየረ ግን የመጨረሻው መጀመሪያ ሆነ ማለት ነው። ስምምነቱ ወሳኝ ነው።

ከስምምነቱ በፊት ኢራንና እስራኤል ጦርነት ውስጥ የሚገቡበት እድል ሰፊ ነበር። ነገር ግን ስምምነቱ ይህን አርግቧል። አሁን ያ የሚቀጥል አይመስልም። ይህ ከሆነ ደግሞ ጊዜ ሲጠብቅ የነበረው አይቀሬው ጦርነት በራሱ ጊዜ ይጀመራል ማለት ነው።