የጆርጅ ፍሎይድ ገዳይ የክስ ሂደቴ እንደ አዲስ ይታይልኝ አለ

ዴሪክ ሾቪን
ታትሟል

የሚኒያፖሊስ ከተማ የቀድሞ የፖሊስ አባል የነበረው እና ባሳለፍነው ወር በጆርጅ ፍሎይድ ግድያ ጥፋተኛ የተባለው ዴሪክ ሾቪን የክስ ሂደቱ በድጋሚ እንዲታይለት ጠየቀ።

የ45 ዓመቱ ዴሪክ ሾቪን ከወራት በፊት ጥቁር አሜሪካዊውን ጆርጅ ፍሎይድን በቁጥጥር ሥር ለማድረግ የተጠርጣሪው አንገት ላይ ከ9 ደቂቃዎች በላይ በጉልበቱ አፍኖ ሲቆይ በተንቀሳቃሽ ምስል ተቀርጾ ነበር።

ይህ የቀድሞ የፖሊስ አባል ተግባር በርካቶችን አስቆጥቶ የነበረ ሲሆን፤ የፖሊስ አባሉ አላስፈላጊ ኃይል ተጠቅሟል በሚል እና ዘረኝነትን በመቃወም በመላው ዓለም የተቃውሞ ሰልፎች ተካሂደው ነበር።

ሾቪን በአገሪቱ የወንጀል ሕግ፤ በሦስት የግድያ ወንጀል ክሶች ነው ጥፋተኛ የተባለው።

ይሁን እንጂ የቀድሞ የፖሊስ አባሉ ጠበቆች የደንበኛቸው ጉዳይ በድጋሚ እንዲታይ የጠየቁት፤ ዓቃቤአን ሕግ ብሎም ጉዳዩን እንዲመረምሩ የተሰየሙ ዳኞች ያልተገባ ምግባር ነበራቸው በሚል ምክንያት ነው።

በጆርጅ ፍሎይድ አንገት ላይ ከ ዘጠኝ ደቂቃ በላይ ተንበርክኮ በቪዲዮ የታየው ሾቪን፤ በግድያ ወንጀል ጥፋተኛ ተብሎ ነበር። ጠበቃው ደንበኛዬ ነፃ እና ገለልተኛ የፍርድ ሂደት አላገኙም ሲሉ ተከራክረዋል።

ለዚህም ከክስ ሂደቱ በፊት በነበረው የመገናኛ ብዙሃን ዘገባ ምክንያት ጉዳዩ ታዋቂ መሆኑ ነው ሲሉም ጠበቃው ለችሎት አስረድተዋል።

ጉዳዩ ከክስ በፊት ብሎም ከክስ በኋላ "እጅግ የተናፈሰ እና ጭፍን ጥላቻ የተሞላበት ነበር" ሲሉ ጠበቃው ለችሎቱ ጽፈዋል። ይህም በክስ ሂደቱ ወቅት "መሠረታዊ መጓደል" አስከትሏል ሲሉም ተከራክረዋል።

ክሱ ጨምሮም በዳኞች የተሰሩ ስህተቶች ነበሩ፤ የዓቃቤ ሕግ ስነ-ምግባር ብሎም ምስክሮችን የማዋከብ እና የማዋረድ ተግባራትም ነበሩ ሲል ዘርዝሯል።

በአሜሪክ የዘር መድልኦ ታሪክ ውስጥ በጣም ባተልመደ መልኩ የዚህ የፖሊስ አባል ላይ የተሰጠው ፍርድ ታሪካዊ ከመባሉ ባለፈ በበርካታ አሜሪካዊያን ዘንድ አድናቆት የተቸረው ነበር።

ሾቪን በሚቀጥለው ወር የቅጣት ውሳኔ ያገኛል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን ጥፋተኛ ከተባለባቸው ክሶች አንጻር ሲታይም እስከ 40 ዓመት በማረሚያ ሊያሳልፍ ይችላል።