ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ልጆቿን ወደ ትምህርት ቤት በማድረስ ላይ ሳለች የተገደለችው እናት
ስፔናዊያን ከፍተኛ ድንጋጤ ውስጥ የከተተ ዜና ነው።
የ45 ዓመቱ ጎልማሳ የቀድሞ ባለቤቱን የገደለበት መንገድ ነው በአገሪቱ ከፍተኛ ድንጋጤን የፈጠረው።
ሰኞ ጠዋት እናት ልጆቿን አለባብሳ፥ ቁርስ አብልታ፣ በመኪና ወደ ትምህርት ቤት እየወሰደቻቸው ሳለ የቀድሞ ባለቤቷ መሣሪያውን አቀባብሎ ልጆቿ ፊት እዚያው መኪና ውስጥ ገድሏታል።
ጆሴ ሉዊስ ድርጊቱን ስለመፈጸሙም ለፖሊስ ተናዟል።
ፖሊስ እንደሚለው ግለሰቡ ከዚህ ቀደም በወንጀለኝነት አይታወቅም። የጾታ ጥቃት ክስ ቀርቦበትም አያውቅም።
ገዳይና ሟች (ባልና ሚስት) ፍቺ የፈጸሙት ባለፈው ዓመት ነበር።
ሆኖም ገዳይ በቅርብ ጊዜ በፌስቡክ ገጹ ላይ "ትዳራችንን አፈረስሽ፤ አሁን ደግሞ ልጆቼን እንዳላያቸው ታደርጊያለሽ?" ሲል ጽፎ ነበር ብሏል አንድ የስፔን ጋዜጣ።
የስፔኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ግድያውን "ዘግናኝ"ሲሉ ያወገዙት ሲሆን ድርጊቱ ጸታዊ ጥቃት ነው እንፋለመዋለን ብለዋል በትዊተር ገጻቸው። "የሴቶች በየሥፍራው መገደል እስኪቆም ድረስ ትግላችን አይቆምም" ብለዋል።
ይህ የወንጀል ድርጊት የተፈጸመው በጋሊሺያ ክልል ቫልጋ በተባለች ከተማ ውስጥ ነው።
የልጆቹ እናት መኪና ውስጥ ልጆቿ ፊት ከመገደሏ በፊት ድረሱልኝ ስትል የጠራቻቸው እህትና እናቷንም ግለሰቡ ተኩሶ ገድሏቸዋል።
ሦስቱን የቤተሰብ አባላትን ልጆቹ ፊት ከገደለ በኋላ ሽጉጡን በአቅራቢያ ወንዝ ወርውሮ ለአፍታ ተሰውሮ ነበር ግለሰቡ። በኋላ ነው በራሱ ጊዜ እኔ ነኝ ሲል ለፖሊስ እጁን የተሰጠው።
የቫልጋ ከተማና አካባቢው ይህ አሰቃቂ ወንጀል ተከትሎ የሦስት ቀን ሐዘን አውጀዋል። የአራትና የሰባት አመቱ አዳጊዎች አጎታቸው ጋ ጥበቃ እየተደረገላቸው በልዪ ከለላ ላይ ይገኛሉ።