300 በላይ ናይጄሪያውያን ከደቡብ አፍሪካ ወደ አገራቸው ተመለሱ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ናይጄሪያ ስድስተኛው እና የመጨረሻ ነው ባለችው ጉዞ ወደ አገራቸው ለመመለስ ፈቃደኛ የሆኑ 306 ሰዎችን ወደ አገራቸው መመለሷን አስታወቀች።
ተመላሾቹ ዛሬ ረፋድ ላይ በሌጎስ በሚገኘው ሙርታላ ሙሐመድ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ደርሰዋል።
በደቡብ አፍሪካ መጤ ጠል ዘመቻ ዳግም ካገረሸ በኋላ ወደ አገራቸው በፈቃደኝነት የተመለሱት ናይጄሪያውያን ቁጥር ከ1200 በላይ መሆኑ ተገልጿል።
በደቡብ አፍሪካ በዚህ ዓመት አጋማሽ ላይ የተጀመረው መጤ ጠል እንቅስቃሴ በብዛት ሰላማዊ የነበረ ቢሆንም፤ ነገር ግን በአንዳንድ አካባቢዎች ብጥብጥ፣ ማስፈራራት እና የሕይወት መጥፋት ተከስቷል።
የደቡብ አፍሪካ ፖሊስ በተፈጠሩ ክስተቶች ዙሪያ ምርመራ እያደረገ መሆኑን አስታውቋል።
የናይጄሪያ መንግሥት ንግዳቸውን፣ ቤታቸውን እና ያላቸውን ንብረት ትተው ከደቡብ አፍሪካ እንዲወጡ ለተደረጉ ዜጎቹ ካሳ እንደሚጠይቅ አስታውቋል።
የደቡብ አፍሪካ ባለሥልጣናት በበኩላቸው ምንም ዓይነት ካሳ እንደማይከፍሉ ተናግረዋል።
በናይጄሪያ ምክር ቤት የዲያስፖራ ጉዳዮች ኮሚቴ በደቡብ አፍሪካ በሚገኙ ስደተኛ ዜጎቹ ላይ የደረሰውን እና ከአገር መውጣታቸውን ተከትሎ የሁለቱ አገራት ግንኙነትን እያጤነው መሆኑን አስታውቋል።
የደቡብ አፍሪካ መንግሥት ከአምስት ሳምንታት በፊት "የስደተኞች አስተዳደር" ላይ ዘመቻ ከከፈተ በኋላ ከ53,000 በላይ የውጭ ዜጎች ከአገር መባረራቸውን ወይንም እንዲወጡ መደረጋቸውን አስታወቀ።
እነዚህ ስደተኞች ከማላዊ፣ ከዚምባብዌ እና ከሞዛምቢክ የመጡ መሆናቸውን የገለጹት ባለሥልጣናቱ፤ ቁጥሩ ከዚህም በላይ ሊጨምር ይችላል ብለዋል።
በደቡብ አፍሪካ ለተከታታይ ሳምንታት ፀረ ስደተኛ ሰልፎች ከተካሄዱ እንዲሁም አለመረጋጋት፣ ማስፈራራት እና ዘረፋ ከተፈጸመ በኋላ በአገሪቱ ያለ ሕጋዊ የመኖሪያ እና የሥራ ፈቃድ የሚገኙ ስደተኞች ላይ ሰፊ የተባለ ዘመቻ እያካሄደች ትገኛለች።





















