ኢራን “በአሜሪካ ጫና” ምክንያት ሆርሙዝን በተመለከተ ከኦማን ጋር ስምምነት ላይ አለመድረሷን ገለጸች

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ኢራን እና ኦማን በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚደረግ የመርከቦች ጉዞን በተመለከተ ያደረጉት ንግግር ያደረጉት “በአሜሪካ ጫና” ምክንያት ስምምነት ላይ መድረስ እንዳልቻሉ ቴህራን አስታወቀች።
በኢራን እና አሜሪካ ጦርነት እንዲሁም ድርድር የክርክር ማዕከል የሆነው የሆርሙዝ ወሽመጥ ከዓለም ነዳጅ እና ጋዝ ምርት ውስጥ 20 በመቶ ገደማው ይተላለፍበት የነበረ የወሳኝ የባሕር መስመር ነው። ከጦርነቱ ወዲህ በወሽመጡ ላይ ያላትን ቁጥጥር ያጠናከረችው ኢራን፤ በሆርሙዝ ሌላኛው ጫፍ ከአሁን በኋላ ከምትገኘው ኦማን ጋር በመነጋገር እንደምታስተዳድረው ስትናገር ቆይታለች።
የኢራን እና ኦማን ባለሥልጣናት ትናንት ቅዳሜ ዕለት የባሕር መስመሩን ትራፊክ አስተዳደር በተመለከተ መወያየታቸው ተገልጾ ነበር።
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ኢስማኢል ባቃኢ ዛሬ ሰኞ ውይይቱን አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ፤ በኦማን ዋና ከተማ በተካሄደው ውይይት ስምምነት ላይ አለመደረሱን አስታውቀዋል። ቃል አቀባዩ፤ “ቅዳሜ ዕለት ሙስካት ውስጥ የተደረገው ንግግር [ከአሜሪካ ጋር በተፈረመው] የመግባቢያ ስምምነት አንቀጽ 5 ላይ በሚገኘው የሆርሙዝ ወሽመጥ ጉዳይ ላይ ብቻ ያተኮረ ነበር” ብለዋል።
አክለውም፤ “አሜሪካ ግልጽ እና ድብቅ በኦማን ላይ ባሳደረችው ጫና ምክንያት መከናወን የነበረበት ነገር ባለመሳካቱ እና ባለመፈጸሙ እናዝናለን" ሲሉ ዋሽንግተንን ተጠያቂ አድርገዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ ኢራን ሆርሙዝ በድጋሚ መዘጋቱን ካስታወቀች በኋላ ከትናንት ምሽት አንስቶ እስካሁን ምንም መርከብ በወሽመጡ እንዳላለፈ ‘ማሪን ትራፊክ’ ከተሰኘው የመርከቦች ጉዞ መከታተያ ድረ ገጽ የተገኘው መረጃ አሳይቷል።
ኢራን የአሜሪካ ጦር በሚያደርገው “ሕገ ወጥ እንቅስቃሴ” ምክንያት በአሁኑ ሰዓት በሆርሙዝ በኩል ጉዞ ማድረግ “የማይቻል” መሆኑን በትናንትናው ዕለት ገልጻ ነበር።
አሜሪካ በበኩሏ ወሳኙ የባሕር መተላለፊያ ክፍት ነው በሚል አቋሟ ጸንታለች። የአሜሪካ ማዕከላዊ እዛ በወጣው መግለጫ ሆርሙዝ ክፍት እንደሆነ እንዲሁም ጦሩ የመርከብ ጉዞ ነጻነትን ለማስጠበቅ ዝግጁ መሆኑን ገልጿል።

