እስራኤል የኢራን ተደራዳሪዎችን ለመግደል እያሴረች እንደነበር ተዘገበ
አሜሪካና ኢራን ወሳኝ የሆነውን የተኩስ አቁም ስምምነት በደረሱበት እስራኤል የኢራንን ከፍተኛ ተደራዳሪዎች ለመግደል እያሴረች እንደነበር የአሜሪካ ባለሥልጣናት እንደሚያምኑ ‘ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ’ ጋዜጣ ዘገበ።
ባለፈው ሚያዝያ አሜሪካ እና ኢራን ጦርነቱን በተኩስ አቁም ጋብ ለማድረግ ያስቻለው ንግግር ወደ መቋጫው ሲቃረብ ዋነኛ የኢራን ተደራዳሪዎች የሆኑት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ እና የፓርላማው አፈ ጉባኤ መሐመድ ባገር ጋሊባፍ የእስራኤል ዒላማ ሊሆኑ ይችላሉ የሚል ስጋት አሜሪካ ተፈጥሮባት እንደነበር ባለሥልጣናት መናገራቸውን ጋዜጣው አስነብቧል።
እንደ ዘገባው ከሆነ ከፍተኛ ስጋት የተፈጠረበት የትራምፕ አስተዳደር እስራኤል ሁለቱን የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ዒላማ ልታደርግ እንደምትችል ቴህራንን እንዲያስጠነቅቁ በአካባቢው አገራት በኩል መልዕክት አስተላልፏል።
የአሜሪካ ባለሥልጣናት በሚያዝያ ወር ድርድሩ ከተጀመረ በኋላ የሚደረግ ማንኛውም የግድያ ሙከራ ውይይቱን እንደሚያቆመው እና ግጭቱን እንደገና እንደሚያባብሰው ስላመኑ ነበር ስጋት የተፈጠረባቸው ተብሏል።
የኢራኑ ፓርላማ አፈ ጉባዔ እና ዋነኛው ተደራዳሪ ጋሊባፍ የእስራኤል የግድያ ዒላማ ዝርዝር ውስጥ መግባታቸውን አሜሪካ ከተረዳች በኋላ እስራኤል ምንም ዓይነት እርምጃ እንዳትወስድ እንዳሳሰበች ጋዜጣው ዘግቧል።
የኢራን ባለሥልጣናት እስራኤል በዲፕሎማሲያዊ ስብሰባዎች ወቅት የድርድር ቡድኗን ዒላማ እንዳታደርግ በፓኪስታን እና በኳታር አሸማጋዮች በኩል የአሜሪካን ዋስትና እንደምትፈልግ መጠየቋንም ጠቅሷል።
ዘገባው ጨምሮም ሚያዝያ ወር ላይ የኢራን የደኅንነት ኃይሎች ሁለት የእስራኤል አውሮፕላኖች ወደ ኢራን የአየር ክልል መግባታቸውን በመጥቀስ ከፓኪስታን ወደ ቴህራን የመልስ በረራ ወደ ላይ የነበሩት ጋሊባፍ አቅጣጫቸውን ቀይረው ማሽሃድ ወደተባለችው የኢራን ከተማ ማምራታቸውን ገልጿል።
ዘገባውን በተመለከተ በአሜሪካ የሚገኘው የእስራኤል ኤምባሲ ባለሥልጣናት አስተያየት ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ጋዜጣው አመልክቷል።