ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
የፔሎሲን ጉብኝት ተከትሎ ቻይና በታይዋን አቅራቢያ ወታደራዊ ልምምድ ጀመረች
የአሜሪካ የኮንግረስ አባልና የምክር ቤቱ አፈ ጉባኤ ናንሲ ፔሎሲ ታይዋንን መጎብኘታቸውን ተከትሎ ቻይና በታይዋን አቅራቢያ ወታደራዊ ልምምድ ማድረግ ጀመረች።
በታይዋን ባሕር አካባቢ ነው ወታደራዊ ልምምዱ የተጀመረው።
ቻይና በቀጠናው ያለውን ማኅበረ-ፖለቲካዊ መዋቅር (status quo) ለመቀየር እየሞከረች ነው ስትል ታይዋን ከሳለች።
ቻይና እንደተገንጣይ ግዛቷ የምታያት ታይዋንን ፔሎሲ መጎብኘታቸው ማወዛገቡን ቀጥሏል።
ቻይና የጀመረችው ወታደራዊ ልምምድ ከዚህ ቀደም በታይዋን አቅራቢያ ካደረገቻቸው የበለጠ ነው።
ልምምዱ የረዥም ርቀት ተኩስን እንደሚጨምር ቻይና አስታውቃለች።
ታይዋን እንደምትለው ወታደራዊ ልምምዱ የባሕር እና አየር በረራ መስመሮችን ስለሚዘጋ፣ ጃፓን እና ፊሊፒንስ ተለዋጭ የአየር መስመር እንዲሰጧት ትጠይቃለች።
በታይዋን ኪንሜን ደሴት ዙሪያ ሲበር የነበረ የጦር ጀትና ሌሎችም ተዋጊ አውሮፕላኖችን ከአካባቢው ለማሸሽ ታይዋን ቀለም የሚለቅ መድፍ ተኩሳለች።
የታይዋን መንግሥት እንዳለው ብዙ የአገሪቱ ባለሥልጣናት የበይነ መረብ ጥቃት እየደረሰባቸው ነው።
የአሜሪካ ብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ ጃክ ሱልቫን የቻይና ወታደራዊ ልምምድ ኃላፊነት የጎደለውና ከቁጥጥር ሊወጣ የሚችል እንደሆነ አስጠንቅቀዋል።
ቻይና ወታደራዊ ልምምድ ለማካሄድ የመረጠቻቸው አካባቢዎች ከጃፓን የምጣኔ ሀብት ቀጠና (ኢኢዜድ) ጋር የሚጣረስ እንደሆነ ጃፓን ተናግራለች።
ታይዋን ነጻ አገር እንድትሆን ንቅናቄ ከሚያደርጉ አንዱን ትላንት ቻይና አስራለች።
በታይዋን ደሴት ዙሪያ ስድስት ትልልቅ የወታደራዊ ልምምድ ቦታዎች የተከበቡ ሲሆን፣ ልምምዱም ለአራት ቀናት ይቆያል።
ቻይና እአአ በ1996 ተመሳሳይ ልምምድ አድርጋለች።
ያኔ ልምምዱ የተካሄደው ከታይዋን ግዛት በርቀት ላይ ነበር።
አሁን ግን ወታደራዊ ልምምዱ በታይዋን 12 ማይል ርቀት ውስጥ ይከናወናል።
የታይዋን መከላከያ ሚኒስትር የቻይና አካሄድ የተባበሩት መንግሥታትን መርኅ ይጥሳል ብሏል።
ቻይና ወደ አካባቢው ወታደራዊ መርከብና አውሮፕላን ብታስጠጋ እንደ ወረራ ይቆጠራል። ታይዋንም ራሷን መከላከሏ አይቀርም።
የአሜሪካ ባሕር ኃይል ውጥረቱን በቅርበት እየተከታተለ ይገኛል።
ፔሎሲ ታይዋንን በመጎብኘት ባለፉት 25 ዓመታት ውስጥ የመጀመሪያዋ ከፍተኛ የአሜሪካ ፖለቲከኛ ናቸው።