በአሜሪካ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች በመዘጋታቸው ምክንያት ትራምፕ 'የዲሞክራቶች ተቋማት' ላይ አነጣጥረዋል

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 3 ደቂቃ

ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከተዘጉ ሦስት ቀን ሊሞላቸው የተቃረቡትን የአሜሪካ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ምክንያት በማድረግ እሳቸውም ሆኑ የበጀት ዳይሬክተሩ የትኛዎቹን የዲሞክራቶች ተቋማት እንደሚቀንሱ እንደሚሠሩ ተናግረዋል።

ሪፐብሊካኖች ዕድሉን እንዲጠቀሙም ሃሳባቸው አቅርበዋል። በዚህም በመንግሥት የገንዘብ ድጋፍ የሚደረግለት ሕግ የጤና እንክብካቤ ኢንሹራንስ ድጎማዎችን ማካተት ያስፈልጋል የሚለውን የዲሞክራቶች ፍላጎት ወደ ጎን እንዲሉ ጠይቀዋል።

በካፒቶል ሂል የሚገኙት ሪፐብሊካኖች እና ዲሞክራቶች የመንግሥት ተቋማት ሥራ ላይ ባለመሆናቸው ምክንያት እርስ በእርሳቸው መወነጃጀላቸውን ቀጥለዋል።

በዚህ ምክንያትም በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ የፌደራል ሠራተኞች ቤት እንዲቆዩ ሆነዋል። ሌሎች ደግሞ ያለ ክፍያ ለመሥራት ተገድደዋል። አንዳንድ የፌዴራል ፓርኮች ለጎብኚዎች የተዘጉ ሲሆን እንደስታቹ ኦፍ ሊበርቲ ያሉት ክፍት ሆነዋል።

ተንታኞች ሁለቱም ወገኖች ከአሜሪካውያን ጫና ሳይደረግባቸው ይስማማሉ ብለው አይጠብቁም።

ትራምፕ በሐሙስ ዕለት ከአሜሪካ የበጀት እና አስተዳደር ቢሮ (ኦኤምቢ) ዳይሬክተር ከራሰል ቮውት ጋር ባደረጉት ውይይት ምን ሊወስኑ እንደሚችሉ በትክክል ግልጽ አልሆነም።

የአገሪቱ ኮንግረስ የመንግሥት ሥራዎችን ክፍት ማድረግ ሲያቅተው የኦኤምቢ ዳይሬክተር የትኛዎቹ የመንግሥት ሥራዎች መቆም እንዳለባቸው እና አስፈላጊ የሆኑትን ለመምረጥ ከፕሬዝዳንቱ ጋር ይሠራሉ።

ከፌዴራል መስሪያ ቤቶች የትኛዎቹ ሠራተኞች በፉርሎው ላይ እንደሚቀመጡ መመሪያ ይሰጣል። ይህም ማለት ሠራተኞች ሳይከፈላቸው እረፍት እንዲወጡ የሚደረግበት አሰራር ነው።

በመጀመሪያ ቀን ዋይት ሐውስ 18 ቢሊዮን ዶላር በኒው ዮርክ ለመሠረተ ልማት ፕሮጄክቶች የተያዘን ጨምሮ ለዲሞክራት ግዛቶች የታሰበውን በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ዶላሮችን ለማዘግየት ወይም ለመሰረዝ ተንቀሳቅሷል። ኒው ዮርክ ሴናተር ቻክ ሹመር እና የተወካዮች ምክር ቤት ዲሞክራቲክ መሪ ሃኪም ጄፍሪስ ግዛት ነው።

የመንግሥት መስሪያ ቤቶች እንደገና እንዲከፈቱ ከተፈለገ ሁለቱም ወገኖች አንድ ላይ መሰብሰብ አለባቸው።

ሪፐብሊካኖች ከእነሱ ጋር ውሳኔ ለማሳለፍ የስምንት ዲሞክራት ሴናተሮች ድምጽ ይፈልጋሉ። ዲሞክራቶች ደግሞ 13 ሪፐብሊካኖች ከጎናቸው እንዲቆሙ ይፈልጋሉ። ባለፈው ረቡዕ በሴኔት በተካሄደው የመጨረሻ ያልተሳካ የድምጽ አሰጣጥ ሦስት ዲሞክራቶች ብቻ ከሪፐብሊካኖች ጎን ቆመዋል።

የሕግ አውጭዎች በሴኔቱ በድምጽ ብልጫ ጉዳዩን ለመቋጨት አርብ ከሰአት በኋላ እንደገና ይሰበሰባሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ሪፐብሊካኖች ምንም ነገር ሳይያያዝበት በጀቱን ማሳለፍ ይፈልጋሉ። ዲሞክራቶች በበኩላቸው ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው ግለሰቦች የጤና መድህን ድጎማ እንዲካተት ይፈልጋሉ። ይህ ድጎማ በዓመቱ መጨረሻ ላይ ይጠናቀቃል።

ሐሙስ ዕለት በካፒቶል ሂል በተደረጉ ጋዜጣዊ መግለጫዎች ላይ ሁለቱም ወገኖች ለመግባባት እንደሚችሉ ፍንጭ አልሰጡም።

የምክር ቤቱ አፈ-ጉባዔ ማይክ ጆንሰን ዲሞክራቶችን "ራስ ወዳድ" ከማለት ባለፈ "የዴሞክራሲ መዘጋት" የሚል ስያሜ ሰጥተውታል። የመድን ድጎማዎችን ወይም ሌሎች እርምጃዎችን በመንግሥት የገንዘብ ድጋፍ ላይ ለማካተት እንደማይደራደር ተናግረዋል።

ጄፍሪስ በበኩላቸው ሪፐብሊካኖችን ለሠራተኛው መደብ አሜሪካውያን የጤና መድን ለመስጠት አልፈለጉም ሲሉ ከማለት ባለፈ ትራምፕ ብዙ የፌደራል ሠራተኞችን ለማባረር የሰነዘሩት ዛቻ ትርጉም የለሽ ነው ብለዋል።

የማሪስት ዩኒቨርሲቲ የሕዝብ አስተያየት ኢንስቲትዩት ዳይሬክተር የሆኑት ሊ ሚሪንግፍ በበኩላቸው ከሕዝብ በተሰበሰቡ አስተያየቶች መሠረት አሜሪካውያን ለመስሪያ ቤቶቹ መዘጋት የሚደግፉትን ፓርቲ ወክለው ተከፋፍለዋል ብለዋል።

አስተያየታቸውን የዲሞክራት እና የሪፐብሊካን ደጋፊዎች አብዛኛዎቹ ሌላኛውን ፓርቲ ለመዘጋቱ ተጠያቂ አድርገዋል። 41 በመቶ የሚሆኑት ገለልተኛ አስተያየት ሰጪዎች ደግሞ ሁለቱንም ወገኖች ለጥፋቱ በእኩል ተጠያቂ አድርገዋል።

"ሁለቱም ፓርቲዎች ጣት በመቀሰር የተካኑ ናቸው። አገሪቱ ወደ አልተፈለገም አቅጣጫ እየሄደች ነው ብለው የሚያስቡ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው" ብለዋል ሚሪንግሆፍ።

አሜሪካውያን የመንግሥት መስሪያ ቤቶች እንደገና እንዲከፍቱ በኮንግረሱ ላይ ጫና እንደሚያደርጉ ይጠብቃሉ። ይህ የሚሆነው ግን መዘጋቱ በራሳቸው ሕይወት ላይ የሚያሳድረውን ተጽዕኖ ካዩ በኋላ ነው የሚሆነው።

ፖለቲከኞች ጣት በሚቀሳሰሩበት በዚህ ወቅት የአሜሪካ መንግሥት አገልግሎቶች መቆም የጀመሩ ሲሆን በሺህዎች የሚቆጠሩ የፌደራል ሠራተኞች ቤት ለመቆየት እየተገደዱ ነው።

የኮንግረሱ የበጀት ጽህፈት ቤት (ሲቢኦ) ባወጣው ግምት መሠረት ወደ 750 ሺህ የሚጠጉ የፌደራል ሠራተኞች ያለክፍያ እረፍት ይወስዳሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ክፍያ ባይፈጸምላቸውም "አስፈላጊ" ተብለው የሚታሰቡ የፌደራል ሠራተኞች ሥራቸውን ቀጥለዋል። ይህም ከ200 ሺህ በላይ የሕግ አስከባሪ መኮንኖችን ያጠቃልላል።

የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች እና የትራንስፖርት ደህንነት አስተዳደር (ቲኤስኤ) ሠራተኞች አስፈላጊ እንደሆኑ ይቆጠራሉ።

የመንግሥት መስሪያ ቤቶች ከዚህ ቀደም በተዘጉበት ወቅት እነዚህ ሠራተኞች ታመናል በማለት መደወል በመጀመራቸው በዋና ዋና አውሮፕላን ማረፊያዎች ላይ አንዳንድ መዘግየቶችን አስከትሏል።