ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ከፑሽ አፕ እስከ አሻንጉሊት እንግዶች፡ ከሰሞኑ በኮሮና ምክንያት በአፍሪካ የተስተዋሉ አስደናቂ ክስተቶች
አለማችን በኮሮና ቫይረስ ወርርሽኝ ምክንያት አዲስ አኗኗርን ለመልመድ ትግል በምታደርግበት ወቅት፣ ከሰሞኑ በኮሮና ምክንያት በአፍሪካ የተስተዋሉ ስድስት አስደናቂ ክስተቶችን እናጋራችሁ።
1) የፕሬዚዳንቱ ፑሽ አፕ
ምናልባት በ70ዎቹ እድሜ ለሚገኝ የእድሜ ባለፀጋ ፖለቲከኛ የፑሽ አፕ ውድድር ማድረግ ትንሽ ወጣ ያለ ነገር ነው።
ነገር ግን የጋምቢያው ፕሬዚዳንት አስር ፑሽ አፕ በማድረጋቸው አገሬውን አስደምመዋል፤ ቪዲዮዋቸውንም ብዙዎች አጋርተውታል።
የ71 አመቱ ፕሬዚዳንት ጠንካራ መሆናቸውን ባሳዩበት በዚህ ውድድር ለወደፊቱ ሃያ አምስት እደርሳለሁም ብለዋል።
"የሃያ አምስት አመት ወጣት የሚያደርገውን ማድረግ እችላለሁ" ያሉት ፕሬዚዳንቱ በሌሎች አገሮች ያሉ መሪዎችም ከመቀመጥ ይልቅ የሳቸውን መርህ እንዲከተሉም ጥሪ አቅርበዋል።
በባለፈው ሳምንት በጋምቢያ የሚገኙ ታዋቂ ፖለቲከኞችና ስመጥር ሰዎችም ይህንኑ ውድድር በማድረግ ላይ ናቸው።
በዚህ ውድድርም ላይ ታዋቂው የኮራ ሙዚቀኛ ጃሊባ ኩያቴህ ተሳታፊ ሆኗል።
የጋምቢያው ጋዜጠኛ ኦማር ዋሊ ከተለያየ የህይወት መስመር የተውጣጡ ሰዎችም በዚህ አዝናኝ እንዲሁም ጠንካራ መልእክት በሚተላለፍበት ውድድር እየተሳተፉ ነው።
"ቤት በመቀመጥ የኮሮና ቫይረስን መዛመት እንታገል" የሚሉ መልእክቶችም እየተሰሙ ነው።
ይህ መልእክት የ75አመት እድሜ ባለፀጋውን የኡጋንዳ ፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሴቪኒንም ሳያነሳሳ አልቀረም፤ ቤታቸውም ሆነው አካላዊ እንቅስቃሴ ሲያደርጉም ታይተዋል።
ውጭ ላይ የሚደረጉ ማንኛውም ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች በኡጋንዳ ክልከላ ተጥሎባቸዋል።
2) ልጇን ማየት ያልቻለችው፣ በለይቶ ማቆያ የወለደችው የኮሮና ታማሚ
የ19 አመቷ ካሜሮናዊት የኮሮና ታማሚ ልጇን የወለደችው በለይቶ ማቆያ ውስጥ ነው፤ እስካሁንም ልጇን ማየት አልቻለችም።
ህፃኗን ስትገላገል በከፍተኛ ጥንቃቄ ሲሆን፤ ልጇም ቫይረሱ እንዳይዛት በሚል ዶክተሮች ህፃኗን በፍጥነት ወደሌላ ክፍል ይዘዋት ሄደዋል።
ምንም እንኳን ዶክተሮች የህፃንቷን ደህንነት በተደጋጋሚ ቢያረጋግጡላትም፤ የመጀመሪያ ልጇን በዚህ ሁኔታ የተገላገለችው እናት እንደተረበሸች ነው። "በጣም የብቸኝነት ስሜት ተሰማኝ። እያለቀስኩ ነበር። ዶክተሮቹ ከፍተኝ ድጋፍ አድርገውልኛል፤ ሁሉም ደህና እንሚሆንም ሲነግሩኝ ነበር" ብላለች።
እናትና ልጅ በሙሉ ጤንነት ላይ እንደሚገኙ የተገለፀ ሲሆን ያውንዴ በሚገኝ አንድ ሆስፒታልም በተለያየ ክፍል ውስጥ ይገኛሉ።
ህፃን ፎራያ የተወለደችው ጊዜዋ ከመድረሱ በፊት ሲሆን በወቅቱም 2.1 ኪሎ ግራም የምትመዝን ስትሆን የኮሮና ምንም አይነት ምልክት የለባትም ተብሏል። እናቷም ከአስር ቀናት በኋላ ቫይረሱ በደሟ መኖር አለመኖሩ ይረጋገጣል።
3) እንቅስቃሴን የሚያነበውና በፀሃይ ብርሃን የሚሰራው የእጅ መታጠቢያ
በኡጋንዳ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች አማካኝነት የተፈጠረው የእጅ መታጠቢያ በመላው ካምፓስ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል።
በአካባቢው እንቅስቃሴ ሲኖር ማንበብ የሚችለው መሳሪያ በፀሃይ ብርሃን የሚሰራ ሲሆን ተማሪዎቹ የሰሩት በ900 ብር ብቻ ነው።
ዝቅተኛ አቅም ያላቸውንም የማህበረሰቡ አካላትን ግንዛቤ ውስጥ በማድረግ የተሰራ ነው።
"በየትኛውም ጄሪካን፣ በርሜል ወይንም የትኛውንም የውሃ ማጠራቀሚያ ውስጥ መግጠም ይችላሉ" በማለት በዩኒቨርስቲው መምህር የሆኑት ኡማር ያህያ ተናግረዋል።
ቴክኖሎጂን በመጠቀም ንክኪን የሚያስቀር ሲሆን፤ የውሃ እጥረትም ባለበትም አካባቢ እጅን በቀላሉ ማፅዳት ይቻላል ተብሏል።
4) ሰርግን ለመታደም የተገኙት የአሻንጉሊት እንግዶች
በሰው ምስል የተቀረፁና ከካርቶን የተሰሩ አሻንጉሊቶች በደቡብ አፍሪካ ሰርግን ለመታደም ተገኝዋል። በኮሮና ቫይረስ ምክንያት የቤት መቀመጥን አስገዳጅ ውሳኔ ባሳለፈችው ደቡብ አፍሪካ ሰርጋቸውን ማከናወን ያልቻሉት ሙሽሮች አሻንጉሊቶችን በመሰብሰብ የቀልፈድ ሰርግ አከናውነዋል።
ህዝባዊ ስብሰባዎችም ሆነ ማንኛውም እንቅስቃሴ የተገደበ ሲሆን፣ የአልኮል መጠጥና ሲጋራም መግዛት ክልክል ነው።
ባለፈው ሳምንት ይህንን ህግ ጥሰው የተጋቡ ሙሽሮች ከእንግዶቻቸው ጋር ዘብጥያ ወርደዋል።
ነገር ግን የፊልም ባለሙያ የሆነው ዳን ማሴ እጮኛው ጋብርኤል ኤስተርሁዘንንን ለማስደሰት በሚል የሰርጉን ዝግጅት አከናውኗል።
የቀልድ ሰርግ ስነስርአቱንም በቪዲዮ አጋርተዋል።
5) መብራት፣ ውሃና ትራንስፖርት ነፃ የሆነባት አገር
በኮሮና ቫይረስ ምክንያት የመብራት አገልግሎት፣ የህዝብ ትራንስፖርትና ውሃ በነፃ እንዲሆን ጊኒ ውሳኔ አስተላልፋለች።
ጠቅላይ ሚኒስትር ኢብራሂማ ካሶሪ ፎፋና በዚህ ሳምንት እንዳሳወቁት እነዚህን አገልግሎት ለመስጠት መንግሥት 264 ሚሊዮን ዶላር በጀት መድቧል።
እነዚህ እርምጃዎች አገሪቷ ኮሮና ቫይረስ ሊያስከትል የሚችለውን የጤና ቀውስ እልባት ለመስጠትና በተለይም በማህበረሰቡ ላይ የሚያመጣውን ኢኮኖሚያዊ ጫና ለመቀነስ ነው ተብሏል።
ከአራት አመታት በፊት ከኢቦላ ጋር የታገለችው ጊኒ መድኃኒቶችም ሆነ መሰረታዊ ቁሳቁሶች ዋጋ እንዳይጨመርባቸው እገዳ ጥላለች።
ሆቴሎችም ሆነ ከቱሪዝም ጋር የተገናኘ ቢዝነስ ያላቸውም ለሶስት ወራት ግብር እንዳይከፍሉ ተደርገዋል።
በመንገግሥትም ሆነ በግሉ ለተከራዩትም ፣ የቤት ኪራይም ለዘጠኝ ወራት ያህል የዋጋ መቀነስ ተደርጓል።
6) የግጥም ምሽት
በአህጉሪቷ የሚገኙ አስራ ሶስት ገጣሚዎች ተሰባስበው የናይጀሪያውን ፀሐፊ ክርስቶፎር ኦኪጎ ግጥሞች አንብበዋል። ግጥሞቹ በ1960ዎቹ የተፃፉ ሲሆን በዚህ ወቅት ብዙዎች እንዲያውቁት ለማድረግ ያለመ ነው ብለዋል።
ፕሮጀክቱን የጠነሰሰችው ናይጀሪያዊቷ ፀሐፊ ሎላ ሾነይን ወጣት ፀሓፊያንን ስራዎቹን ለማስተዋወቅ እንዲሁም አህጉሪቷ ያፈራቻቸውን ስመ ጥር ፀሃፍት ስራዎችም እንዲያነቡ ለማበረታታት ነው ብላለች።
የፀሃፊው ስራዎች ተስፋን የሚፈነጥቁ እንዲሁም የአሁንን ሁኔታ ማንፀባረቅ የሚችሉ እንዲሁም የሰው ልጅ የሚሰማውን ስሜት ውብ በሆኑ ቃላት መግለፅ የሚችሉ እንደሆኑም አስረድታለች።