የወለጋ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ወደቤታቸው ሊመልስ ነው

የፎቶው ባለመብት, የወለጋ ዩኒቨርሲቲ የፌስቡክ ገጽ
የወለጋ ዩኒቨርሲቲ እስከ ረቡዕ ታህሳስ 22 2012 ዓ.ም. ድረስ ትምህርት የማይጀመር ከሆነ ተማሪዎች ወደቤታቸው እንዲሄዱ ሴኔቱ መወሰኑን አስታወቀ።
ዩኒቨርሲቲው ዛሬ ታህሳስ 20/2012 ዓ.ም. ያወጣው መግለጫ ላለፉት አራት ሳምንታት ተቋርጦ የነበረውን ትምህርት ለማስጀመር በተደጋጋሚ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አድርጓል ይላል።
ሆኖም እስከ ታህሳስ 20/2012 ዓ.ም. ድረስ ትምህርት መጀመር አለመቻሉንና መሻሻሎች አለመታየታቸውን ማረጋገጥ ችለናል ይላል መግለጫው። በዚህም ምክንያት በሴሚስተሩና በአጠቃላይ በዓመቱ የትምህርት መርሀ ግብር ላይ ጫና ማሳደሩን ዩኒቨርሲቲው ገልጿል።
በመሆኑም እስከ ረቡዕ ታህሳስ 22 2012 ዓ.ም. ድረስ ትምህርት የማይጀመር ከሆነ ተማሪዎች የክሊራንስ ቅጽ በመሙላትና የሚመለከታቸው የቢሮ ሀላፊዎችን በማስፈረም እንዲሁም በእጃቸው የሚገኙ የዩኒቨርሲቲው ንብረቶችን በመመለስ የሚጠበቅባቸውን አሟልተው ግቢውን ለቅቀው እንዲወጡ ሲል የወለጋ ዩኒቨርሲቲ ለተማሪዎቹ መልእክቱን አስተላልፏል።
አክሎም ትምህርት እየተከታተሉ ካሉ ተማሪዎች ውጪ ማንኛውም ዩኒቨርሲቲው የሚሰጠውን አገልግሎቶች እንደሚያቋርጥ ገልጿል። የመልሶ ቅበላ ጊዜ ደግሞ በተለያዩ የመገናኛ ብዙሀን ወደፊት እንደአስፈላጊነቱ እንደሚገልጽ ዩኒቨርሲቲው አስታውቋል።
የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ሀሰን የሱፍ (ፒኤችዲ) ለቢቢሲ እንደተናገሩት ተማሪዎች እስከ ረቡዕ ድረስ ወደ ትምህርት ገበታቸው ለመመለስ ፈቃደኛ ከሆኑ የመማር ማስተማሩ ሂደት ይቀጥላል።
ነገር ግን ተማሪዎች የደህንነት ስጋት አለብን ወደቤታችን መሄድ እንፈልጋለን ካሉ በመመሪያው መሰረት ወደቤታቸው መሄድ ይችላሉ።
'' አሁን ባለው ሁኔታ ከበድ ያለ የጸጥታ ችግር የለም፤ ስለዚህ ተማሪዎች ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ ነበር ጥረት ስናደርግ የነበረው። ነገር ግን ተማሪዎቹ በመቆየታቸው ደስተኞች ስላልሆኑ ሴኔቱ ይህንን አማራጭ አቅርቧል'' ብለዋል።
ባለፈው ቅዳሜ የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ አንድ ተማሪ መገደሉን ተከትሎ ባጋጠመ አለመረጋጋት ምክንያት ተማሪዎች ወደቤታቸው እንዲመለሱ ውሳኔ ማስተላለፉ ይታወሳል።
የዩኒቨርሲቲው ምክትል ፕሬዝዳንት ረዳት ፕሮፌሰር አባያ ደገፋ የመማር ማስተማር ሂደቱን ለማቆም ያደረሳቸውን ምክንያት ለቢቢሲ ሲያስረዱ የዩኒቨርሲቲው ሴኔት የተማሪዎችን ህይወት ከአደጋ ለማጠበቅ ሲል ወደቤት ለመላክ ወስኗል ብለው ነበር።












