አንድ የሩሲያ ወታደራዊ ቤተ-ክርስቲያን የፑቲንን 'ሞዛይክ' ሊያፈርስ ነው

ፕሬዝደንት ፑቲን

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

ታትሟል

ሩሲያ ውስጥ የሚገኝ አንድ ወታደራዊ ቤተ-ክርስቲያን ለፕሬዝደንት ቭላድሚር ፑቲን የቀረፀውን የግድግዳ ላይ ምስል [ሞዛይክ] ፕሬዝደንቱ በመቃወማቸው ምክንያት መሰረዙን አስታውቋል።

አጨቃጫቂው ምስል ፕሬዝደንት ፑቲን፣ የመከላከያ ሚኒስትሩ እንዲሁም የፀጥታ ኃላፊውና ሌሎች የሚታዩበት ነው።

ሞስኮ አቅራቢያ የሚገኘው የግዙፉ ቤተ-ክርስቲያን ጳጳስ የግድግዳ ላይ ምስሉ [ሞዛይኩ] በቅርቡ ሊነሳ እንደሚችል አስታውቀዋል።

ሌላኛው ሊፈርስ ይችላል የተባለው ሞዛይክ አንዲት ሴት 'ክሪሚያ የእኛ ናት' የሚል መዝሙር ስታቀነቅን ያሳያል።

ሩሲያ በ2014 [እ.አ.አ.] የክሪሚያ ባሕረ-ሰላጤን ከዩክሬን መነጠሏ አይዘነጋም።

የፑቲን ሞዛይክ ምስል የተሰቀለበት ቤተ-ክርስቲያን ከ75 ዓመታት በፊት ሶቪየት ሕብረት ሁለተኛው የዓለም ጦርነትን በድል ከተወጣች በኋላ የተገነባ ነው።

የቤተ-እምነቱ መግቢያ ከናዚ ወታደሮች በተነጠቁ ዕቃዎች የተሠራ ነው። ነገር ግን የፕሬዝደንት ፑቲን ምስል ግድግዳ ላይ መሳሉ አጨቃጫቂ ሆኖ ነበር። ጉዳዩ አጨቃጫቂ ሆኖ ሲገኝ ክሬምሊን [የሩስያ ቤተ-መንግሥት] ምስሉን ፑቲን አላፀደቁትም የሚል መግለጫ አውጥቷል።

የቤተ-መንግሥቱ ቃል-አቀባይ ጉዳዩ ተቀባይነት የለውም ሲሉ ተደምጠዋል። አልፎም ምስሉ ወዲያው እንደሚነሳ አሳውቀዋል።

ቃል-አቀባዩ አንድ አዲስ ቤተ-ክርስቲያን ላይ የሚታየው የጆሴፍ ስታሊን ምስል ስለመነሳት አለመነሳቱ ያሉት የለም።

የጆሴፍ ስታሊን ምስል የሚታይበት አዲሱ ቤተ-ክርስቲያን በያዝነው ወር ይመረቃል ተብሎ የነበረ ቢሆንም በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ሊራዘም ይችላል ተብሏል።