የቀድሞው የኬንያ ፕሬዚዳንት ዳንኤል አራፕሞይ በ95 ዓመታቸው አገግመው ከሆስፒታል ወጡ

የፎቶው ባለመብት, AFP
ታትሟል
የቀድሞው የኬንያ ፕሬዚዳንት ዳንኤል አራፕ ሞይ ከአስር ቀናት የሆስፒታል ቆይታ በኋላ ተሽሏቸው እንደወጡ አንድ ቃል አቀባይ ለቢቢሲ ገልጿል።
ህመማቸው ምን እንደሆነ እስካሁን የታወቀ ነገር የለም።
የዘጠና አምስቱ አዛውንት ከህመማቸው አገግመው ወደ ቤታቸው እንደገቡም ቃል አቀባዩ በተጨማሪ ገልጿል።
ኬንያን በፕሬዚዳንትነት በማገልገል ለረዥም ዓመታት፣ ሃያ አራት አመታት በሥልጣን ላይ በመቆየት የሚወዳደራቸው አልተገኘም።
በሥልጣን ላይ በነበሩበትም ወቅት ሃገሪቷን እንደ ሰም አቅልጠው ገዝተዋል የሚባሉት ዳንኤል አራፕሞይ፤ በሰብዓዊ መብት ጥሰቶች የሚተቿቸው አሉ።
በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ግፊት ነው እንደ ጎርጎሳውያኑ 1992 ሌሎች ፓርቲዎች ወደ ምርጫው መድረክ እንዲመጡ የፈቀዱት፤ ቢሆንም ግን ምርጫው ከፍተኛ ግጭቶች የበዙበትና ማጭበርበርም ነበረበት ተብሏል።
በዚሁ ዓመትም ፍርድ ቤት በሕገወጥ መንገድ መሬቷን ተቀራምተዋል በሚልም ለአንዲት ሴት 10.5 ሚሊዮን ዶላር እንዲከፍሉም ቅጣት ጥሎባቸዋል።












