ቀጥታ, የአሜሪካ እና የኢራን የመጀመሪያ ዙር ድርድር ‘አበረታች ውጤት’ አሳይቶ መገባደዱ ተገለጸ

የአሜሪካ እና የኢራን የመጀመሪያ ዙር ድርድር “አበረታች ውጤት” እንዳሳየ አሸማጋዮቹ ኳታር እና ፓኪስታን አስታወቁ። ኳታር እና ፓኪስታን ዛሬ በጋራ ባወጡት መግለጫ “ከፍተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ኮሚቴ በ60 ቀናት ውስጥ የመጨረሻ ስምምነት ላይ ለመድረስ የሚያስችል ፍኖተ ካርታ ላይ ተስማምቷል” ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የአሜሪካ እና ኢራን ንግግር ውጤት እያስገኘ መሆኑን ምክትል ፕሬዝዳንት ቫንስ ገለጹ

    አሜሪካው ምክትል ፕሬዝዳንት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ እና ኢራን ስዊትዘርላንድ ውስጥ እየካሄዱት ባለው ንግግር “መልካም ውጤቶች መገኘታቸውን” እና የተሳካ የመጨረሻ ስምምነት ላይ ለመድረስ “ጥሩ መሠረት መጣሉን” የአሜሪካው ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ ተናገሩ።

    ንግግሩ ከተጀመረ በኋላ የኢራን ልዑካን ረግጠው ለመውጣት ቢዝቱም በሁለቱ አገራት ተወካዮች መካከል የሚካሄደው ድርድር ለረጅም ሰዓታት ቀጥሎ ነው አዎንታዊ ደረጃ ላይ መድረሱ የተነገረው።

    የዓለም አቀፉ አቶሚክ ኤነርጂ የኒውክሌር ተቆጣጣሪዎች ተመልሰው ወደ ኢራን በመግባት በመጀመሪያ ደረጃው ንግግር ስምምነት የተደረሰባቸውን ነጥቦች ማክበሯን ያረጋግጣሉ ተብሏል።

    በአሜሪካም በበኩሏ ኢራን የተለያዩ የእህል ምርቶችን ከውጭ ለመግዛት እንድትችል ለማድረግ ሲባል የታገደባት ሀብት እንዲንቀሰቀስ ትፈቅዳለች።

    ወሳኙ የባሕር ላይ መተላለፊያ ሆርሙዝ ወሽመጥ “ክፍት ነው” ያሉት የአሜሪካው ምክትል ፕሬዝዳንት፣ በሊባኖስ የሚካሄደውን ጦርነት በተመለከተም ተገቢው ቅንጅት እና ቴክኒካዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ንግግር ማድረግ እንደሚቀጥል አመልክተዋል።

  2. የመጀመሪያው ቀን ድርድር ሲጠናቀቅ፤ በቀጣይ ቀናት የቴክኒክ ውይይት እንደሚቀጥል ተገለጸ

    የኢራን ልዑካን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን እና አሜሪካ የመጀመሪያ ቀን ድርድር የተገባደደ ሲሆን፤ ሳምንቱን በሙሉ በስዊትዘርላንድ የቴክኒክ ጉዳዮች ውይይት እንደሚቀጥል ተገልጿል።

    አደራዳሪዎቹ ኳታር እና ፓኪስታን “የኢስላማባድ የመግባቢያ ሰነድ ማዕቀፍን በተመለከተ የመጀመሪያው ዙር ንግግር ተገባዷል” ብለዋል።

    በተቀረው የሳምንቱ ቀናት የቴክኒክ ውይይት እንደሚቀጥልም አስታውቀዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን በቀጣይ 60 ቀናት ውስጥ የመጨረሻ ስምምነት ላይ ለመድረስ የሚያስችል ፍኖተ ካርታ ላይ መስማማታቸው ተመልክቷል።

    በሊባኖስ ጦርነቱን ማስቆም የሚቻልበት መንገድ መዘርጋት ላይም መግባባት ላይ መደረሱን አሸማጋዮቹ አስታውቀዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ድርድሩን “ትልቅ ለውጥ” የታየበት እንደሆነ በኤክስ ገጻቸው ተናግረዋል።

    “በነዳጅ እና በፔትሮኬሚካል የወጪ ንግድ ላይ የተጣለው እገዳተነስቷል” ሲሉም አክለዋል።

    የኢራን እና አሜሪካ የመጀመሪያ ቀን ድርድር

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

  3. በኢራን እና አሜሪካ የመጀመሪያ ቀን ድርድር ምን ጉዳዮች ተነሱ?

    ሉስርኔ በተባለ ሐይቅ የተካሄደው ድርድር አወንታዊ እና ገንቢ ድባብ እንደታየበት ተገልጿል

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ሉስርኔ በተባለ ሐይቅ የተካሄደው ድርድር አወንታዊ እና ገንቢ ድባብ እንደታየበት ተገልጿል

    አሸማጋዮቹ ኳታር እና ፓኪስታን በጋራ ባወጡት መግለጫ የድርድር ሒደቱን የሚከታተል የፖለቲካ ኮሚቴ እና በሊባኖስ ጦርነት የሚያስቆም ቡድን መመሥረቱን አስታውቀዋል።

    “ከፍተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ኮሚቴ በ60 ቀናት ውስጥ የመጨረሻ ስምምነት ላይ ለመድረስ የሚያስችል ፍኖተ ካርታ ላይ ተስማምቷል” ብለዋል።

    የአሜሪካ እና ኢራን ድርድር በስዊትዘርላንድ የተካሄደ ሲሆን፤ ኳታር እና ፓኪስታን በጋራ ባወጡት መግለጫ የመጀመሪያውን ቀን ድርድር ነጥቦችን እንደሚከተለው ዘርዝረዋል፦

    • ሉስርኔ በተባለ ሐይቅ የተካሄደው ድርድር አወንታዊ እና ገንቢ ድባብ እንደታየበት ተገልጿል።
    • ከፍተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ኮሚቴ ድርድሩን በዋናነት የሚከታተል ይሆናል።
    • ዋነኛ ተደራዳሪዎች የደረሱበትን ለኮሚቴው ያስታውቃሉ።
    • ኮሚቴው ግጭትን ለማስቆም ከተቋቋመው ቡድን ጋር በመሆን የኒውክሌር፣ የማዕቀብ እና የመግባቢያ ሰነዱ አተገባበርን ይከታተላል።
    • በስምምነቱ አንቀጽ 5 መሠረት የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት እንዲሁም በተደራዳሪዎች መካከል አለመግባባት እንዳይኖር የንግግር መስመር ክፍት ይሆናል።
    • ግጭትን ለማስቆም የተቋቋመው ቡድን በሊባኖስ ድርድር እንዲደረግ እና ወታደራዊ ግጭት እንዲቆም ያደርጋል።
  4. ኢራን የነዳጅ ማዕቀብ እንደተነሳላት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ገለጹ

    ድርድር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ “በነዳጅ እና በፔትሮኬሚካል የወጪ ንግድ ላይ የተጣለው እገዳ መነሳቱን” ገለጹ።

    ከድፍድፍ ነዳጅ እና ከተፈጥሮ ጋዝ የሚገኘው ፔትሮኬሚካል የወጪ ንግድ ላይ የተጣለው ማዕቀብ ከመነሳቱ በተጨማሪ በኢራን የባሕር መተላለፊያ ላይ ተጥሎ የነበረው ክልከላ መነሳቱንም አክለዋል።

    በተጨማሪም ማዕቀብ ተጥሎባቸው የነበሩ “የተወሰኑ የኢራን ሃብቶች እንደተለቀቁ” ተናግረዋል።

    የማዕቀቦች መነሳት የኢራንን የምጣኔ ሃብት መልሶ ግንባታ እንደሚደግፍ በኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት አስታውቀዋል።

    “በሊባኖስ ያለው ጦርነት እንዲቆም” የኳታር እና ፓኪስታን ልዑካን ላበረከቱት አስተዋጽኦም አመስግነዋል።

    ኢራን እና አሜሪካ የተስማሙበት መግባቢያ ሰነድ አንቀጽ 1፣ 10 እና 11 ለድርድሩ ዋነኛ መነሻ መሆናቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጠቁመዋል።

    አንቀጽ 1- አሜሪካ፣ ኢራን እና አጋሮቻቸው ሊባኖስን ጨምሮ በሁሉም ግንባሮች “በአፋጣኝ እና በዘላቂነት” ተኩስ ማቆም አለባቸው ይላል።

    አንቀጽ 10- ዋሽንግተን ለነዳጅ ኤክስፖርት እና ለፔትሮሊየም ምርቶች አስፈላጊውን ፈቃድ እንድትሰጥ እና ባንክ እና መጓጓዣን ጨምሮ በሌሎችም ዘርፎች ውሳኔው እንደሚተገበር ይገልጻል።

    አንቀጽ 11- ማዕቀብ የተጣለባቸውን የኢራን ሃብቶች ይመለከታል።

  5. የአሜሪካ እና የኢራን የመጀመሪያ ዙር ድርድር ‘አበረታች ውጤት’ እንዳሳየ ተገለጸ

    የአሜሪካ ልዑካን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካ እና የኢራን የመጀመሪያ ዙር ድርድር “አበረታች ውጤት” እንዳሳየ አሸማጋዮቹ ኳታር እና ፓኪስታን አስታወቁ።

    ድርድሩ ትናንት እሑድ በስዊትዘርላንድ ተጀምሯል። ሁለቱ አገራት ከስምምነት ላይ የደረሱት ባለፈው ሳምንት እንደነበር ይታወሳል።

    ኳታር እና ፓኪስታን ዛሬ ሰኞ በጋራ ባወጡት መግለጫ “ከፍተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ኮሚቴ በ60 ቀናት ውስጥ የመጨረሻ ስምምነት ላይ ለመድረስ የሚያስችል ፍኖተ ካርታ ላይ ተስማምቷል” ብለዋል።

    በያዝነው ሳምንት የቴክኒክ ጉዳዮችን በተመለከተ ውይይት እንደሚቀጥል በመግለጫው ተመልክቷል።

    በድርድሩ ተሳታፊ የሆኑ የአሜሪካ ዲፕሎማት እንደተናገሩት ውይይቱ “ከኢራን የወጡ አወዛጋቢ መልዕክቶችን ማጥራት ላይ ያተኮረ ነው”።

    በተጨማሪም በሊባኖስ የተኩስ አቁም ስምምነትን ማስተግበር እና የሆርሙዝ ወሽመጥን ማስከፈት የውይይቱ ግቦች መሆናቸውን ገልጸዋል።

    ተደራዳሪዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters