የአሜሪካ እና ኢራን ንግግር ውጤት እያስገኘ መሆኑን ምክትል ፕሬዝዳንት ቫንስ ገለጹ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
አሜሪካ እና ኢራን ስዊትዘርላንድ ውስጥ እየካሄዱት ባለው ንግግር “መልካም ውጤቶች መገኘታቸውን” እና የተሳካ የመጨረሻ ስምምነት ላይ ለመድረስ “ጥሩ መሠረት መጣሉን” የአሜሪካው ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ ተናገሩ።
ንግግሩ ከተጀመረ በኋላ የኢራን ልዑካን ረግጠው ለመውጣት ቢዝቱም በሁለቱ አገራት ተወካዮች መካከል የሚካሄደው ድርድር ለረጅም ሰዓታት ቀጥሎ ነው አዎንታዊ ደረጃ ላይ መድረሱ የተነገረው።
የዓለም አቀፉ አቶሚክ ኤነርጂ የኒውክሌር ተቆጣጣሪዎች ተመልሰው ወደ ኢራን በመግባት በመጀመሪያ ደረጃው ንግግር ስምምነት የተደረሰባቸውን ነጥቦች ማክበሯን ያረጋግጣሉ ተብሏል።
በአሜሪካም በበኩሏ ኢራን የተለያዩ የእህል ምርቶችን ከውጭ ለመግዛት እንድትችል ለማድረግ ሲባል የታገደባት ሀብት እንዲንቀሰቀስ ትፈቅዳለች።
ወሳኙ የባሕር ላይ መተላለፊያ ሆርሙዝ ወሽመጥ “ክፍት ነው” ያሉት የአሜሪካው ምክትል ፕሬዝዳንት፣ በሊባኖስ የሚካሄደውን ጦርነት በተመለከተም ተገቢው ቅንጅት እና ቴክኒካዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ንግግር ማድረግ እንደሚቀጥል አመልክተዋል።






