የናይጀሪያ ጦር ጂሃዲስት ቡድኖችን ይረዳል ያለውን ግብረ ሰናይ ድርጅት ዘጋ

የፎቶው ባለመብት, AFP
የናይጀሪያ ጦር በአገሪቷ ሰሜን ምሥራቅ አካባቢ የሚገኙትን የቦኮሃራም ታጣቂዎች ይረዳል ያለውን ዓለም አቀፍ ግብረ ሰናይ ድርጅት መዝጋቱ ተሰማ።
'አክሽን አጌንስት ሃንገር' የተባለው ግብረ ሰናይ ድርጅት ለታጣቂዎቹ ምግብ እና መድሃኒቶችን ሲያቀርብ ቆይቷል ተብሏል።
ድርጅቱ የቀረበበትን ክስ የተቃወመ ሲሆን፤ ባሳለፍነው ሀሙስ የናይጀሪያ ጦር ቢሯቸው ድርስ በመሄድ በሰሜይ ምሥራቅ ቦርኖ ግዛት፤ ማይዱግሪ የሚገኘውን ቢሯቸውን እንደዘጉት ተናግረዋል።
"ውሳኔው በግዛቱ ለምግብ እጦት ለተጋለጡ ሰዎች የሚደረገውን ድጋፍ አደጋ ላይ የጣለ ነው፤ ድርጅቱ በማይዱግሪ፣ ሞንጉኖ እና ዳማሳክ ለሚገኙ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች የምግብ ድጋፍ ያደርጋል" ሲሉ በመግለጫቸው ውንጀላውን ተቃውመዋል።
የአንድ ግብረ ሰናይ ድርጅትን ስም በግልፅ በመጥቀስ የሽብር ቡድን ለመደገፍ በሚያደርገው ብልሹ አሠራርና የደህንነት ጥሰት ሲወነጀል ይህ የመጀመሪያው ነው።
ግብረ ሰናይ ድርጅቱ ሽብርተኞችንና የጭካኔ ድርጊታቸውን መደገፍ እንዲያቆም በተለያየ ጊዜ ማስጠንቀቂያ ቢሰጠውም በፅናት መቆየቱን በመግለጫቸው አክለዋል።
ጦሩ በበኩሉ ለውንጀላው ተጨባጭ የደህንነት ማስረጃ እንዳለው አስረድቷል።
የቦኮሃራም ታጣቂዎች በሰሜን ምሥራቅ ናይጀሪያ፣ እንዲሁም በጎረቤት አገሮች ቻድ፣ ኒጀር እና ካሜሩን ከ10 ዓመታት በላይ ድንገተኛ ጥቃቶችን ሲፈፅሙ ቆይተዋል።
በግጭቱ ምክንያትም በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ ሰላማዊ ዜጎች የተገደሉ ሲሆን፤ ከሁለት ሚሊየን የሚበልጡ ሰዎች ቀያቸውን ጥለው ወጥተዋል።
ታጣቂ ቡድኑ በርካታ ተማሪዎችን ከትምህርት ቤት በመጥለፍ፤ በተለይ ከአምስት ዓመታት በፊት ከ200 በላይ የሚሆኑ ሴት ተማሪዎችን ከቦርኖ፤ ችቦክ ጠልፈው ከወሰዱና ካገቱ በኋላ የዓለምን ሚዲያ ትኩረት ስበዋል።
ግዛቱ ታጣቂ ቡድኑ በንቃት የሚንቀሳቀሱበት አካባቢ እንደሆነም ተጠቅሷል።














