ሆንዱራስ፡ በእርዳታ ገንዘብ ጌጣጌጥ የገዙት የቀድሞዋ እመቤት የ58 ዓመት እስር ተፈረደባቸው

የቀድሞዋ ቀዳማዊት እመቤት ሮሳ ኢሌና ቦኒላ

የፎቶው ባለመብት, Reuters

የምስሉ መግለጫ, የቀድሞዋ ቀዳማዊት እመቤት ሮሳ ኢሌና ጥፋተኛ አይደለሁም በማለት ይግባኝ እንደሚሉ ተናግረዋል።
ታትሟል

በመካከለኛው አሜሪካ የምትገኘው አገር ሆንዱራስ፤ የቀድሞ ቀዳማዊት እመቤት ሮሳ ኢሌና ቦኒላ 58 ዓመታትን በእስር እንዲያሳልፉ ውሳኔ ተላልፎባቸዋል።

የ52 ዓመቷ ሮሳ ጥፋተኛ የተባሉት ባለቤታቸው ፖርፊሪዮ ሎቦ ለአራት ዓመታት በሥልጣን ላይ በቆዩበት ጊዜ ከዓለም አቀፍ ድርጅቶችና ከሕዝብ ለእርዳታ የተሰበሰበ 779 ሺህ ዶላር ያለአግባብ ተጠቅመዋል ተብለው ነው።

የቀድሞዋ ቀዳማዊት እመቤት ገንዘቡን ለጌጣጌጥ መግዣ፣ ለሕክምና ክፍያ እና ለልጆቿ የትምህርት ቤት ክፍያ እንዳዋለችው አቃቤ ሕግ አስታውቋል።

የግለሰቧ ጠበቃ በበኩላቸው "ጥፋተኛ እይደሉም" ሲሉ የተከራከሩ ሲሆን የተላለፈባቸው ውሳኔ በድጋሜ እንዲታይ ይግባኝ እንደሚሉ ተናግረዋል።

ሮሳ ከሕዝብ የተሰበሰበው እና በአገሪቷ ለሚገኙ ችግረኛ ልጆች ጫማ ለመግዛት የተመደበ ገንዘብ መጥፋቱን ተከትሎ ነበር ባሳለፍነው ዓመት የካቲት ወር ላይ ለእስር የተዳረጉት።

የግለሰቧ የግል ረዳት ሳኡል እስኮባርም በማጭበርበር ወንጀል 48 ዓመታት እስር ተበይኖባቸዋል። ውሳኔው ሲተላለፍ ቀዳማዊት እመቤቷም ሆኑ ባለቤታቸው ፍርድ ቤት እንዳልተገኙ ተገልጿል።

የአገሪቷ መሪ የነበሩት ሎቦ ቤተሰቦች ለእስራት ሲዳረጉ ይህ የመጀመሪያ ጊዜ አይደለም።

ከሁለት ዓመታት በፊት ታላቅ ልጃቸው ፋቢዎ፤ የኮኬይን እፅ ወደ አሜሪካ ለማስገባት አሲሯል በሚል 24 ዓመታትን በእስር እንዲያሳልፍ ተበይኖበታል።