አንድ ህፃንን ውሻ ቤት ውስጥ የቆለፈች ናይጄሪያዊት ተያዘች

የፎቶው ባለመብት, @opetodolapo
ታትሟል
የናይጀሪያ ፖሊስ በአንድ ህፃን ላይ ጥቃት የፈፀመችና በውሻ ቤት ውስጥ አስገብታ የቆለፈችበትን ሴት በቁጥጥር ሥር አዋለ።
ግለሰቧ ድርጊቱን ስትፈፅም የሚያሳው ተንቀሳቃሽ ምስል እንዴት እንደተቀረፀ ግልፅ ባይሆንም በዚህ ወር መጀመሪያ አካባቢ የትዊተር ገፅ ተጠቃሚዎችን ያነጋገረ ነበር።
ተንቀሳቃሽ ምስሉ በማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች ዘንድ ቁጣን ቀስቅሷል። በድርጊቱ የተደናገጡትም ግለሰቧን ተከታትሎ ለያዘ ሽልማት እንደሚሰጡ አስታውቀው ነበር።
ታዲያ ባለፈው ሐሙስ የናይጀሪያ ፖሊስ ቃል አቀባይ ዶላፖ ባድሞስ ግለሰቧ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር መዋሏን በትዊተር ገፃቸው አስታወቁ።
"ተጠርጣሪዋ ግለሰብ በእስር ላይ የምትገኝ ሲሆን ክስ ይመሰረትባታል፤ አሳዳጊውን ያጣው ህፃንም ከአደጋው ተርፎ በሌጎስ የመንግሥት መጠለያ ይገኛል" ሲሉም ቃል አቀባይዋ ገልፀዋል።
በትዊተር ገፃቸው ላይ ካሰፈሩት ፅሁፍ ሥርም በፖሊስ የተቀረፀውንና ህፃኑ ተቆልፎበት የነበረውን የውሻ ቤት የሚያሳይ ተንቀሳቃሽ ምስል አያይዘዋል።













