
የፎቶው ባለመብት, EPA
ጋዛ ውስጥ ታግተው ከነበሩት አንዷ ዮቼቭድ ሊቭሺትዝ አጋቾቻቸው "በቁርዓን እናምናለን" አንጎዳችሁም እንዳሏቸው ተናገሩ።
በትናንትናው ምሽት የተለቀቁት የ85 ዓመቷ የዕድሜ ባለጸጋ በሞተር ሳይክል በማይመች ሁኔታም እንደተወሰዱና መተንፈስም ተቸግረው እንደነበር ገልጸዋል።
በሐማስ ታጋቾች ሲወሰዱም
ጌጣጌጦች እና ሰዓታቸው እንደተወሰደባቸው እንዲሁም መመታታቸውንም የገለጹት የዕድሜ ባለጸጋዋ “ሲዖል ውስጥ ነበርኩ” ብለዋል።
ከሞተር ብስክሌቱ ከወረዱ በኋላ ሰላምታ የሰጧቸው ሰዎች " በቁርዓን እናምናለን" ሲሉም ጉዳት እንደማያደርሱባቸው ነግረውኛል ብለዋል።
እሳቸው እና ሌሎች 24 ሰዎች ወደ ዋሻዎች መወሰዳቸውን በአስተርጓሚ ልጃቸው በኩል ተናግረዋል።
የዋሻዎቹ መተላለፊያዎች "እርጥበት የተሞላበት መሬት" መሆኑን መግለጻቸውንም ነው ልጃቸው የተናገረችው።
ከሁለት ወይም ከሶስት ሰዓታት ገደማ በኋላ ከኪቡትዝ ኒር ኦዝ አካባቢ የመጡ አምስት ሰዎችን ወደተለየ ክፍል ወሰዷቸው ብለዋል።
በስፍራው ጠባቂዎች፣ የድንገተኛ አደጋ የጤና ባለሙያ እንዲሁም ዶክተር መኖራቸውንም ገልጸዋል።
እሳቸው እና ሌሎች ታጋቾች ንጽህናው በተጠበቀ መልኩ መያዛቸውንም አስረድተዋል።
በዋሻዎች ውስጥ እያሉም ነጭ አይብ እና ኩከምበር እንዲመገቡ ይሰጣቸው እንደነበርም ነው በዚህ ወቅት ያስረዱት።
የሐማስ ታጣቂዎችም እየተመገቡት የነበረው ተመሳሳይ ምግብም እንደነበርም ገልጸዋል።
በጋዛ ስር ባሉ ዋሻዎች ውስጥ ፍራሽ ላይ ያድሩ እንደነበር እና ዶክተሩም በየሁለት እና ሶስት ቀናት ልዩነት ይጎበኘን ነበር ብለዋል።
ወደ ጋዛ በሚወስደው የሞተር ሳይክል ጉዞ ላይ አደጋ የደረሰበት ታጋች ህክምና እንዳገኘም ገልጸዋል።
የድንገተኛ አደጋ የጤና ባለሙያውም የሚያስፈልጋቸውን መድኃኒቶች እንዳመጣላቸውም ነው የተናገሩት
ሐማስ ሁለቱን አረጋውያን ሴቶች ለመልቀቅ የወሰነው በሰብዓዊነት እና በጤና ምክንያት እንደሆነም አስታውቋል።
የሐማስ ወታደራዊ ክንፍ ግለሰቦቹን ለአለም አቀፉ ቀይ መስቀል ድርጅት ተወካዮች ሰኞ ዕለት አስረክቧል።
ታጋቾቹ የተለቀቁት በግብጽ እና ኳታር አሸማጋይነት ነው። እስራኤል ሁለቱን ታጋቾች ለማስመለስ ግብጽ በማሸማገሉ ረገድ ላደረገችው ጥረት እንዲሁም ቀይ መስቀል ስላበረከተው አስተዋጽኦ አመስግናለች።