በአሜሪካ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ወደ 6 ሚሊዮን ተቃረበ

በአሜሪካ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ወደ 6 ሚሊዮን ተቃረበ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በዓለማችን በከፍተኛ ሁኔታ ወረርሽኙ እየተስፋፋ ያለው የት ነው?

    የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሥርጭት በአንዳንድ አገራት እየቀነሰ ቢሆንም ፤ በአንዳንድ አገራት ደግሞ ሊጠፋ ነው ሲባል ዳግም እያገረሸ አስቸግሯል።

    ለመሆኑ በዓለማችን የወረርሽኙ ማዕከል የሆኑ አገራት የትኞቹ ናቸው?

    ላቲን አሜሪካና እስያ በአንድ ቀን በቫይረሱ የሚያዙ ከፍተኛ ሰዎች ቁጥር የተመዘገበባቸው አህጉሮች ናቸው። በአገራት ደረጃ ደግሞ፡

    አሜሪካ ፡ አሜሪካ በቫይረሱ በተያዙ ሰዎች ቁጥር በመጀመሪያ ደረጃ ላይ የተቀመጠች ሲሆን ፤ ብራዚል ትከተላታለች።

    ሜክሲኮ፡ በሜክሲኮ በቫይረሱ ሳቢያ ከ60 ሺህ በላይ ሰዎች ሕይወታቸው ያለፈ ሲሆን፤ በሟቾች ቁጥር በአህጉሩ በሁለተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች።

    አርጀንቲና፡ ምንም እንኳን የለይቶ ማቆያ ሕጓ ጥብቅ የነበረ ቢሆንም አርጀንቲና ሰኞ ዕለት ከፍተኛ የተባለውን በቫይረሱ የተያዙና ሞቱ ሰዎች ቁጥር መዝግባለች።

    ሕንድ ፡ በሕንድ እስካሁን ከ3 ሚሊየን ሰዎች በላይ በቫይረሱ ተይዘዋል። በአማካይ በአንድ ቀን ከ60 ሺህ በላይ አዲስ ሰዎች በቫይረሱ እየተያዙ ነው። ከ58 ሺህ በላይ ሰዎችም በበሽታው ሳቢያ ሕይወታቸውን አጥተዋል። ሕንድ በዓለማችን ከፍተኛ ሞት የተመዘገበባት አራተኛዋ አገር ናት።

  2. ደቡብ ኮሪያ ትምህርት ቤቶችን መልሳ ዘጋች

    ደቡብ ኮሪያ በኮሮናቫይረስ ምክንያት በዋና ከተማ ሴኡል የሚገኙ መዋዕለ ሕጻናትን ጨምሮ ሁሉም ትምህርት ቤቶች በአስቸኳይ እንዲዘጉ አዘዘች።

    በቅርብ ቀናት ውስጥ በዋና ከተማዋ እና በከተማዋ ዙርያ የኮሮናቫይረስ ማገርሸቱን ተከትሎ ነው ባለሥልጣናቱ እዚህ አስቸኳይ ውሳኔ ላይ የደረሱት።

    ባለፉት ሁለት ሳምንታት ብቻ 200 የሚሆኑ መምህራንና ተማሪዎች በኮሮናቫይረስ ተይዘው ተገኝተዋል።

    በዚህም የተነሳ ወረርሽኙን ለመቆጣጠር እስከ መስከረም 11 ድረስ ትምህርት የመስጠቱ ሂደት በርቀት እንዲቀጥል የደቡብ ኮሪያ የትምህርት ሚኒስቴር ቁርጥ ውሳኔ ላይ ደርሷል።

    የጤና ጥበቃ ባለሥልጣናት በመላው አገሪቱ ወረርሽኙ መልሶ እንዳያገረሽ ስጋትአላቸው። ተጨማሪ ከዚህ ያንብቡ ደቡብ ኮሪያ ትምህርት ቤቶች ተመልሰው እንዲዘጉ አዘዘች

  3. የለይቶ ማቆያ ደንብን የተላለፈችው ግለሰብ የ6 ወር እስር ተፈረደባት

    አውስትራሊያ ውስጥ የሚገኝ አንድ ፍርድ ቤት በአገሪቱ የተጣለውን የኮሮናቫይረስ መቆጣጠሪያ የለይቶ ማቆያ ደንብን በመተላለፍ ከአንድ ግዛት ወደ ሌላ ግዛት ተደብቃ ለመጓዝ በሞከረች ሴት ላይ የስድስት ወራት እስር ፈረደ።

    የ28 ዓመቷ አሸር ፋይ ቬንደር ፍርድ ቤት ቀርባ የወጣውን በሽታውን የመቆጣጠሪያ ደንብ መተላለፏን አምናለች።

    ግለሰቧ ወደ ሌላ ቦታ ከመሄዷ በፊት በእራሷ ወጪ በሆቴል ውስጥ ለ14 ቀናት ተለይታ እንድትቆይ ብትታዘዝም፤ በተሽከርካሪ ተደብቃ ወደ ሌላ ግዛት ለመሄድ ስትሞክር መያዟን ፍርድ ቤቱ አመልክቷል።

    በጆንሰው ሆፕኪንስ ሆስፒታል መረጃ መሰረት አውስትራሊያ አስካሁን 25,053 ሰዎች በበሽታው እንደተያዙባት የመዘገበች ሲሆን 525 ሰዎች ደግሞ ሞተዋል።

    ወረርሽኙ እየተስፋፋ በመምጣቱ የአውስትራሊያ የተለያዩ ግዛቶች በሽታውን ለመከላከል የሚወስዷቸውን እርምጃዎች እያጠናከሩ ነው።

  4. ኮቪድ-19 ንክች አላደረገንም የሚሉት 10 አገራት

  5. የኮሮናቫይረስ ክትባት ሙከራ እየተፋጠነ ነው

    በኦክስፎርድ ዩኒቨርስቲ የተሰራውን ክትባት ውጤታማነትና ደኅንነትን ለማረጋገጥ በዓለም ዙሪያ በሚገኙ 50 ሺህ በሚደርሱ ሰዎች ላይ ሙከራ ሊደረግ መሆኑን ክትባቱን እያዘጋጀ ያለው ቡድኑ አባል የሆኑት ፕሮፌሰር አንድሪው ፖላርድ ተናገሩ።

    ለኮሮናቫይረስ መከላከያ ይሆናል የተባለው ክትባት በኦክስፎርድ ዩኒቨርስቲና በመድኃኒት አምራቹ ድርጅት አስትራዜኔካ የተዘጋጀ ሲሆን በዓለም ዙሪያ እየተደረጉ ካሉት የክትባት ሙከራዎች ተስፋ ሰጪው እንደሆነ ተነግሯል።

    በዚህ የክትባት ሙከራ ሂደት 10 ሺህ ሰዎች በዩናይትድ ኪንግደም እንዲሁም ሌሎች 10 ሺህ ሰዎች ደግሞ በብራዚልና በደቡብ አፍሪካ ውስጥ ተሳታፊ ሆነዋል።

    ከዚህ ባሻገርም በአሜሪካ ውስጥ በ30 ሺህ ሰዎች ላይ ክትባቱን ለመሞከር ዕቅድ አለ።

    ፕሮፌሰር ፖላርድ ለቢቢሲ እንደተናገሩት በቀጣይ ሳምንታት እንዲሁም ወራት በበሽታው የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ክትባቱ ምን ያህል ውጤታማ መከላከያ እንደሆነ በፍጥነት ለማረጋገጥ ለተመራማሪዎቹ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል።

  6. ዋነኛውን የኮሮናቫይረስ ክትባት ምርምርን የሚመሩት ሴት ማን ናቸው?

  7. በኢትዮጵያ በቫይረሱ ሳቢያ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 692 ደረሰ

    በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓታት በተካሄደ 18 ሺህ 851 የናሙና ምርመራ 1472 ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ተረጋገጠ።

    የጤና ሚንስትር እና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም በሰጡት መግለጫ መሠረት፤ ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች አጠቃላይ ቁጥር 42 ሺህ 143 ደርሷል።

    በአንድ ቀን 14 ተጨማሪ ሰዎች የሞቱ ሲሆን፤ በቫይረሱ ሳቢያ ሕይወታቸው ያለፈ ሰዎች ቁጥር 692 መድረሱ ተገልጿል።

    ተጨማሪ 267 ሰዎች ከበሽታው አገግመው፤ በአጠቃላይ ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 15 ሺህ 262 ደርሷል።

    በኢትዮጵያ እስካሁን 775 ሺህ 908 ናሙና ላይ ምርመራ ተካሂዷል።

  8. ሳይንቲስቶች በድጋሚ በኮሮናቫይረስ የተያዘ ሰው አገኙ

    የሆንክ ኮንግ ዩኒቨርስቲ ሳይንቲስቶች አንድ ጤናማና ወጣት ግለሰብ በድጋሚ በኮቪድ-19 መያዙን ገለጹ። ግለሰቡ ከአራት ወር ከግማሽ በፊት በበሽታው ተይዞ ነበር።

    ሳይንቲስቶቹ የመጀመሪያው ቫይረስ እንዳላገረሸና ሁለተኛው ቫይረስ ከመጀመሪያው የተለየ እንደሆነ ገልጸዋል።

    በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች በሽታውን የመከላከል አቅም እንደሚያዳብሩና ይህም በቫይረሱ ዳግመኛ እንዳይያዙ እንደሚረዳቸው ሳይንቲስቶች ይገልጻሉ።

    በሽታውን የመከላከል አቅም ምን ያህል እንደሚቆይ ግን ግልጽ መረጃ የለም።

    ሰዎች በቫይረሱ ዳግመኛ የሚያዙ ከሆነ በርካቶችን ከበሽታው ለመታደግ ክትባት ያስፈልጋል ማለት ነው።

    በእርግጥ በጠና የታመሙ ሰዎች መጠነኛ ምልክት ከሚያሳዩ ህሙማን በተሻለ በሽታውን የመከላከል አቅም ያዳብራሉ።

    እንደ ጉንፋን ባሉ በሽታዎች ሰዎች በድጋሚ ስለሚይዙ፤ ኮቪድ-19ን የሚያስከትለው ሳርስ-ኮቭ-2 ቢያገረሽም አያስገርምም።

    የዓለም ጤና ድርጅት በበኩሉ በቫይረሱ ዳግመኛ የተያዘ አንድ ሰውን ተመርኩዞ ወደ ድምዳሜ መድረስ አይቻልም ብሏል።

    የሆንክ ኮንጉ ሙሉ ጥናት ስላልታተመ ብዙ ዝርዝር መረጃዎች የሉም።

    በድጋሚ በቫይረሱ ተይዟል የተባለው ግለሰብ ምልክት ሳያሳይ፤ በአየር መንገድ ምርመራ ሲደረግ ነው በሽታው እንዳለበት የታወቀው።

    ሰዎች ዳግመኛ በቫይረሱ ሊያዙ ይችላሉ የሚል ድምዳሜ ላይ ከመደረሱ አስቀድሞ፤ በርካታ የማኅበረሰብ ምርመራዎች መካሄድ አለባቸው።

  9. ወረርሽኙ በደቡብ ኮርያ በአገር አቀፍ ደረጃ እንደሚሰራጭ ተሰግቷል

    ኮቪድ-19ን በተሻለ ሁኔታ በመከላከል ስትመሰገን የነበረችው ደቡብ ኮርያ ውስጥ በአገር አቀፍ ደረጃ ወረርሽኙ ሊሰራጭ እንደሚችል ባለሥልጣኖች አስጠነቀቁ።

    በቅርቡ አንድ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በቫይረሱ የተያዙ በርካታ ሰዎች የተገኙ ሲሆን፤ ወረርሽኙ በ17ቱም ግዛቶች ተሰራጭቷል።

    በየቀኑ በሽታው የተያዙ ሰዎች ቁጥር ባለ ሦስት አሃዝ ሆኗል።

    አብዛኞቹ ህሙማን በመዲናዋ ስዑል የሚገኙ ናቸው። በከተማዋ ከዓሥር ሚሊዮን በላይ ሰዎች ይኖራሉ።

    በሌላ በኩል ቀኝ ዘመም አማኞች፤ ቫይረሱ ቤተ ክርስቲያን ለማዘጋት የተወጠነ ሴራ እንደሆነ ያምናሉ። ምርመራ እንዲደረግላቸውም ፍቃደኛ አይደሉም።

    ይህ ደግሞ የወረርሽኙን ስርጭት እንዳያባብሰው ተሰግቷል።

    ከቤተ ክርስቲያኑ በብዛት በቫይረሱ የተያዙት በ20ዎቹ የእድሜ ክልል ያሉ ናቸው።

  10. አሜሪካ የደም ፕላዝማ ለኮሮናቫይረስ ህክምና እንዲውል ፈቀደች

  11. በአውሮፓ ወረርሽኙ እንዳያገረሽ ተሰግቷል

    በአውሮፓ ወረርሽኙ እንደገና እንዳያገረሽ ተሰግቷል። በፈረንሳይና በጣሊያን ባሳለፍነው ቅዳሜና እሁድ የተመዘገቡ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከፍተኛ መሆኑ በርካቶችን አስጨንቋል።

    ፈረንሳይ ባለፉት 24 ሰዓታት ከ4 ሺህ 800 በላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን የመዘገበች ሲሆን ይህም ከግንቦት ወር ወዲህ በአንድ ቀን የተመዘገበ ከፍተኛው ቁጥር ነው ተብሏል።

    የጤና ሚኒስትር ኦሊቪየር ቬራን፤ ዕድሜያቸው ከ40 ዓመት በታች ያሉ ሰዎች በተለይ አካላዊ ርቀትን ሳይጠብቁ የተለያዩ ድግሶች ላይ ስለሚገኙ የቫይረሱ በመካከላቸው የመዛመት ፍጥነት በሌላ የዕድሜ ክልል ከሚገኙት ጋር ሲነፃፀር አራት እጥፍ እንደሆነ ተናግረዋል።

    ከዓለም አገራት ቀድማ በርካታ ዜጎቿን በቫይረሱ ያጣችው ጣሊያንም ከግንቦት ወር ወዲህ ከፍተኛ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር መዝግባለች። ባለፉት 24 ሰዓታት1 ሺህ 071 ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል።

    በአገሪቷ የቫይረሱ ሥርጭት መጨመሩ ከጉዞና ከቱሪስት መዝናኛዎች ጋር የተያያዘ መሆኑን ሪፖርቱ አመልክቷል።

    ይሁን እንጅ በጣሊያን አጠቃላይ አዲስ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከፈረንሳይና ስፔን ያነሰ ነው።

  12. በደቡብ አፍሪካ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው ተመለሱ

    በደቡብ አፍሪካ በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ስጋት ለሳምንታት ተዘግተው የቆዩ ትምህርት ቤቶች ዛሬ በሁሉም ደረጃ ላይ ያሉ ተማሪዎቻቸውን መቀበል መጀመራቸው ተገለፀ።

    የመጨረሻ ዓመት ተማሪዎች ግን ለፈተና ለመዘጋጀት ትምህርት የጀመሩት ቀደም ብለው ነበር።

    አገሪቷ በወረርሽኙ ሳቢያ ትምህርት ቤቶችን አንዴ ስትከፍት አንዴ ስትዘጋ ቆይታለች።

    የአገሪቷ ፕሬዚደንት ሲሪል ራማፎሳ ትምህርት ቤቶችን በይፋ እንዲከፈቱ ካደረጉ በኋላ ወረርሽኙ መስፋፋቱን ተከትሎ በተፈጠረ የሕዝብ ቁጣ ተማሪ ቤቶቹ በድጋሜ እንዲዘጉ ያዘዙት ሃምሌ ወር ላይ ነበር።

    አሁን ላይ እንዲከፈቱ የተደረገውም በአገሪቷ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየቀነሰ በመምጣቱ እንደሆነ ተነግሯል።

    የጤና ሚኒስተሩ በአገሪቷ የበሽታው ሥርጭት ከፍተኛ እንደነበር ገልፀው አሁን ላይ መቀነስ መጀመሩን አስታውቀዋል።

    ባለፈው ሳምንት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅቶች፤ የአፍሪካ መንግሥታት ወረርሽኙን ለመከላከል ከሚያስችሉ የጥንቃቄ እርምጃዎችን ጋር ትምህርት ቤቶችን እንዲከፍቱ አሳስበዋል።

    የደቡብ አፍሪካ ባለሥልጣናትም በዚህ ሳምንት ጥንቃቄ በተሞላበት ሁኔታ የመማር ማስተማር ሂደቱን እንደገና ለመጀመር መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።

  13. ሩዋንዳ በአንድ ቀን ከፍተኛውን በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር መዘገበች

    ሩዋንዳ ኮሮናቫይረስ በአገሪቷ መግባቱን ካረጋገጠችበት መጋቢት ወር ወዲህ ትናንት በአንድ ቀን ከፍተኛ የተባለውን በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር መዘገበች።

    አዲስ በቫይረሱ ከተያዙ 200 ሰዎች መካከልም አብዛኞቹ የተገኙት በዋና መዲናዋ ኪጋሊ ሲሆን የአንድ ሰው ሕይወትም አልፏል።

    ይህም በአጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር ከ3 ሺህ በላይ አድርሶታል። 1 ሺህ የሚጠጉት የተመዘገቡትም ባለፉት ሁለት ሳምንታት ነው ተብሏል።

    ባለፈው ሳምንት የተወሰኑ የመዲናዋ አካባቢዎች ለበርካታ ሳምንታት ተጥሎ የነበረው የእንቅስቃሴ ገደብ ቢነሳላቸውም፤ የወረርሽኙን ሥርጭት ተከትሎ ሁለት ትላልቅ የገበያ ቦታዎች ለአንድ ሳምንት እንዲዘጉ ተደርገዋል።

    በኪጋሊ እየተዛመተ ያለው ወረርሽኝም በከተማዋ በድጋሚ አዳዲስ ገደቦች ሊጣሉ ይችላሉ የሚል ስጋትን ፈጥሯል።

    በሩዋንዳ በደቡብ ሱዳን እያገለገሉ የነበሩና ለሕክምና ወደ አገሪቷ የመጡ ሁለት የተባበሩት መንግሥታት የሰላም አስከባሪዎችን ጨምሮ 12 ሰዎች በቫይረሱ ሕይወታቸው አልፏል።

    ሩዋንዳ ከሰሃራ በታች ካሉ አገራት ቀድማ የእንቅስቃሴ ገደብ የጣለች አገር ናት። ቱሪዝሟን መክፈትና ኢኮኖሚያዋን ማንቀሳቀስ የጀመረችውም በቅርቡ ነው።

    ሆኖም ትምህርት ቤቶች ፣ ስፖርት ቤቶች፣ መሰባሰብን የሚሹ ሌሎች የመዝናኛ ተግባራትን እንደዘጋች ነው።

  14. አሜሪካ የደም ፕላዝማን ለኮሮናቫይረስ ታማሚዎች ሕክምና በስፋት እንዲውል ፈቀደች

    የአሜሪካ ምግብና መድሃኃኒት አስተዳደር የደም ፕላዝማ ለኮሮናቫይረስ ታማሚዎች ድንገተኛ ሕክምና እንዲውል ፈቃድ ሰጠ።

    አንድ ሰው በኮሮናቫይረስ ሲያዝ የተፈጥሮ በሽታን የመከላከያ ሥርዓቱ በሽታን አምጪ ተህዋስን የመከላከያ ዘዴን ያዘጋጃል፤ ይህም ቫይረሱን በማጥቃት ወደ በሽታ እንዳይሸጋገር ያደርጋል።

    ይህ ሂደትም በአንድ ወር ውስጥ የሚፈጠር ሲሆን ፕላዝማ በተባለውና በደም ውስጥ ባለው ፈሳሽ ክፍል ውስጥ የሚገኝ ነው።

    ይህንን ፕላዝማ በኮቪድ-19 በጠና ለታመሙ ሰዎች በመስጠት ከቫይረሱ ጋር ፍልሚያ የገጠመውን የእራሳቸውን ተፈጥሯዊ በሽታን የመከላከያ ሥርዓት በማጠናከር ከበሽታው እንዲያገግሙ ለማገዝ የሚያስችል ነው።

    በመሆኑም ሕክምናው ከበሽታው ካገገሙ ሰዎች ከተወሰደና በበሽታ መከላከል አቅም [አንቲ ቦዲ] የበለፀገውን ይህን የደም ፕላዝማ ይጠቀማል።

    ይህ ሕክምና ቀደም ብሎ በአሜሪካ ከ70 ሺህ በላይ ሰዎች ላይ ጥቅም ላይ የዋለ ሲሆን አሁን የፈቀደችው ሕክምናው በስፋት እንዲሰጥ ነው። ኮሮናቫይረስ፡ አሜሪካ የደም ፕላዝማ ለኮቪድ-19 በሽተኞች እንዲውል ፈቀደች

  15. በኢትዮጵያ 1ሺህ 638 ሰዎች በቫይረሱ ሲያዙ፤ የ16 ሰዎች ሕይወት አለፈ

    በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓታት በተደረገ 20 ሺህ 153 የላብራቶሪ ምርመራ ተጨማሪ 1 ሺህ 638 ሰዎች በቫይረሱ ሲያዙ የ16 ሰዎች ሕይወት ማለፉን የጤና ሚኒስቴርና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ባወጡት ዕለታዊ መግለጫ አስታወቁ።

    ይህም አጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 40 ሺህ 671 አድርሶታል።

    በአጠቃላይም በቫይረሱ ሳቢያ እስካሁን የ678 ሰዎች ሕይወት አልፏል።

    ባለፉት 24 ሰዓታት 515 ሰዎች ከበሽታው ያገገሙ ሲሆን በአጠቃላይ 14 ሺህ 995 ሰዎች ከበሽታው ማገገማቸው ተገልጿል።

    ኢትዮጵያ ቫይረሱ መገኘቱ ከተረጋገጠ ጊዜ ጀምሮ 757 ሺህ 57 የላብራቶሪ ምርመራዎችን አድርጋለች።

    የቫይረሱ ሥርጭትም ከዕለት ተዕለት እየጨመረ ነው።

  16. ክትባት ፍለጋ

    በአሁኑ ሰዓት አለም የኮሮናቫይረስ ክትባትን በጉጉት እየጠበቀ ይገኛል።

    ቢያንስ 30 ያህል የሙከራ ክትባቶች በሰዎች ላይ ሙከራ እየተደረገባቸው እንደሆነ ተገልጿል። በጎ ፈቃደኞችም ተመርጠው እየተሞከረባቸው ነው።

    ሆኖም ነገሩ ቀላል አይደለም። ረዥም ጊዜንም ሊወስድ እንደሚችል እየተነገረ ነው። ለዚህም አንደኛው ምክንያት በጎ ፈቃደኞች በቫይረሱ እንዲጠቁ ማድረግና በየቀኑ የሚኖራቸውን መስተጋብር መከታተል ጊዜ ስለሚወስድ ነው።

    ሌላኛው ሙከራ ደግሞ በጎ ፈቃደኞች የሙከራው ክትባት ከተሰጣቸው በኋላ በኮሮናቫይረስ እንዲጠቁ ይደረጋል፤ ከዚያም ክትባቱ ጠብቋቸው እንደሆነም ክትትል ይደረጋል።

    በዚህኛው ወቅት ውጤቱ በፍጥነት የሚታወቅ ቢሆንም አደጋና የሞራል ጥያቄ ስለሚያስነሳም ክትባቱን እየሰሩ ያሉ ኩባንያዎች መጣደፍ አልፈለጉም።

    ሆኖም በርካታ በጎ ፈቃደኞች በኮሮናቫይረስ ሆን ብሎ መጠቃትንና ሙከራ ለመደረግ ፈቃደኛነታቸውን እያሳዩ ነው።

    ከእነዚህም አንዱ አላስቴይር ፍሬዘር ኡርኳሃርት ነው። ዕድሜውም ገና አስራ ስምንት ነው።

    "በእድሜም ሆነ በጤናዬ ተጋላጭ ከሆኑት ማህበረሰብ አልመደብም። እናም ከኔ በላይ የማይቋቋሙትን ለማዳን ሙከራው ቢደረግብኝ ምን ችግር አለው?" ብሏል።

  17. እድሜያቸው 12 እና ከዚያ በላይ የሆኑ ታዳጊዎች የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ አለባቸው ተባለ

  18. "ከቤት መውጣት ያስፈራኛል" ሦስት ሚሊዮን ህሙማን ያለባት ሕንድ ነዋሪ

    የኮሮናቫይረስ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ ባለባት ሕንድ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ከሦስት ሚሊየን ተሻግሯል።

    ሕንድ ከአሜሪካና ብራዚል በመቀጠል ከአለም ቀዳሚ ከሆኑ አገራት ሦስተኛ ብትሆንም በቀን ውስጥ በቫይረሱ በሚያዙ ሰዎች ቁጥር ግን እየመራች ትገኛለች።

    በደቡብ ሕንድ ባንጋሎር ግዛት የኮሮናቫይረስ በኑሯቸው ላይ ከፍተኛ ጫና እያሳደረባቸው እንደሆነ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ነዋሪዎችን ዋቢ አድርጎ ዘግቧል።

    "በጣም ነው የፈራሁት" በማለት የሚናገረው ራሜሽ "ከቤት መውጣት ያስፈራኛል፤ ቢሮ መሄድ እፈራለሁ። ቤት የእድሜ ባለፀጋ የሆነችው የ67 አመት እናቴ አለች። ባለቤቴ ነፍሰ ጡር ናት። ከዚህም በተጨማሪ የሦስት አመት ህፃን አለን። በአጠቃላይ ከቤት መውጣት በጣም ነው የሚያስፈራኝ" ብሏል።

    ሕንድ ያላት የሕዝብ ቁጥር ከ1.3 ቢሊዮን በላይ ከመሆኑ አንፃር ከሌላ አገራት ጋር ስናወዳድር ይህ ከግምት ውስጥ ቢገባም፤ የምትመረምራቸው ሰዎች ቁጥር ማነስም ስጋትን አጭሯል።

    በቫይረሱ ክፉኛ ከተመቱት መካከል ዋና መዲናዋ ዴልሂ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር መቀነሱን ቢያሳይም አዳዲስ የወረርሽኝ ማዕከል ብቅ እያሉ ነው።

    ከነዚህም መካከል በሰሜናዊ ሕንድ የሚገኙት ኡታር ፕራዴሽና ቢሃር እንዲሁም በደቡባዊ ክፍልም ከፍተኛ ቁጥር እየተመዘገበ ነው።

  19. ጀርመን በዚህ ወረርሽኝ ወቅት በአንድ ቀን ሦስት የሙዚቃ ድግሶችን ለምን አሰናዳች?

  20. “ኢንተርኔት የዘመናችን ልዩ ስጦታ፣ በአግባቡ ካልተጠቀምንበት ደግሞ አደጋ ነው” ዶክተር ጋሻው አብዛ