በአሜሪካ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ወደ 6 ሚሊዮን ተቃረበ

በአሜሪካ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ወደ 6 ሚሊዮን ተቃረበ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በኢትዮጵያ ተጨማሪ 1ሺህ186 ሰዎች በቫይረሱ ሲያዙ፤ የ20 ሰዎች ሕይወት አለፈ

    በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓታት በ18 ሺህ 060 ናሙናዎች ላይ በተደረገ የላብራቶሪ ምርመራ 1 ሺህ 186 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን የጤና ሚኒስቴርና የኅብረተሰብ ጤና ተቋም በዕለታዊ መግለጫቸው አስታወቁ።

    ይህም በአጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 46 ሺህ 407 አድርሶታል።

    ቫይረሱ ከተገኘባቸው ሰዎች በተጨማሪ ባለፉት 24 ሰዓታት ከወረርሽኙ ጋር በተያያዘ የ20 ሰዎች ሕይወት ማለፉም ተገልጿል። እስካሁን ከቫይረሱ ጋር በተያያዘ የ745 ሰዎች ሕይወት አልፏል።

    በሌላ በኩል ተጨማሪ 518 ሰዎች ከበሽታው ያገገሙ ሲሆን ከበሽታው ያገገሙ ሰዎች ቁጥርም 16 ሺህ 829 ደርሷል።

    በኢትዮጵያ ከጊዜ ወደ ጊዜ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ 330 ሰዎችም በፅኑ መታመማቸውን መግለጫው አመልክቷል።

    እስካሁን 831 ሺህ 470 የላብራቶሪ ምርመራዎች ተከናውነዋል።

  2. በሚሊኒየም አዳራሽ የሚገኘው የኮቪድ-19 ጽኑ ህሙማን ክፍል እየሞላ ነው

  3. የዓለም ጤና ድርጅት "በአውሮፓ የትምህርት ቤቶች መከፈት" አሳስቦኛል አለ

    የዓለም ጤና ድርጅት አውሮፓ 'ግራ የሚያጋባ' ሁኔታ ውስጥ መሆኗን ጠቁሟል።

    ይህን ያለው ለአዲስ የትምህርት ዘመን ትምህርት ቤቶች ሊከፈቱ በዝግጅት ላይ መሆናቸውን ተከትሎ ነው።

    ምንም እንኳ ትምህርት ቤቶች የወረርሽኙ መዛመት ሁነኛ ሚና እንዳልነበራቸው ያስታወሰው ድርጅቱ ሆኖም ግን ወጣት ልጆች ሕዝብ በተሰበሰበባቸው አካባቢዎች በሽታውን በስፋት ማስተላለፋቸው የከዚህ ቀደም መረጃዎች ያሳያሉ ብሏል።

    የድርጅቱ የአውሮፓ ዳይሬክተር ሐንስ ክሉግ በሰጡት ጋዜጣዊ መግጫ እንደተናገሩት ትምህርት ቤቶች ቢከፈቱ ተማሪዎች ያልቃሉ ማለት ባይሆንም ነገሩ ጣጣ አያመጣብንም ማለትም አይደለም ብለዋል።

    የፈረንጆቹ ክረምት (ዊንተር) መምጣቱን ተከትሎም ልጆች ከአያቶቻቸውና ከአዋቂዎች መገናኘታቸው አይቀርም ብለዋል ሐንስ። ይህም የመዛመቱን ስጋት ይጨምራል ብለው ሰግተዋል።

  4. በአውሮፓ አገሮች የኮቪድ-19 ስርጭት እየሰፋ ነው

    በፈረንሳይ፣ ጣልያን፣ ስፔን፣ ስዊዘርላንድ፣ ክሮሽያ እንዲሁም በሌሎችም የአውሮፓ አገሮች ኮቪድ-19 እንደ አዲስ እየተሰራጨ ነው።

    ቫይረሱ ድጋሚ ሊያገረሽ ይችላል የሚል ስጋትም አለ።

    ከተለያዩ የአውሮፓ አገራት የተውጣጡ ዜናዎችን እንመልከት፦

    ·ፈረንሳይ፡በ24 ሰዓት ውስጥ 5,429 ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል። ጠቅላይ ሚንስትር ዣን ካስቴክስ ከመንግሥት በተጨማሪ ሁሉም ሰው በሽታውን ለመከላከል የድርሻውን እንዲወጣ አሳስበዋል።

    ·ጣልያን፡ በአንድ ቀን 1,367 በቫይረሱ መያዛቸውና 13 ሰዎች መሞታቸው ተረጋግጧል።

    ·ስፔን፡ ትምህርት ለማስጀመር የተለያዩ ግዛቶች አመራሮች ከጤናና ትምህርት ኃላፊዎች ጋር ይወያያሉ። በ24 ሰዓት ውስጥ 3,594 ሰዎች ቫይረሱ ተገኝቶባቸዋል።

    ·ክሮሽያ፡ ቱሪዝም የአገሪቱ የጀርባ አጥንት ቢሆንም፤ ጎብኚዎችን ተከትሎ የበሽታው ስርጭትም እየሰፋ ነው። 358 ተጨማሪ ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል።

    ስዊዘርላንድ፡በከፍተኛ ሁኔታ በሽታው እየተሰራጨ ያለው በዙሪክ ነው። ከ100 ሰዎች በላይ በሚሰበሰቡባቸው የምሽት ክበቦች የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል ማድረግ ግዴታ ነው።

  5. ቻይና ለሠራተኞች ክትባት መስጠት ጀምራለች

    በዚህ ወር መባቻ፤ የአንድ የግል ድርጅት ኃላፊ ጥቅምት ላይ የኮቪድ-19 ክትባት እንደሚዳረስ ለሠራተኞቻቸው ተናግረዋል።

    ይህም ምጣኔ ሀብቱ እንዲያገግም፣ ድርጅቱ በርካታ ምርት እንዲሸጥ እንደሚረዳም ገልጸዋል።

    እንዲህ መባሉን ተከትሎ የቻይና መንግሥት ክትባትን በተመለከተ የደረሰበትን ይፋ ለማድረግ ተገዷል።

    ከቻይና ተነስቶ መላው ዓለምን ያዳረሰውን ኮቪድ-19 ለመግታት ቻይና ቀን ከሌት ክትባት ላይ ምርምር እያደረገች ነው።

    ባለፈው ሳምንት ክትባቱ ስለደረሰበት ደረጃ በብሔራዊ ቴሌቭዥን ጣቢያ ተገልጿል። አንዲት ሴት ቤተ ሙከራ ውስጥ ፈገግ ብላ የክትባት ብልቃጥ ይዛም ታይቷል።

    ሲኖፋርም እንዳለው ክትባቱን ጥቅምት ላይ ለማዳረስ ተስፋ አለ። ዋጋው ወደ 140 ዶላር ሊጠጋ እንደሚችልም ገልጿል።

  6. ታንዛንያ 3 ተጨማሪ የኬንያ አየር መንገዶችን አገደች

    ታንዛንያ ሦስት ተጨማሪ የኬንያ አየር መንገዶችን አገደች።

    የታንዛንያ ሲቪል አቪየሽን ለፍላይ 540፣ ኤር ኬንያ ኤክስፕረስ እና ሳፋሪሊንክ አቪየሽን የተሰጠ ፍቃድን ሰርዟል።

    አየር መንገዶቹ የቱሪስት መዳረሻ ወደሆኑት ዛንዚባር እና ኪሊማንጃሮ በየቀኑ በረራ ነበራቸው።

    የሲቪል አቪየሽኑ ዋና ኃላፊ ሐምዛ ጆሃሪ እንዳሉት፤ የሦስቱ የኬንያ አየር መንገዶች ፍቃድ የተሰረዘው ወቅታዊውን የታንዛንያ እና የኬንያ ሽኩቻ ተከትሎ ነው።

    ቀደም ሲል ኬንያ የታንዛንያ ተጓዦች ለ14 ቀናት ለይቶ ማቆያ ይገባሉ በማለቷ የኬንያ አየር መንገድ ታግዶ ነበር።

    ፕሬዘዳንት ጆን ማጉፉሊ፤ ሰኔ ላይ ታንዛንያ ከኮሮናቫይረስ ነፃ ናት ብለዋል። መንግሥታቸው በሽታውን ለመከላከል ጥብቅ እርምጃ ባለመውሰዱ ይተቻል።

  7. 53 ሰዎች ብቻ ያሉት ጎሳ ኮሮናቫይረስ አስግቶታል

  8. በኢትዮጵያ የተጠለሉ ስደተኞች ለረሀብ ሊጋለጡ ይችላሉ ተባለ

    የተባበሩት መንግሥታት፣ የዓለም የምግብ ፕሮግራም (ደብሊውኤፍፒ) በምሥራቅ አፍሪካ አገራት ረሀብና የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ሊከሰት እንደሚችል ጠቆመ።

    በምሥራቅ አፍሪካ የሚገኙና በድርጅቱ እርዳታ ሕይወታቸውን የሚገፉ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ስደተኞች ተጋላጭ መሆናቸው ተገልጿል።

    ኮቪድ-19 ያሳደረው ማኅበራዊና ምጣኔ ሀብታዊ ተጽዕኖ የእርዳታ ሰጪዎችን ድጋፍ እንደቀነሰውም አክለዋል።

    ድርጅቱ በኢትዮጵያ፣ ኡጋንዳ፣ ኬንያ፣ ደቡብ ሱዳን እና ጅቡቲ ለተጠለሉ ከ2.7 ሚሊዮን በላይ የሆኑ ስደተኞች ያደርግ የነበረውን የምግብና የገንዘብ ድጋፍ 30 በመቶ ለመቀነስ ተገዷል።

    የድርጅቱ የምሥራቅ አፍሪካ ኃላፊ ማይክል ደንፎርድ፤ “ስደተኞች በተጨናነቀ ሁኔታ፣ በቂ ውሃና የጤና አገልግሎት ሳያገኙ ስለሚኖሩ የበለጠ ለኮቪድ-19 ተጋላጭ ናቸው” ብለዋል።

  9. በእስር ቤቶች ያለውን የወረርሽኝ ስጋት ለመቀነስ ተጨማሪ እስረኞች እንዲለቀቁ ተጠየቀ

    የኮሮናቫይረስ መከሰትን ተከትሎ የተጣለውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈጻጸም የሚከታተለው መርማሪ ቦርድ በእስር ቤቶች ሊከሰት የሚችለውን የወረርሽኙን ስጋት ለመቀነስ ተጨማሪ እስረኞች እንዲለቀቁ ሐሳብ አቀረበ።

    ቦርዱ እንዳለው በማረሚያ ቤቶች አካባቢ የሚከሰትን የኮሮናቫይረስ ስርጭት ለመቀነስ የይቅርታና የአመክሮ መስፈርት የሚያሟሉ የሕግ ታራሚዎች እንዲለቀቁ ባቀረባቸው የውሳኔ-ሐሳቦች ውስጥ ጠይቋል።

    ከዚህ በተጨማሪ ቦርዱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ቀነ ገደብ ሲጠናቀቅ ትኩረት እንዲሰጥ ብሎ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የውሳኔ ሐሳቦችን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ-ጉባዔና ለሚመለከታቸው አስፈጻሚ አካላት አቅርቧል።

    ከእነዚህም መካከል በቀጣይ ሳምንታት በርካታ ሕዝብ ሊሰባሰብባቸው የሚችሉ የተለያዩ ክብረ በዓላትና ማኅበራዊ ክንውኖች ለኮሮናቫይረስ መስፋፋት በር ሊከፍቱ ስለሚችሉ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚያስፈልግ ቦርዱ አሳስቧል።

    በተጨማሪም የድጋፍም ይሁን የተቃውሞ፣ ታቅደውም ይሁን በድንገት የሚካሄዱ ሰልፎችና ስብሰባዎች፤ “በግንዛቤ ሥራ እንዲሁም ሕግ በማስከበር ታግዘው መከናወን እንደሚጠበቅባቸው” ቦርዱ ጠቁሟል።

    የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ተከትሎ የተጣለውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈጻጸም ለመቆጣጠር የተቋቋማው መርማሪ ቦርድ የሥራው ጊዜ እንዲራዘም ካልተደረገ በስተቀር የተሰጠው ኃላፊነት በነሐሴ ወር መጨረሻ ላይ ያበቃል።

  10. በኮሮናቫይረስ በመያዜ ከህመሙ በላይ ጭንቀቱ በርትቶብኝ ነበር፡ ዶ/ር ፋሲካ አምደሥላሴ

  11. ተመልሰናል!

    ይህ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን የተመለከቱ ዜናዎችና ታሪኮች ወደናንተ የምናደርስበት የቀጥታ ዘገባ ገፃችን ነው።

    የዕለተ ሐሙስ ዘገባችንን ይዘን ተመልሰናል።

    ኢትዮጵያ የመጀመሪያውን በኮሮናቫይረስ የተያዘ ሰው ካገኘች ስድስት ወር ሊሞላት የቀሯት ጥቂት ሳምንታት ናቸው። በእነዚህ ጊዜያቶች ውስጥ 813 ሺህ 410 ናሙናዎች ላይ የኮቪድ-19 ምርመራ በማድረግ 45 ሺህ 221 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን አረጋግጣለች። ከእነዚህ መካከልም 725 ሰዎች ሞተዋል።

    ከበሽታው አገግመው ወደ መደበኛ ህይወታቸው የተመለሱ ሰዎችም ቁጥር 16 ሺህ 311 ነው።

    ቢሆንም በተለይ እንደ አዲስ አበባ ባሉ ከተሞች በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በፍጥነት እየጨመረ ይገኛል። በተለይ ከቅርብ ወራት ወዲህ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በፍጥነት እየጨመረ ነው።

    በርካታ የሕክምና ባለሙያዎች የሕብረተሰቡ መዘናጋት ለቫይረሱ እያጋለጠ መሆኑን በመጥቀስ ስርጭቱን ባለበት ለማቆም መከላከያዎቹን ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን ይናገራሉ።

    አካላዊ ርቀትን መጠበቅ፣ እጅን ደጋግሞ በሳሙና መታጠብ፣ እንዲሁም የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ በሽታወን ለመከላከል ወሳኝ ናቸው።

  12. በኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ45 ሺህ አለፈ

    ባለፉት 24 ሰዓታት በተደረገ 18 ሺህ 724 የናሙና ምርመራ 1 ሺህ 533 ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው ተረጋገጠ።

    የጤና ሚንስትር እና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ባወጡት መግለጫ፤ ባጠቃላይ ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች ቁጥር 45 ሺህ 221 ደርሷል።

    ባለፉት 24 ሰዓታት ተጨማሪ 16 ሰዎች ሕይወታቸው ያለፈ ሲሆን፤ ይህም የሞቱ ሰዎችን ቁጥር 725 አድርሶታል።

    በአንድ ቀን 515 ሰዎች ከበሽታው ማገገማቸው የተገለጸ ሲሆን፤ ባጠቃላይ ከቫይረሱ ያገገሙ ሰዎች 16 ሺህ 311 ናቸው።

    በኢትዮጵያ እስካሁን 813 ሺህ 410 የናሙና ምርመራ ተደርጓል።

  13. ኢትዮጵያ በቫይረሱ በተያዙ ሰዎች ቁጥር ከአፍሪካ ሰባተኛ ናት

    በአፍሪካ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች ቁጥር ወደ 1.2 ሚሊዮን እየተቃረበ መሆኑን የአህጉሪቱ የበሽታ ቁጥጥር ተቋም (ሴንተር ፎር ዲዚዝ ኮንትሮል ኤንድ ፕሪቨንሽን) አስታወቀ።

    እስካሁን 28,014 ሰዎች ሕይወታቸው ሲያልፍ 922,833 ሰዎች ደግሞ ከበሽታው አገግመዋል።

    በቫይረሱ በተያዙ ሰዎች ቁጥር ደቡብ አፍሪካ የመጀመሪያውን ደረጃ ትይዛለች። በአገሪቱ 611,450 ሰዎች በበሽታው የተያዙ ሲሆን በተከታይነት ግብፅ (97,478)፣ ሞሮኮ (53,252)፣ናይጄሪያ (52,548)፣ ጋና (43,622)፣አልጄሪያ (42,302)፣ኢትዮጵያ (42,143) እና ኬንያ (32,803) ይገኛሉ።

    ደቡብ አፍሪካ በበሽታው ክፉኛ ጉዳት የደረሰባት ሲሆን፤ በቀጣይም ሰሜናዊ አፍሪካ፣ ምዕራባዊ አፍሪካ፣ ምሥራቅ አፍሪካ እና ማዕከላዊ አፍሪካ በቫይረሱ ሳቢያ ተጎድተዋል።

    የአፍሪካ የበሽታ ቁጥጥር ተቋም፤ አገራት ምርመራ በማካሄድ እንዲሁም በሽታው ከያዛቸው ጋር ንክኪ ያላቸውን ሰዎች በማግኘት ወረርሽኙን ለመቆጣጠር የሚያደርጉትን ጥረት እንዲያጠናክሩ አሳስቧል።

    ወረርሽኙ በአህጉሪቱ ላይ ያደረሰውን ጉዳት ለመረዳት ተቋሙ በቅርቡ የአንቲቦዲ ምርመራ ላይ ያተኮረ ጥናት መጀመሩ ይታወሳል።

  14. በደልሂ በቀን 40 ሺህ ሰዎች እየተመረመሩ ነው

    በሕንዷ መዲና ደልሂ በአንድ ቀን የሚመረመሩ ሰዎች 40 ሺህ መድረሳቸውን የጤና ኃላፊው አርቪድ ከጂዋል ገለጹ።

    በከተማዋ ባለፉት 24 ሰዓታት 1,500 ሰዎች ላይ ኮቪድ-19 ቢገኝም፤ ኃላፊው “ሁሉም ነገር በቁጥጥር ሥር ነው” ብለዋል።

    በመላው ሕንድ በአንድ ቀን 67,000 በቫይረሱ መያዛቸው ተገልጿል። ይህም በአጠቃላይ በሽታው የተገኘባቸውን ሰዎች ቁጥር 3.2 ሚሊዮን አድርሶታል።

    ሕንድ ከአሜሪካ እና ከብራዚል ቀጥሎ በቫይረሱ በተያዙ ሰዎች ቁጥር ከዓለም ሦስተኛዋ ናት። እስካሁን 59,449 ሰዎች ሕይወታቸውን አጥተዋል።

  15. ስፔን ኮሮናቫይረስን ለመቆጣጠር ወታደር ልታሰማራ ነው

    ስፔን ለኮሮናቫይረስ የተጋለጡ ሰዎችን ለመለየት እንዲያስችላት የጦር ሠራዊቷን ልታሰማራ እንደሆነ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ፔድሮ ሳንቼስ ተናገሩ።

    እነዚህ 2 ሺህ የሚደርሱት የሠራዊቱ አባላት ለወረርሽኝ ተጋላጭ የሆኑትን ለመለየት የሚያስችላቸውን ሥልጠና የወሰዱ ሲሆን ወደ ተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች እንደሚሰማሩም ተነግሯል።

    አንዳንድ የጤና ባለሙያዎች እንዳሉት ማድሪድንና ካታሎኒያን በመሳሰሉ አካባቢዎች በሽታው መልሶ እንዲያገረሽ ያደረገው ለበሽታው የተጋለጡና ንክኪ ያላቸውን ሰዎች ለመለየት በነበገ ችግር ነው።

    ስፔን ከ400 ሺህ በላይ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ያሉባት ሲሆን ይህም አገሪቱን በምዕራብ አውሮፓ ከሚገኙ አገራት በውስጥ ከፍተኛው ነው። እስካሁንም 29 ሺህ ሰዎች በወረርሽኙ ሳቢያ ሞተውባታል።

  16. በኢትዮጵያ 800 ሺህ የሚጠጋ ምርመራ ተደርጓል

    ኢትዮጵያ የመጀመሪያውን በኮሮናቫይረስ የተያዘ ሰው ካገኘች ስድስት ወር ሊሞላት የቀሯት ጥቂት ሳምንታት ናቸው።

    በእነዚህ ጊዜያቶች ውስጥ ወደ 800 ሺህ የሚጠጉ ናሙናዎች ላይ የኮቪድ-19 ምርመራ በማድረግ 43 ሺህ 688 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን አረጋግጣለች። ከእነዚህ መካከልም 709 ሰዎች ሞተዋል።

    ከበሽታው አገግመው ወደ መደበኛ ህይወታቸው የተመለሱ ሰዎችም ቁጥር ወደ 16 ሺህ እየተጠጋ ነው።

    ቢሆንም በተለይ እንደ አዲስ አበባ ባሉ ከተሞች በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በፍጥነት እየጨመረ ይገኛል። በተለይ ከቅርብ ወራት ወዲህ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በፍጥነት እየጨመረ ይገኛል።

    በርካታ የሕክምና ባለሙያዎች የሕብረተሰቡ መዘናጋት ለቫይረሱ እያጋለጠ መሆኑን በመጥቀስ ስርጭቱን ባለበት ለማቆም መከላከያዎቹን ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን ይናገራሉ።

    አካላዊ ርቀትን መጠበቅ፣ እጅን ደጋግሞ በሳሙና መታጠብ፣ እንዲሁም የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ በሽታወን ለመከላከል ወሳኝ ናቸው።

  17. በኢትዮጵያ በዛሬው ዕለት በቫይረሱ የ17 ሰዎች ሕይወት አለፈ

    በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓታት በተደረጉ 18 ሺህ 778 የላብራቶሪ ምርመራዎች 1 ሺህ 545 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን የጤና ሚኒስቴርና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም በዕለታዊ መግለጫቸው አስታወቁ። ይህም አጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 43 ሺህ 688 አድርሶታል።

    ባለፉት 24 ሰዓታትም የ17 ሰዎች ሕይወት ሲያልፍ ፤ በአጠቃላይ 709 ሰዎች በበሽታው መሞታቸውን መግለጫው አመልክቷል።

    በሌላ በኩል ተጨማሪ 534 ሰዎች ከበሽታው ማገገማቸው ተገልጿል። እስካሁንም 15 ሺህ 796 ሰዎች ከበሽታው አገግመዋል።

    በኢትዮጵያ የበሽታው ሥርጭት እየተስፋፋ ሲሆን በበሽታው ተይዘው ፅኑ ሕክምና ክፍል የሚገቡ ህሙማንም ቁጥር እየጨመረ ነው። አሁንም 290 ሰዎች በጽኑ መታመማቸውን መግለጫው ጠቅሷል።

  18. በአላባማ ዩኒቨርሲቲ በአንድ ሳምንት ከ500 በላይ ሰዎች በቫይረሱ ተያዙ

    በአሜሪካ የሚገኘው አላባማ ዩኒቨርሲቲ ባለፈው ሳምንት ትምህርት ከጀመረ ወዲህ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተገለፀ።

    የዩኒቨርሲቲው ባለሥልጣናት እንደተናገሩት ከተማሪዎችና ከሰራተኞች ውስጥ በአጠቃላይ 566 በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ተገኝተዋል።

    ሁኔታውን በተመለከተ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚደንት ስቱዘርት ቤል “የእኛ ተግዳሮት ተማሪዎች አይደሉም። የእኛ ፈተና ቫይረሱ ነው። አሁን ማድረግ ያለብን ቫይረሱ ከየት እንደተነሳና ወዴት እየተሰራጨ እንደሆነ መለየት እንዲሁም አደጋውን ለመቀነስ ከተማሪዎቻችን፣ ከትምህርት ክፍሎቻችን እና ከሰራተኞቻችን ጋር እንዴት አብረን እንደምንሰራ መለየት ነው” ማለታቸውን የአገሪቷ መገናኛ ብዙኃን እርሳቸውን ጠቅሶ ዘግቧል።

    ፕሬዚደንቱ አክለውም በዩኒቨርሲቲው በቫይረሱ ለተያዙ ወይም ለቫይረሱ ለተጋለጡ ተማሪዎች ለይቶ ማቆያነት ቀድሞ ከተዘጋጀው 450 አልጋዎች በተጨማሪ ሌላ ለመጨመር እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል።

    ከመጋቢት ወር ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ ባለፈው ሳምንት ከ20 ሺህ በላይ ተማሪዎች ለገፅ ለገፅ ትምህርት ወደ ዩኒቨርሲቲው ተመልሰዋል።

  19. በአንጎላ የኮቪድ ሕግን በማስፈፀም ሒደት ሰባት ታዳጊዎች መገደላቸው ተገለፀ

    በአንጎላ የፀጥታ ኃይሎች የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመግታት የተጣሉ ገደቦችን ሲያስፈፅሙ ከግንቦት እስከ ሐምሌ ባሉት ወራት ብቻ ቢያንስ 7 ታዳጊዎች መገደላቸው ተገለፀ።

    ከሟቾቹ መካከል በዕድሜ ትንሹ የ14 ዓመት ታዳጊው ማሪዮ ፓልማ ሲሆን፤ የተገደለው ለእናቱ ስኳር ለመግዛት ወደ ሱቅ በወጣበት ነው ተብሏል።

    ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች አምነስቲ ኢንተርናሽናል የምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ ዳሬክተር ዲፕሮሴ ሙቸና “አንድ ታዳጊ ፊቱ ላይ በጥይት የተመታ ሲሆን፤ ሌላኛው ደግሞ ፖሊስ በስፖርት ሜዳ ላይ ልምምድ ሲያደርጉ የነበሩ ጓደኛሞች ላይ ሲተኩስ ተገድሏል” ሲሉ አስረድተዋል።

    አምነስቲ ባወጣው መግለጫ በአንድ ሌላ አደጋም፤ የቀደመ የጤና ችግር እንደነበረበት የተነገረው ታዳጊ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ አልለበስክም በሚል መንገድ ላይ በፖሊስ እንዲቆም ተደርጎ በቅጣት ስፖርት እንዲሰራ ይታዘዛል። ልጁም የታዘዘውን አልተገብርም በማለቱ ፖሊስ ጭንቅላቱ ላይ እንደተኮሰበት ያትታል።

    ወደ ሆስፒታል ቢወሰድም ሊተርፍ አልቻለም። ጎረቤቶቹ እንዳሉት ታዳጊው የልብ ሕመም እና የደም ግፊት ችግር እንደነበረበት የተናገሩ ሲሆን የሕክምና ውጤቱ ግን ገና አልተገለፀም።

    ምርመራውን ያካሄደው ከቤተሰብና ከጓደኞች ያገኘውን መረጃ በማጠናቀር እንደሆነ ያስታወቀው ድርጅቱ፤ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለሰብዓዊ መብት ጥሰት ምክንያት ሊሆን አይችልም ብሏል።

    ሁሉም ግድያዎች የተፈፀሙት በዋና መዲናዋ ሉአንዳ አቅርቢያ ነው ተብሏል።

    የአንጎላ ብሔራዊ ፖሊስ እና የአንጎላ ታጣቂ ኃይሎች መኮንኖች በግድያው እጃቸው እንዳለበት የተጠረጠሩ ሲሆን የአገሪቷን ባለሥልጣናት እያደረጉት ያለውን ምርመራ ገለልተኛ፣ ፈጣንና እና ከአድሎ ነፃ እንዲሆን ድርጅቱ አሳስቧል።

    በሰብዓዊ መብት ጥሰትና ጥቃት እጃቸው አለበት ተብለው የተጠረጠሩት ተጠያቂ እንዲሆኑና ለሟች ቤተሰቦች ፍትህ እና ካሳ እንዲሰጥ አምነስቲ ጥሪ አቅርቧል።

  20. በደቡብ አፍሪካ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየቀነሰ ነው

    በሐምሌ ወር በአንድ ቀን 15 ሺህ ሰዎች በቫይረሱ ይያዙባት የነበረችው ደቡብ አፍሪካ ባለፉት 24 ሰዓታት የመዘገበችው ከ1 ሺህ 600 በላይ ነው።

    ባለሙያዎችም በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በተከታታይ እየቀነሰ መሆኑን መረጃዎች እንደሚያሳዩ ጠቅሰው፤ በአገር አቀፍ ደረጃ ተጥሎ የነበረው የእንቅስቃሴ ገደብ በላላበት ሁኔታ እስካሁን 'የሁለተኛ ዙር ወረርሽኝ' ምልክት አለመኖሩን ተናግረዋል።

    ይሁን እንጅ የሁለተኛ ዙር ወረርሽኝ አደጋ እንዳለ በመግለፅ፤ ሰዎች የጥንቃቄ መመሪያዎችን እንዲተገብሩ አስጠንቅቀዋል።

    በአገሪቷ በትናንትናው እለት 100 ሰዎች በቫይረሱ ሳቢያ ሕይወታቸው አልፏል። ይህም አጠቃላይ የሟቾቹን ቁጥር ከ13 ሺህ በላይ አድርሶታል።

    ከበሽታው የሚያገግሙ ሰዎች ቁጥር ደግሞ ከ80 በመቶ በላይ ጨምሯል።