
የፎቶው ባለመብት, Reuters
የዩናይትድ ኪንግደም መንግሥት ከስፔን የሚገቡ
ተጓዦች ለሁለት ሳምንታት በለይቶ ማቆያ እንዲቆዩ የጣለው ገደብ ፍትሃዊ አለመሆኑን የስፔን ጠቅላይ ሚኒስተር ተናገሩ።
ጠቅላይ ሚኒስተር ፔድሮ ሳንቼዝ በአብዛኛው የስፔን አካባቢዎች ያሉ
ጎብኝዎች ከዩኬ በተሻለ ከኮሮናቫይረስ የተጠበቁ ሊሆኑ ይችላሉ በማለት አገሪቷ ውሳኔዋን መልሳ እንደምታስብበት ተስፋ አድርገው
እንደነበር ገልፀዋል።
ነገር ግን የዩናይትድ ኪንግደም መንግሥት ውሳኔውን
የመለወጥ እቅድ እንደሌለው አስታውቋል። የጠቅላይ ሚኒስተር ቦሪስ ጆንሰን ቃል አቀባይ በዚህ ወረርሽኝ ወቅት ‘ማንኛውም ጉዞ
ከአደጋ ነፃ አይደለም’ ሲሉ አስጠንቅቀዋል።
ሰኞ ዕለት የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት፤ ሰዎች አስገዳጅ ካልሆነ በስተቀር ወደ ካናሪይ እና ባሌሪክ
ደሴቶች፤ እንዲሁም ወደ ስፔን ጉዞ እንዳያደርጉ መክረዋል።
ከስፔን ቴሌሲንኮ ቴሌቪዥን ኔትወርክ ጋር ቃለ ምልልስ
ያደረጉት ጠቅላይ ሚኒስተር ፔድሮ፤ የዩኬ መንግሥት ስፔን የለይቶ ማቆያ ሕጉ ከሚመለከታቸው አገራት ዝርዝር ውስጥ ያወጧታል ብለው ተስፋ አድርገው እንደነበር
እና አሁንም ከመንግሥት ጋር እየተነጋገሩ መሆኑን ገልፀዋል።
64.5 በመቶ የሆነው አዲስ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች የተመዘገቡት በሁለት ግዛቶች
ብቻ መሆኑን በመግለፅም ዩኬ የወረርሽኙን ሥርጭት የጨመረው በመላ አገሪቷ እንደሆነ በማሰብ ‘ስህተት’ ሰርታለች ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።
እንደ የአውሮፓ በሽታ መከላከያና መቆጣጠሪያ ማዕከል
በስፔን የቫይረሱ ሥርጭት ከ100 ሺህ ሰዎች 35.1 ሲሆን በዩናይትድ ኪንግደም ግን ይህ አሃዝ 14.7 ነው።
ሆኖም ወረርሽኙ በአብዛኛው የስፔን አካባቢዎች በቁጥጥር
ሥር የዋለ ሲሆን፤ አንዳንድ አካባቢዎች በተለይ በሰሜን ምስራቋ ካታሎኒያ እና ጎረቤቷ አራጎን ግን የወረርሽኙ ሥርጭት በከፍተኛ ሁኔታ
እየጨመረ ነው።