በኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ወደ 16 ሺህ እየተጠጋ ነው

በኢትዮጵያ የኮሮናቫይረስ የማህበረሰብ ስርጭት በፍጥነት እየተስፋፋ ነው። በዛሬው ዕለት ቫይረሱ እንዳለባቸው በምርመራ የተረጋገጠውን 610 ሰዎች ጨምሮ በአጠቃላይ በአገሪቱ በቫይረሱ መያዛቸው የታወቀው ሰዎች ቁጥር ወደ 16 ሺህ እየተጠጋ ነው። ። ቫይረሱ በስፋት እየተሰራጨ ካለባች ከተሞች ደግሞ ቀዳሚውን የምትይዘው ዋና መዲናዋ አዲስ አበባ ስትሆን፣ እስከ አሁን በዋና መዲናዋ ብቻ 10ሺህ 703 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ታውቋል። ከአዲስ አበባም ኮቪድ-19 ይበልጥ እየተሰራጨባቸው የሚገኙት ክፍለ ከተሞች ቦሌ (1652 ሰዎች)፣ አዲስ ከተማ (1329 ሰዎች) እንዲሁም ጉለሌ (1308 ሰዎች) ናቸው። የሕክምና ባለሙያዎች በተደጋጋሚ እንደሚሉት በህብረተሰቡ ዘንድ የሚታየው ቸልተኝነት ለወረርሽኙ በስፋት መሰራጨት አስተዋጽኦ አድርጓል። እናም አሁንም ቢሆን አካላዊ ርቀትን መጠበቅ፣ ማስክ ማድረግና እጅን መታጠብ ላይ መዘናጋት ዋጋ ያስከፍላል።

የቀጥታ ሽፋን

  1. የአንድ ክለብ አባል የሆኑ 15 እግር ኳስ ተጫዋቾች በኮሮናቫይረስ ተያዙ

    እጅ የሚታጠብ ሰው

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, የክለቡ መሪ ተጨዋቾችና ደጋፊዎች የእጃቸውን ንፅህና እንዲጠብቁ አሳስበዋል

    በዛምቢያ ፕሪሚየር ሊግ የናፕሳ ሰታርስ ክለብ 15 ተጫዋቾችና አራት ኃላፊዎች በአጠቃላይ 19 የክለቡ አባላት በኮሮናቫይረስ መያዛቸውን የክለቡ ቃል አቀባይ አስታወቁ ።

    ከሁለት ሳምንት በፊት የፎረስት ሬንጀርስ ክለብ 28 ተጨዋቾችና ባለሥልጣናት በቫይረሱ መያዛቸውን የሚታወስ ሲሆን ይህ ለሁለተኛ ጊዜ ያጋጠመ ነው ተብሏል።

    የናፕሳ ስታር ክለብ አስራ አምስት ተጫዋቾችና አራት ባለሥልጣናት በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠው በተደረገ መደበኛ ምርመራ እንደሆነ የክለቡ ቃል አቀባይ ግዌን ቺፓሱላ በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል።

    በቫይረሱ የተያዙት ተጨዋቾችና ባለሥልጣናት በጤና ሚኒስቴር መመሪያ መሰረት ወደ ለይቶ ማቆያ መግባታቸውን ቃል አቀባይዋ ተናግረዋል።

    ቃል አቀባይዋ በተጨማሪ የቫይረሱን ሥርጭት ለመግታት፤ ግለሰቦቹ ላይ የቅርብ ክትትል እየተደረገ መሆኑን ለማረጋገጥ ክለቡ ከጤና ሚኒስቴር ጋር እየተነጋገረ መሆኑን አክለዋል።

    ቀሪው የቡድኑ አባላትም ለሚመጡት ጨዋታዎች ዝግጅታቸውን መቀጠላቸውን ተናግረዋል።

    የክለቡ መሪ ግሬግ ቾላ ሶፉ በበኩላቸው “ ተጫዋቾቻችንን፣ ደጋፊዎቻችንን እንዲሁም አጠቃላይ የእግር ኳስ አፍቃሪዎችን የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግን ፣ አካላዊ ርቀት መጠበቅን እና የእጅ ማፅጃ ፀረ- ተሕዋስ መጠቀምን ጨምሮ ሌሎች የጥንቃቄ እርምጃዎችን እንዲወስዱ እጠይቃለሁ” ሲሉ ጥንቃቄ እንዳይለያቸው አሳስበዋል።

    በዛምቢያ እስካሁን 4 ሺህ 481 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን 139 ሰዎች ደግሞ በበሽታው ሳቢያ ሕይወታቸው አልፏል።

  2. በኢትዮጵያ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 15 ሺህ 810 ደረሰ

    ግራፊክስ

    በዛሬው ዕለት በኢትዮጵያ ለ7760 ሰዎች በተደረገው የላብራቶሪ ምርመራ 610 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል። በዚህም መሰረት በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 15 ሺህ 810 መድረሱን ከጤና ሚኒስቴር ዕለታዊ መግለጫ መረዳት ተችሏል።

    ከእነዚህ መካከል 465 ከአዲስ አበባ፣ 21 ከትግራይ፣ 53 ከኦሮሚያ ፣ 10 ከሲዳማ፣ 14 ከደቡብ፣ 4 ከአፋር፣ 11 ከጋምቤላ፣ 6 ከአማራ፣ 6 ከድሬዳዋ፣ 5 ከሃረሪ እና 15 ከሶማሌ የተገኙ መሆናቸው ተገልጿል።

    በዛሬው ዕለት 14 ሰዎች በኮሮናቫይረስ ምክንያት ህይወታቸው ማለፉን ተከትሎ አገሪቱ በቫይረሱ ያጣቻቸው ዜጎችንም ቁጥር 253 አድርሶታል።

    ከዚህም በተጨማሪ 159 ሰዎች ማገገማቸውን መግለጫው ያመላከተ ሲሆን በአጠቃላይ ያገገሙ ሰዎች ቁጥርም 6ሺህ 685 ደርሷል።

    በኢትዮጵያ አጠቃላይ የተከናወኑ የላብራቶሪ ምርመራዎችም 403 ሺህ 611 መሆኑም ተገልጿል።

  3. የፈረንሳይ ፖሊስ በኮቪድ-19 ፍራቻ 1500 ስደተኞችን ከመኖሪያቸው አነሳ

    የፈረንሳይ ፖሊስ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በሰሜን ምስራቅ ፓሪስ የፈረንሳይ ፖሊስ በብዛት ከአፍሪካ ቀንድና ከአፍጋኒስታን የሄዱ 1500 የሚሆኑ ስደተኞችን በኮቪድ-19 ፍራቻ ከመኖሪያ ካምፕ ማስወጣቱን አስታውቋል።

    ስደተኞቹ ከአንድ ግድብ አጠገብ ድንኳኖች ውስጥ ነበር የሚኖሩት።

    ስደተⶉቹ በስፖርት ማዘውተሪያዎች፣ ሆቴሎችና መጠለያዎች ለመሄድ ወደ መኪናዎች ውስጥ ሲጫኑ ሁሉም የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማስክ አድርገው ነበር ተብሏል።

    ባለሥልጣናት ስደተኞቹ የሚኖሩበት ሁኔታ ለኮሮናቫይረስ ስርጭት በከፍተኛ ሁኔታ ተጋላጭ እንደሆነ አስታውቀዋል።

    አንዳንድ የበጎ አድራጎት ሰራተኞችን ግን ስደተኞቹ በእጅጉ ተዳክመዋል፤ አንዳንዶቹ እስከ 10 ጊዜ ከአንድ ካምፕ ወደ ሌላ ሲዘዋወሩ ነበር ብለዋል።

    አንዲት ከሶማሊያ የመጣች ስደተኛ 'ኤኤፍፒ' ለተባለው የዜና ወኪል ስትናገር ያሉበት ሁኔታ አስቸጋሪ መሆኑን ገልጻለች።

    '' ላለፉት ሶስት ወራት ሆቴል ውስጥ ነበር የቆየነው፤ ከዛ በኋላ ግን መልሰው መንገድ ላይ አውጥተው ጣሉን'' ብላለች።

  4. ካሜራ አምራቹ ኮዳክ ወረርሽኙን ለመዋጋት መድሃኒት ወደ ማምረት ገባ

  5. በዚምባብዌ ሆስፒታል በአንድ ምሽት ሰባት አራስ ሕፃናት መሞታቸው ተነገረ

  6. ሶማሊያዊው ጋዜጠኛ በኮቪድ-19 ፅሁፉ ለእስር ተዳረገ

    ጭምብል ያጠለቁ ታዳጊዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በሶማሊያ የሚገኝ ፍርድ ቤት ጋዜጠኛ አብዲያዚዝ አህመድ ጉርቢየ መንግሥት የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን አስመልክቶ እየሰጠ ያለውን ምላሽ አስመልክቶ በመተቸት ፌስቡክ ላይ በመፃፉ ጥፋተኛ ሆኖ አግኝቶታል።

    የስድስት ወር እስርም ፈርዶበታል።

    አብዲያዚዝ በመዲናዋ ሞቃዲሾ መቀመጫውን ያደረገው ጉብጆግ ሚዲያ ግሩፕ የተባለው ጋዜጣ ዋና አዘጋጅና ምክትል ዳይሬክተር ነው።

    ሃሰተኛ መረጃን በማሰራጨት፣ አስተዳደሩንና የፍትህ ስርአቱን በመስደብ ወንጀልም ነው የተከሰሰው።

    ጋዜጠኛው ወደ ሞቃዲሾ ማዕከላዊ እስር ቤትም ተዛውሯል።

    ጠበቆቹ በበኩላቸው ፍርድ ቤቱ ክሱን መሰረት ያደረገው ጊዜው ባለፈበት የወንጀል መቅጫ ነው በማለት ተከራክረዋል።

    ሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ ድርጅት ሂውማን ራይትስ ዋችና የጋዜጠኞችን መብት ለማስከበር እሰራለሁ የሚለው ሲፒጄ የፍርድ ሂደቱን በመቃወም አውግዘዋል።

    ለወራት ሲካሄድ የነበረው የፍርድ ሂደት በሶማሊያ ውስጥ ከፍተኛ ቀልብን የሳበም ነበር ተብሏል።

  7. በቬትናም ከሦስት ወር በኋላ ኮቪድ-19 ማገርሸቱ ተገለጸ

    የቬትናም መንግሥት በመላ አገሪቱ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሊስፋፋ እንደሚችል አስጠነቀቀ።

    ቬትናም ላለፉት ሦስት ወራት አንድም በኮቪድ-19 የተያዘ ሰው ያልነበረባት ሲሆን፤ አሁን ግን 30 አዲስ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን በምርምራ አግኝታለች። ሁሉም በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ከማዕከላዊ የወደብ መዝናኛ ከተማዋ ዳ ናንግ ጋር የተገናኙ ናቸው ተብሏል።

    ዳ ናንግ ከዚህ ሳምንት መጀመሪያ አንስቶ ለጎብኚዎች ዝግ የሆነች ሲሆን፤ ሁሉም ነዋሪዎች ከእንቅስቃሴ ታቅበው ቤታቸው እንዲቀመጡ ታዝዟል።

    በወደብ ከተማዋ ተገኝተው የነበሩትን ፈልጎ በማግኘት፣ ራሳቸውን እንዲለዩ እንዲደረግ የአካባቢው ባለስልጣናት ታዘዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዡዋን ፉክ ረቡዕ እለት እንዳሉት፤ በአገሪቱ ውስጥ የሚገኙ ሁሉም ግዛቶችና ከተሞች ውስጥ ወረርሽኙ ከፍተኛ የመስፋፋት እድል አለው። “በቁጥጥር ስር ለማዋል በፍጥነትና በቅልጥፍና እርምጃ እንወስዳለን” ማለታቸው በአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኀን ተዘግቧል።

    ለመንግሥት ባለስልጣናትም የቫይረሱ ዝርያ ቀድሞ በቬትናም ተከስቶ ከነበረው እንደሚለይ በመናገር፤ በመላው አገሪቱ የቱሪስት መዳረሻዎች በአጠቃላይ ከፍተኛ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ አሳስበዋል።

    የጤና ሚኒስትሩ ረቡዕ እለት እንዳሉ፤ ስምንት በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ከዳ ናንግ ጋር የሚገናኙ ሲሆን፤ በዋና ከተማዋ ሃኖይም ከከተማዋ ጋር ግንኙነት የነበራቸው በርካቶች በቫይረሱ ተይዘዋል።

    በመላ አገሪቱ የሚገኙ ሆስፒታሎች የመከላከል እርምጃዎቻቸውን ያጠበቁ ሲሆን፣ በዋና ከተማዋ ሃኖይ ደግሞ ሕዝብ በሚሰበሰብበት ስፍራ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል ማድረግ ግዴታ መሆኑ ተገልጿል።

    ባለስልጣናት በሳምንቱ መጨረሻ ላይ በዳ ናንግ 80 ሺህ ያህል የአገር ውስጥ ቱሪስቶች እንደነበሩ ገልጸው፣ ኮቪድ-19 መከሰቱ እንደተሰማ ሁሉም ወደ የመጡበት እንዲሄዱ ተደርጓል።

    ቬትናም

    የፎቶው ባለመብት, EPA

  8. ማዶና ስለ ኮቪድ-19 ክትባት ሐሰተኛ መረጃ በማሰራጨቷ ተተቸች

    ማዶና በኢንስታግራም ገጿ ስለ ኮሮናቫይረስ ሐሰተኛ የሴራ ትንተና አሰራጭታለች ተባለ።

    ድምጻዊቷ የኮሮናቫይረስ ክትባት እንደተገኘና “ሀብታሞችን የበለጠ ለማበልጸግ” ሲባል እንደተደበቀ የሚተነትን ተንቀሳቃሽ ምስል በገጿ አጋርታለች።

    ቪድዩውን የአሜሪካው ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕም ሲሞካሹት ነበር።

    ኢንስታግራም፤ ማዶና ያጋራችውን ቪድዮ አደብዝዞ፤ “ሐሰተኛ መረጃ” የሚል ማሳሳቢያ ለጥፎበታል። ለኢንስታግራም ተጠቃሚዎች አሁን ላይ ለበሽታው ክትባት አለመገኘቱን የሚያስረዳ ድረ ገጽም ተያይዞ ቀርቧል።

    አሁን ተንቀሳቃሽ ምስሉ ከማዶና ገጽ ላይ ቢጠፋም፤ ሐሰተኛ መረጃ በማሰራጨቷ ተከታዮቿ ተችተዋታል።

    ማዶናን ከተቹ አንዷ ድምጻዊት አኒ ለኖክስ፤ “ይሄ ጤናማ አይደለም። ይህን አደገኛ የሐሰት ትንተና ማጋራትሽን ማመን ይከብደኛል። የኢንስታግራም ገጽሽን የበይነ መረብ ሰርሳሪዎች ጠልፈውት ነው ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ” ብላለች።

    ማዶና

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ማዶና
  9. በቫይረሱ የሚያዙ የአውሮፓ ወጣቶች ቁጥር መጨመሩ ተገለጸ

    የዓለም ጤና ድርጅት የአውሮፓ ቅንጫፍ ኃላፊ ዶ/ር ሀንስ ክሊግ፤ በአውሮፓ በቫይረሱ የሚያዙ ወጣቶች ቁጥር እየጨመረ ነው አሉ።

    የመንግሥት ባለሥልጣኖች በተሻለ ሁኔታ ለወጣቱ ማኅበረሰብ መረጃ ማድረስ እንዳለባቸውም ለቢቢሲ ገልጸዋል።

    “በብዙ አገሮች በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው። ከጤና ዘርፍ ኃላፊዎች ባገኘነው መረጃ መሠረት በዋነኛነት እየተጠቁ ያሉት ወጣቶች ናቸው። ስለዚህም ከወጣቱ ጋር መነጋገር ያስፈልጋል” ብለዋል።

    የሁለት ወጣቶች አባቱ ዶ/ር ሀንስ፤ ወጣቶች የበጋ ሽርሽር እንዲያመልጣቸው እንደማይፈልጉ እረዳለሁ ብለዋል።

    ሆኖም ግን “ስለ ራሳቸው ብቻ ሳይሆን ስለ ወላጆቻቸው፣ ስለ አያቶቻቸው እና ስለ ማኅበረሰቡም ኃላፊነት ስላለባቸው ጤናማ ሕይወት የሚመሩበትን መንገድ መከተል አለባቸው” ሲሉ አሳስበዋል።

    ወጣቶች

    የፎቶው ባለመብት, EPA

  10. ዩኬ 60 ሚሊዮን ክትባት እንዲመረት አዘዘች

    የዩናይትድ ኪንግደም መንግሥት 60 ሚሊዮን ክትባት እንዲመረት ከስምምነት ደርሷል። ይህ ክትባት ተስፋ ሰጪ ከተባሉ የክትባት አይነቶች አራተኛው ነው።

    የሚመረተው ክትባት ለሙከራ ሕክምና የሚውል ይሆናል። አምራቾቹ ጄኤስኬ እና ሳንፎኒ የተባሉ ትልልቅ የመድኃኒት ድርጅቶች ናቸው።

    ሙከራው ውጤታማ ከሆነ ክትባቱ በቀጣዩ ዓመት የመጀመሪያው አጋማሽ ፍቃድ እንደሚያገኝ ይጠበቃል።

    መንግሥት በኦክስፎርድ ዩኒቨርስቲ እየተሠራ ያለው ክትባት 100 ሚሊዮን እንዲመረት መስማማቱ ይታወሳል።

    90 ሚሊዮን ያህል ሌሎች ሁለት ተስፋ ሰጪ ክትባቶች እንዲመረቱም ተስማምቷል።

    ተስፋ ከተጣለባቸው ክትባቶች መካከል የትኛው ውጤታማ እንደሚሆን እስካሁን የታወቀ ነገር የለም።

    ክትባት

    የፎቶው ባለመብት, PA Media

  11. የቤላሩስ ፕሬዘዳንት ኮሮናቫይረስን ‘ድል ነሳሁት’ አሉ

    የቤላሩስ ፕሬዘዳንት አሌክሳንደር ሊካሽንኮ ከኮሮናቫይረስ ማገገማቸውን ተናገሩ።

    ፕሬዘዳንቱ ምንም አይነት የበሽታውን ምልክት እንደማያሳዩ ከሀኪሞች እንደተነገራቸው ለመከላከያ ኃላፊዎች ተናግረዋል።

    አያይዘውም “97 በመቶ የሚሆነው ሕዝባችን ምልክት ባያሳይም ቫይረሱ አለበት” ያሉት ምንም ማስረጃ ሳያቀርቡ ነው።

    ጆንስ ሆፕኪንስ ዩኒቨርስቲ እንዳለው፤ በአገሪቱ 67,366 ሰዎች በቫይረሱ ሲያዙ 543 ሞተዋል።

    የአውሮፓ አገራት የበሽታውን ስርጭት ለመግታት ድንበር ሲዘጉ ቤላሩስ ምንም እርምጃ አልወሰደችም። እንዲያውም የእግር ኳስ ውድድር እንዳይቋረጥ ተወስኖ ነበር።

    ከጎርጎሮሳውያኑ 1994 ወዲህ ስልጣን ያሉት ፕሬዘዳንቱ፤ ‘የአውሮፓ የመጨረሻው አምባገነን መሪ’ ተብለው ይጠራሉ።

    ኮሮናቫይረስን መፍራትን ከሥነ ልቦና ችግር ጋር አይይዘው መግለጻቸውን ተከትሎ፤ በርካቶች ለተቃውሞ አደባባይ ወጥተው ነበር። ተቃዋሚዎቹን ፖሊስ አስሯቸዋል።

    አሌክሳንደር ሊካሽንኮ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, አሌክሳንደር ሊካሽንኮ
  12. የኮቪድ-19 ተጋላጭነት ከዘር ጋር ያለው ትስስር ሊጠና ነው

    በዩናይትድ ኪንግደም አነስተኛ የሚባሉ የዘር ግንዶች አባላት ለኮቪድ-19 በስፋት ስለሚጋለጡበት ምክንያት ጥናት ሊካሄድ ነው።

    ሳይንቲስቶች ለሚያካሂዱት ምርምር መንግሥት በሚሊዮኖች የሚቆጠር ፓውንድ እመድባለሁ ብሏል።

    በዘረ መል አማካይነት ለበሽታው የመጋለጥ እድልን፣ ማኅበራዊ ሁኔታን፣ የእለት ከእለት እንቅስቃሴን እንዲሁም ጤናን በተመለከተ የሚሰበሰበው መረጃ በስድስት ፕሮጀክቶች ይዳሰሳል።

    ከጥናቶቹ አንዱ ለዓመት 30 ሺህ ሰዎች ላይ ያተኩራል።

    አጥኚዎቹ እንደሚሉት፤ የምርምሩን ግኝት ተከትሎ አፋጣኝ እርምጃዎች ይወሰዳሉ።

    በሦስት ጥናቶች የሚሳተፉት፣ በሌስተር ዩኒቨርስቲ የሚሠሩት ፕ/ር ካምሊሽ ኩሁንቲ፤ የጥናቱ ግኝት ጥቁሮችና እስያውያንን ጨምሮ የሌሎችንም ሕይወት ይታደጋል ብለው እንደሚያምኑ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    ገበያ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

  13. "ሃይድሮክሲሎሮኩዊንን እያጣጣላችሁት ያላችሁት እኔ ጥሩ ነው ስላልኩ ነው" ዶናልድ ትራምፕ

  14. በሙምባይ የተጨናነቁ መንደሮች ከሚኖሩት ገሚሱ በኮቪድ-19 ተይዘው ነበር

    በሕንድ፣ ሙምባይ በሚገኙ የተጨናነቁ መንደሮች ውስጥ ከሚኖሩ ሰዎች ከግማሽ በላዩ ሲመረመሩ የኮሮናቫይረስ ቅንጣቶች እንደተገኙባቸው አንድ ጥናት አሳየ።

    ከነዚህ የተጨናነቁ መንደሮች ውጪ ካሉ ነዋሪዎች ለበሽታው ተጋላጭነት ያላቸው 16 በመቶው ብቻ እንደሆኑ ጥናቱ አሳይቷል።

    ጥናቱ የ7,000 ሰዎችን የምርመራ ውጤት የተመረኮዘ ነው። ግለሰቦቹ እጅግ በተጨናነቁ ሦስት መንደሮች ይኖራሉ።

    በሙምባይ ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎችከ110,000 በላይ ሲሆኑ፤ 6,187 ሰዎች ሞተዋል።

    የተጨናነቁ መንደሮች
  15. ከኮቪድ-19 ያገገሙት የብራዚሉ ፕሬዘዳንት ከደጋፊዎቻቸው ጋር ተገናኝተዋል

    ከጥቂት ቀናት በፊት ከኮቪድ-19 ያገገሙት የብራዚሉ ፕሬዘዳንት ዣቪር ቦልሶናሮ ደጋፊዎቻቸው በተሰበሰቡበት የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብላቸውን አውልቀዋል።

    ፕሬዘዳንቱ ጭምብላቸውን ያወለቁት ደጋፊዎቻቸውን በብራዚሊያ ከተማ በሰበሰቡበት ወቅት ነበር።

    ሐምሌ 7 በኮሮናቫይረስ እንደተያዙ የተናገሩት ቦልሶናሮ፤ ከሁለት ሳምንታት በኋላ ግን አገግመው፣ ውጤታቸው ከቫይረሱ ነፃ መሆኑን ተናግረዋል።

    ፕሬዘዳንቱ በሽታው እምብዛም የከፋ አይደለም በማለትና ሀይድሮክሲክሎሮክዊን ለህሙማን እንዲሰጥ በማበረታታት ይታወቃሉ።

    ከላቲን አሜሪካ መሪዎች ከቫይረሱ ያገገሙት እሳቸው ብቻ ናቸው።

    ዣቪር ቦልሶናሮ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, ዣቪር ቦልሶናሮ
  16. በሆንግ ኮንግ ታማሚዎች ከሆስፒታሎች አቅም በላይ ሊሆኑ ነው

    የሆንግ ኮንግ መሪ ካሪ ላም፤ በኮሮናቫይረስ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በመናሩ የተነሳ፤ ከከተማዋ ሆስፒታሎች አቅም በላይ ሊሆን እንደሚችል ተናገሩ።

    በሽታው በከተማዋ ማሕበረሰብ ዘንድ በስፋት ሊሰራጭ ስለሚችል ሰዎች ከቤታቸው እንዳይወጡም ኃላፊቷ አሳስበዋል።

    የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል ማድረግ ግዴታ ሲሆን፤ ምግብ ቤቶች መስተንግዶ እንዲያቆሙም ውሳኔ ተላልፏል።

    ወረርሽኙ መሰራጨት በጀመረበት ወቅት በሽታውን በመቆጣጠር ረገድ ስኬታማ ሆና የነበረው ሆንክ ኮንግ፤ አሁን ላይ በየቀኑ ወደ 100 ሰዎች ገደማ በኮቪድ-19 እንደተያዙ ሪፖረት እያደረገች ነው።

    ከአንድ ወር በፊት በአማካይ በአንድ ቀን በበሽታው የሚያዙ ሰዎች 10 ነበሩ።

    ካሪ ላም

    የፎቶው ባለመብት, GETTY IMAGES

    የምስሉ መግለጫ, ካሪ ላም
  17. እንደምን አደራችሁ?

    የቢቢሲ አማርኛ ወዳጆች እንደምን አደራችሁ? የቀጥታ ዘገባ ገጻችን ተጀምሯል።

    በአገራችን በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ15 ሺህ አልፏል።

    በሽታው በከፍተኛ ደረጃ አየተሰራጨ ስለሆነ ራሳችሁን እንዲሁም ቤተሰባችሁን ከኮቪድ-19 ለመከላከል የጥንቃቄ እርምጃዎችን እንድትትገብሩ እናሳስባለን።

    ከቻላችሁ ከቤት አትውጡ፣ ከወጣችሁም አካላዊ ርቀት ጠብቁ። የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል አድርጉ፤ እጃችሁንም በውሃና ሳሙና አዘውትራችሁ ታጠቡ።

    መልካም ቀን!

    ኮቪድ-19

    የፎቶው ባለመብት, AMANUEL SILESHI

  18. በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በኮሮናቫይረስ ወቅት ክብደት ጨምረዋል ተባለ

    በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ቤት ተሰብስበው ተቀምጠው ሳሉ ክብደት መጨመርዎ ከተሰማዎ ብቻዎን አይደሉም።

    ተመራማሪዎች በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በዚህ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ወቅት ክብደታቸው መጨመሩን ደርሰንበታል ብለዋል።

    450 ሺህ ሰዎች የኮቪድ-19 ምልክቶችን በሚለየው መተግበሪያ ላይ እንዳስቀመጡት መረጃ ከሆነ ክብደታቸው ጨምሯል። ከመተግበሪያው ላይ በተገኘው በዚህ መረጃ መሰረት በጥናቱ ላይ ከተሳተፉት ሦስት እጅ ያህሉ ክብደታቸው የጨመረው ከመጋቢት ወዲህ ነው።

    35 በመቶ ያህሉ የሚመገቡት መጨመሩን፣ 27 በመቶዎቹ ደግሞ አካል ብቃት እንቅስቃሴ መተዋቸውና አልኮል መጎንጨት ማዘውተራቸውን ተናግረዋል።

    ጥናቱን በበላይነት የመሩት ቲም ስፔክተር፤ ዩናይትድ ኪንግደም ከወረርሽኙ በፊትም ከመጠን ያለፈ ውፍረት የሚታይባት ነበረች ካሉ በኋላ “የእንቅስቃሴ ገደቡ ሁኔታዎችን አባብሷል” ብለዋል።

    በጥናቱ ከተሳተፉ ሰዎች መረዳት እንደተቻለው፤ በአማካይ 0.78 ኪሎ ግራም መጨመር መታየቱም ተጠቅሷል።

    አርብ እለት በእንግሊዝ ሕብረተሰብ ጤና የታተመው ሪፖርት እንደጠቀሰው፤ ክብደት መጨመርም ሆነ ከመጠን ያለፈ ውፍረት በኮሮናቫይረስ የሚያዙ ሰዎች ሆስፒታል ተኝተው እንዲታከሙ ሲከፋም ለሞት እንዲዳረጉ ያደርጋል።

    ክብደት

    የፎቶው ባለመብት, PA Media

  19. ፍንጃል ቡና ለኮሮናቫይረስ 'አጋለጠኝ' ያሉት ከንቲባ

    የቡና ሱሰኛውና ጥንቁቁ ከንቲባ በኮሮናቫይረስ ለመያዛቸው የቡና ሱሳቸው ምከንያት ሊሆን እንደሚችል ተናግረዋል።

    ዳንኤል ኩዊንቴሮ፣ የኮሎምቢያዋ ሜዲሊን ከተማ ከንቲባ ናቸው። አሁን በኮሮናቫይረስ ከመያዛቸው በፊት አብዝተው በመጠንቀቃቸው ነበር የሚታወቁት።

    የኮሮናቫይረስ እንዲህ ዓለምን ከእግር እስከ ራሷ ወርሮ ሳያስጨንቃት በፊት በወርሃ ታህሳስ በከተማቸው የሚንቀሳቀሱ ፖለቲከኞችን በመሰብሰብ እና ምክክር በማድረግ የመከላከል እርምጃዎችን ነድፈዋል።

    የመከላከል ስልታቸውም ፍሬ አፍርቶ በሚያዚያ መጨረሻ አካባቢ በሚያስተዳድሯት ሜዲሊን ሁለት ሰዎች ብቻ ነበር የሞቱት። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በከተማዋ በኮሮናቫይረስ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ መጥቷል።

    ከንቲባው ለኮሎምቢያ ሬዲዮ በሰጡት ቃለ ምልልስ ላይ እንደገለፁት፤ በኮሮናቫይረስ ለመያዛቸው የቡና ሱሳቸው ምክንያት ሳይሆን እንደማይቀር ተናግረዋል።

    “በጣም ብዙ ቡና ነው የምጠጣው በቀን ውስጥ፤ እናም ቡናዬን ለመጠጣት በተደጋጋሚ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛዬን አወልቃለሁ፤ ያ ሊሆን ይችላል ያጋለጠኝ” ብለዋል።

    ቡና አፍቃሪያንም ቢያንስ በራሳቸው ፔርሙስ ቡናቸውን ይዘው እየተንቀሳቀሱ ቢጠጡ የተሻለ መሆኑን በመጥቀስ ምክራቸውን ለግሰዋል። ይህ ደግሞ በየካፍቴሪያው ከሚቀርብላቸው ስኒ ቫይረሱን እንዳይሸምቱ ለመከላከል እንዲረዳቸው በሚል ነው።

    ከንቲባው

    የፎቶው ባለመብት, AFP

  20. 45 ሚሊዮን የሚጠጉ ደቡብ አፍሪካውያን ለረሃብ ተጋልጠዋል ተባለ

    45 ሚሊዮን የሚጠጉ ደቡብ አፍሪካውያን በድርቅ፣ በጎርፍና በኮሮናቫይረስ ምክንያት ረሃብ እንደተጋረጠባቸው 16 አገራትን የሚወክለው ቀጠናዊ ቡድን አስታወቀ።

    ደቡባዊ አፍሪካ የእድገት ማኅበረሰብ (ሳድክ) የተባለው የቀጠናው ቡድን፤ በደቡባዊ አፍሪካ የከተማ ድሆች ኮሮናቫይረስ ክፉኛ እንደጎዳቸው ጠቅሰዋል።

    በአገራቱ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመከላከል በሚል የተጣለው የእንቅስቃሴ ገደብ ድሆች እንደልባቸው ወጥተው ነግደውና ሸምተው እንዳይኖሩ ፈተና ሆኖባቸዋል ተብሏል።

    ሥራ አጥነት እየጨመረ፣ ንግዶች እየተቀዛቀዙ እንዲሁም ከባህር ማዶ የሚላክ የውጪ ምንዛሬ እየቀጨጨ መሆኑም ተጠቅሷል።

    ዜጎች መሰረታዊ የቤት እቃቸውን በመሸጥ ምግብ እየገዙ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጠናው ትምህርት ቤት በመዘጋቱ ምክንያት 20 ሚሊዮን ታዳጊዎች ከትምህርት ቤት ምገባ ቀርተዋል።

    ደቡብ አፍሪካ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images