“ፈረንሳዊያኑ ‘የቫይረሱ ክትባት በአፍሪካ መሞከር አለበት’ ማለታቸው ያበሳጫል”- የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ዳይሬክተር
የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ዳይሬክተር ፈረንሳዊው ዶክተር የኮሮናቫይረስ ክትባት በአፍሪካ ይሞከር ማለታቸውን አወገዙ።
ፈረንሳዊው ዶክተር፤ "ይህንን ሙከራ ማድረግ ያለብን አፍሪካ አይደለምን? የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ (ማስክ) በሌለበት፣ ህክምና በላደገበትና፣ መተንፈስ ቢያዳግት እንኳን ትንፋሽ መመለስ የሚያስችል መሳሪያ በሌለበት መሆን አይገባውም?" ብለዋል።
ጨምረውም "ልክ በአፍሪካውያን የወሲብ ንግድ ተዳዳሪዎች ላይ የኤድስ ጥናት እንደተሞከረባቸው። ምክንያቱም ራሳቸውን መጠበቅ እንደማይችሉምና፤ በጣም ተጋላጭ እንደሆኑ እናውቃለን” ሲሉ ነበር ዶ/ር ጂን ፖል ሚራ በቴሌቪዥን በተካሄደ ውይይት ላይ የተናገሩት።
በውይይቱ ተሳታፊ የነበሩትና የኢንሰርም የጥናት ቡድንን ወክለው የተገኙት ካሚሌ ሎችትም በዶክተሩ ሃሳብ ተስማምተዋል።
ታዲያ ይህ ዘረኛ የተባለው ንግግራቸው በርካቶችን አስቆጥቷል።
በዶክተሩ ንግግር ከተበሳጩት መካከል ታዋቂዎቹ አፍሪካዊያን እግር ኳስ ተጨዋቾች ዲዲየር ድሮግባና ሳሙኤል ኤቶም ይገኙበታል።
“ንግግሩ ዘረኝነት የተሞላበት እና አፍሪካውያንን እንደ የቤተ ሙከራ አይጦች የቆጠረ ነው” ሲሉ ነቅፈውታል።
የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ዳሬክተር ዶ/ር ማሺዲሶ ሞቲም በትዊተር ገጻቸው ላይ ንግግሩን በጥብቅ አውግዘዋል።
ዶ/ር ጂን ትናንት መስሪያ ቤታቸው ባወጣው መግለጫ ላይ በንግግራቸው ክፉኛ የተጎዱትን በሙሉ “ይቅር በሉኝ!” ብለዋል።
ይህ ጽሑፍ በX. የቀረበ ይዘት ይዟል። ገጹ ቴክኖሎጂዎች ወይም ኩኪዎች ሊኖረው ስለሚችል ገጹ ከመከፈቱ በፊት የእርስዎን ፍቃድ እንጠይቃለን። ፍቃድዎን ከመስጠትዎ በፊት የX ኩኪ ፖሊሲ እና የ ማንበብ ይፈልጉ ይሆናል። ይዘቱን ለማንበብ ‘እቀበላለሁ ቀጥል’ የሚለውን ይምረጡ።
የ X ይዘት መጨረሻ



















