ወደ ቻይና በሚጓዝ የኩዌት ነዳጅ ጫኝ መርከብ ላይ ጥቃት ተፈጸመ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ሌሊቱን የኩዌት ሰንደቅ ዓላማ የሚያውለበልብ አል ሳልሚ የተባለ ነዳጅ ጫኝ መርከብ “ምንነቱ ባልታወቀ ተተኳሽ” በዩናይትድ አረብ ኤሜሬትስ የባሕር ዳርቻ ዱባይ ላይ በቆመበት ጥቃት እንደደረሰበት ቫንጋርድ የተሰኘው የባሕር ትራንስፖርት ደኅንነት ኩባንያ አስታውቋል።
ኩባንያው ጥቃቱን ተከትሎ በመርከቧ ላይ መጠነኛ ጉዳት መድረሱ እና እሳት ተቀስቅሶ እንደነበር ጠቅሶ በቁጥጥር ስር መዋሉን ገልጿል።
የመርከቧ 24 ሠራተኞችም ምንም ዓይነት ጉዳት እንዳላጋጠማቸው እንዲሁም ጥቃቱን ተከትሎ የፈሰሰ ነዳጅ አለመኖሩን ይፋ አድርጓል።
የዱባይ ባለሥልጣናት ስለ ጥቃቱ መፈጸም አረጋግጠው ስለመርከቧ ዝርዝር መረጃ ከመስጠት ተቆጥበዋል። የኩዌት ነዳጅ ኮርፖሬሽን ግን ጥቃቱን “የኢራናውያን ጨካኝ የአየር ጥቃት” ሲል ገልጾታል።
የኢራን መገናኛ ብዙኃን ስለ ጥቃቱ ቢዘግቡም ማን እንደፈጸመው ግን አልገለጹም።
አል ሳልሚ በአውሮፓውያኑ 2011 የተሠራች ሲሆን፣ በባለቤትነት የተያዘችው እና የምትንቀሳቀሰው በኩዌት የነዳጅ ዘይት ጫኝ ኩባንያ ስር ነው።
ቢቢሲ አደጋውን በተመለከተ ከኩባንያው አስተያየት ለማግኘት ጥያቄ አቅርቧል።
ታንከርታንከርስ የተባለ ሌላ የማሪታይም ደኅንነት ኩባንያ መርከቧ 1.2 ሚሊዮን በርሜል የሳዑዲን እንዲሁም 800,000 በርሜል የኩዌት ድፍድፍ ነዳጅ መጫኗን ገልጿል።
የነዳጅ ጭነቱ የተጠናቀቀው ባለፈው ወር መሆኑን ድርጅቱ ጨምሮ አስታውቋል።
ስለ መርከቧ የጉዞ መስመር ይፋ የሆኑ መረጃዎች መዳረሻዋ ኪንጋዶ ቻይና መሆኑን ያሳያሉ።

የፎቶው ባለመብት, Nader Itayim

















