ትራምፕ ከኢራን ያሉ ነገሮች “በጥሩ ሁኔታ እየሄዱ ነው” አሉ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለኤኤፍፒ የዜና ወኪል በስልክ በሰጡት አጭር ቃለ ምልልስ ከኢራን ጋር “ሁኔታዎች በጥሩ ሁኔታ እየሄዱ ነው” ብለዋል።
ትራምፕ ይህንን ያሉት በማኅበራዊ ድረ ገጻቸው ላይ ከቴህራን ጋር መነጋገራቸውን እና አገሪቱ የሆርሙዝ ወሽመጥን እንድትከፍት ያስቀመጡትን የሰዓታት ገደብ በአምስት ቀናት ማራዘማቸውን ከተናገሩ በኋላ ነው።
ትራምፕ ይህንን ቢሉም የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ግን በሁለቱ አገራት መካከል የተደረገ ምንም ዓይነት ንግግር አለመኖሩን በመግለጽ አስተባብሏል።
ዶናልድ ትራምፕ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ላይ “ለአምስት ቀን ያህል እንጠብቃለን፤ እና ያ እንዴት እንደሚሄድ እናያለን፤ ሁኔታዎች ጥሩ የሚሄዱ ከሆነ በስምምነት በእንቋጨዋለን” ሲሉ ተናግረዋል።
“ያ ካልሆነ ግን ድብደባችንን እንቀጥላለን” ሲሉ ተናግረዋል።
ትራምፕ ኢራን “ድርድር ማድረግ በጣም ነው የሚፈልጉት፤ እኛም ከስምምነት መድረስ እንፈልጋለን” ብለዋል።
አክለውም “ምናልባት በስልክ ዛሬም ንግግራችንን እንቀጥላለን” ሲሉ ከቴህራን ጋር ያላቸው ንግግር መቀጠሉን አስረድተዋል።
“በመካከለኛው ምሥራቅ ያሉ አጋሮች” ያሏቸው አገራት “በውይይታችን ውስጥ በጣም የምናስባቸው ይሆናል” ሲሉ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።
ትራምፕ የኢራን ጦርነት እንዲያበቃ ከስምምነት ላይ መድረስ ከተቻለ የነዳጅ ዘይት ዋጋ “በፍጥነት ይቀንሳል” ሲሉ ተናግረዋል።
የካቲት 21 2018 ዓ.ም. አሜሪካ እና እስራኤል በቴህራን ላይ ጥቃት መክፈታቸውን ተከትሎ የነዳጅ ዘይት እና የተፈጥሮ ጋዝ ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ ጭማሪ አሳይቷል።
ትራምፕ ለጋዜጠኞች “ስምምነት ላይ የመድረስ ዕድል አለን” ያሉ ሲሆን፤ አክለውም “ያ ግን ለምንም ነገር ዋስትና አይሰጥም። ምንም ዋስትና እየሰጠሁ አይደለም” ብለዋል።
ትራምፕ ሁለቱ አገራት ጦርነቱን ለማቆም በ15 ነጥቦች ላይ መነጋገራቸውን አብራርተው፣ ኢራን የኒውክሌር ጦር መሣሪያዎቿን እንድትተው “አንደኛው፣ ሁለተኛው እና ሦስተኛው ነጥቦች” መሆናቸውን ተናግረዋል።
ይሁን እንጂ ትራምፕ “በጣም ወሳኝ የሆነ የስርዓት ለውጥ” ማየት እንደሚፈልጉ ገልጸዋል።














