ተጨማሪ ወታደሮቿ እና የጦር መርከቧ ወደ ባሕረ ሰላጤው የደረሱት አሜሪካ የእግረኛ ዘመቻ ለማካሄድ መዘጋጀቷ ተነገረ

ቅዳሜ ዕለት በሺዎች የሚቆጠሩ ተጨማሪ ወታደሮች እና አንድ የጦር መርከቧ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ የደረሱት የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስቴር ፔንታገን በኢራን ውስጥ ለሳምንታት የሚቆይ የእግረኛ ሠራዊት ዘመቻ ለማካሄድ እየተዘጋጀ መሆኑ ተገለጸ።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኢራን ከጠላት ጋር ተባብረዋል ያለቻቸውን ዜጎቿን ንብረት መውረስ ጀመረች

    የኢራን ወታደር ቴህራን ውስጥ

    የፎቶው ባለመብት, Anadolu via Getty Images

    የኢራን መንግሥት “ከጠላት” ጋር ግንኙነት ያላቸው እና የእስላማዊ ሪፐብሊኩ ተቃዋሚዎች ናቸው ያላቸውን ሰዎች ንብረት መውረስ መጀመሩን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን እየዘገቡ ነው።

    መንግሥት ጠላት ካላቸው አገራት ጋር በማበር ጉዳት እንዲደርስ ያደረጉ እና መረጃን ያቀበሉ በውጭ የሚኖሩ የአገሪቱ ዜጎች እና ቤተሰቦቻቸው ንብረት ላይ ነው በዐቃቤ ሕግ ውሳኔ የተላለፈው።

    ዘገባዎች ስማቸው በግለጽ ያልተጠቀሱ ሁለት ሰዎች ንብረት በዐቃቤ ሕግ ውሳኔ መወረሱን አመልክተዋል። የቀረበባቸው ክስም ከአገሪቱ ከወጡ በኋላ በውጭ አገራት ሆነው “ከጠላት ጋር በመተባበር ፀረ-ኢራን የሆኑ ተግባራትን መፈጸም” የሚል ነው።

    ለኢራን መንግሥት እና የአብዮታዊው ዘብ ቅርብ የሆኑ መገናኛ ብዙኃን ንብረታቸው የተወረሰ ሰዎችን ስም እና ምሥል በማውጣት የዘገቡ ሲሆን፣ እርምጃውንም አወድሰዋል።

    ሌላኛው የኢራን መንግሥት የዜና ወኪል “ሚዛን” እንደዘገበው “ከውጭ የስለላ ተቋማት ጋር በመገናኘት በኢራን ውስጥ የሽብር ተግባራት እንዲፈጸሙ” አድርጓል የተባለ ግለሰብ እና የዘመዶቹ ንብረት እንዲወረስ ተደርጓል።

    የኢራን የሕግ እና የደኅንነት ተቋማት በተደጋጋሚ ዜጎች በአገሪቱ ውስጥ የሚከሰቱ ነገሮችን መቅረጽ እና ለመገናኛ ብዙኃን አሳልፎ መስጠት “በአገር ብሔራዊ ጥቅም ላይ የሚፈጸም ወንጀል ማስረጃ” እንደሚሆን በተደጋጋሚ ሲያስጠነቅቁ ቆይተዋል።

  2. የእስራኤል ጦር የደቡባዊ ሊባኖስ ግዛትን ተቆጣጥሬ እቆያለሁ አለ

    እስራኤል ሊታኒ ወንዝ ላይ የሚገኙ አምስት ድልድዮችን አውድማለች

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, እስራኤል ሊታኒ ወንዝ ላይ የሚገኙ አምስት ድልድዮችን አውድማለች

    የእስራኤል ወታደሮች ሄዝቦላህ ላይ ለከፈቱት ዘመቻ ሲባል በደቡባዊ ሊባኖስ የሚገኝ መሬትን ተቆጣጥረው እንደሚቆዩ የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስትር ኢዝራኤል ካትዝ ተናገሩ።

    የእስራኤል ጦር የሚቆጣጠረው የመሬት ክፍል ከአገሪቱ አጠቃላይ ስፋት 10 በመቶው ገደማ እንደሚሆን ሮይተርስ ዜና ወኪል ዘግቧል።

    የመከላከያ ሚኒስትሩ፤ ጦራቸው ከሊባኖስ እና እስራኤል ድንበር 30 ኪሎ ሜትር ገደማ ውስጥ የሚገኙትን የሊታኒ ወንዝ ድልድዮች ማፈንዳቱን ተናግረዋል።

    የእስራኤል ጦር ስፍራውን “የደኅንነት ዞን” እንደሚታደርገው የተናገሩት ካትዝ፤ የሰሜን እስራኤል ደኅንነት ሳይጠበቅ የተፈናቀሉ ነዋሪዎች ወደ ቅያቸው እንዲመለሱ እንደማይፈቀድላቸው ገልጸዋል።

    “በሄዝቦላህ ለሽብርተኞች እና መሣሪያዎች መተላለፊነት ጥቅም ላይ ሲውሉ” የነበሩ አምስት ድልድዮች ወድመዋል ብለዋል።

    ሄዝቦላህ እርምጃውን ለሊባኖስ “የኅልውና ስጋት” ሲል ጠርቶታል። የእስራኤል ወታደሮች ደቡባዊው የአገሪቱን ክፍል እንዳይቆጣጠሩ እንደሚዋጋም አስታውቋል።

    የሄዝቦላህ ከፍተኛ ሕግ አውጪ የሆኑት ሐሰን ፍድላላህ፤ እስራኤል በደቡባዊ ሊታኒ የፈጸመችው ወረራ ፍልሚያ ይገጥመዋል ማለታቸውን ሮይተርስ ዘግቧል። “አጥቂዎቹን ከመጋፈጥ እና መሬቱን ከመያዝ ውጪ አማራጭ የለንም” ብለዋል።

    እስራኤል በሊባኖስ ሰሞነኛውን ዘመቻ የከፈተችው በኢራን የሚደገፈው ሄዝቦላህ ወደ ሰሜን እስራኤል ሮኬቶችን ካስወነጨፈ በኋላ ነው። ቡድኑ ይህንን ጥቃት የፈጸመው እስራኤል እና አሜሪካ በከፈቱት ጥቃት ለተገደሉት የኢራን ጠቅላይ መሪ በቀል ነው።

    እስራኤል በሊባኖስ ጥቃት ከከፈተች ወዲህ 121 ሕጻናትን እና 42 የጤና ባለሙያዎችን ጨምሮ 1,072 ሰዎች መገደላቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር ገልጿል። ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰዎችን ከመኖሪያቸው ተፈናቅለዋል።

  3. ኢራን የኒውክሌር ኃይል ማመንጫዋ በድጋሚ ጥቃት እንደተፈጸመበት አስታወቀች

    በደቡባዊዋ ቡሼህር የሚገኘው ይህ ተቋም ሥራ ላይ ያለው ብቸኛው የኢራን የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ነው

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በደቡባዊዋ ቡሼህር የሚገኘው ይህ ተቋም ሥራ ላይ ያለው ብቸኛው የኢራን የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ነው

    የኢራን አውቶሚክ ኤነርጂ ድርጅት ‘ቡሼህር’ የተባለው የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ተቋም በትናንትናው ዕለት በድጋሚ ጥቃት እንደተፈጸበት አስታወቀ።

    ዓለም አቀፉ የአውቶሚክ ኤነርጂ ተቋም በበኩሉ በኢራን የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ላይ የተሰነዘረ ጥቃት “ግቢውን ስለመምታቱን” በቴህራን እንደተነገረው ገልጿል።

    የኒውክሌር ስፍራው የተመታው አሜሪካ እና እስራኤል የከፈቱት “ቀጣይነት ያለው” ጥቃት እንደሆነ የኢራኑ አውቶሚክ ኤነርጂ ድርጅት ተግሯል።

    ይሁን እንጂ በጥቃቶቹ “የፋይናንስም ሆነ ቴክኒካል እንዲሁም በሰው ላይ ጉዳት” አለመድረሱን አስታውቋል። “የተቋሙ የትኛውም ክፍል” አልተመታም ብሏል።

    እንደ አውቶሚክ ኢነርጂ ድርጅቱ ገለጻ፤ ይኸው የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ከሳምንት በፊት ጥቃት ደርሶበት የነበረ ቢሆንም የመጀመሪያው ጥቃትም በሰው እና በንብረት ላይ ጉዳት አላደረሰም።

    “በሰላማዊ የኒውክሌር ተቋማት ላይ” የተፈጸሙትን ጥቃቶች ያወገዘው ድርጅቱ፤ ይህ ዓይነት እርምጃዎች ለቀጣናው በተለይም በባሕረ ሰላጤው “ለሚገኙ አገራት” ደኅንነት “አደገኛ እና ሊቀለበስ የማይችል መዘዝ ያመጣሉ” ሲል አስጠንቅቋል።

    ዓለም አቀፉ የአውቶሚክ ኤነርጂ ተቋም ባወጣው መግለጫ ስለ ጥቃቱ ከኢራን መረጃ እንደደረሰው ገልጿል። “እንደ ኢራን ገለጻ በራሱ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫው ላይ ወይም ሠራተኞች ላይ የደረሰ ጉዳት የለም፤ የማመንጫው ሁኔታ ጥሩ ነው” ብሏል።

    የተቋሙ ኃላፊ ራፋኤል ግሮሲ “በግጭቱ የኒውክሌር ደኅንነት ስጋትን ለማስወገድ ሲባል” ተሳታፊ አገራት ወታደራዊ እርምጃ ከመውሰድ “በከፍተኛ መጠን እንዲታቀቡ” በድጋሚ ጠይቀዋል።

    በደቡባዊዋ ኢራን ከተማ ቡሼህር የሚገኘው እና በሥራ ላይ ያለው ብቸኛው የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ የተጠናቀቀው በሩሲያ እገዛ ነበር።

    አከራካሪው የኢራን ኒውክሌር ፕሮግራም አገሪቱ ዓለም አቀፍ ማዕቀብ እንዲጣልባት ምክንያት ሆኗል። አሜሪካ እና እስራኤል ኢራን ላይ ጥቃት የከፈቱት ዋሽንግተን እን ቴህራም ጄኔቫ ውስጥ ቀጥተኛ ባልሆነ መንገድ ሦስተኛ ዙር የኒውክሌር ድርድር ካደረጉ ከሁለት ቀናት በኋላ ነበር።

  4. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ባለ 15 ነጥብ የድርድር እቅድ ወደ ኢራን ላኩ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ባለ 15 ነጥብ የተኩስ አቁም እቅድ በፓኪስታን በኩል ወደ ኢራን መላካቸውን መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    የትራምፕ እቅድ ኢራንን የኒውክሌር አቅም በሙሉ ማጥፋት በምላሹም ቴህራን ላይ የተጣሉ ማዕቀቦችን ማንሳትን እንደሚያካትት ተነግሯል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ትናንት ምሽት ባደረጉት ከጋዜጠኞች ጋር በነበራቸው ቆይታ ጦርነቱን ለመቋጨት ኢራን ውስጥ ካሉ “ትክክለኛዎቹ ሰዎች ጋር” ንግግር እያደረጉ እንደሆነ ገልጸዋል። የኢራን ባለሥልጣናት “ክፉኛ ስምምነት ላይ መድረስ ፈልገዋል” ሲሉም ተደምጠዋል።

    እንደ ትራምፕ ገለጻ እየተደረገ ባለው ንግግር ምክትል ፕሬዝዳንቱ ጄዲ ቫንስ እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማርኮ ሩቢዮ ተሳታፊ ናቸው።

    የኢራን መንግሥት በጭራሽ የኒውክሌር መሣሪያ እንዳይኖረው ተስማምቷል ሲሉም ከዚህ ቀደም ሲናገሩ የነበሩትን ሀሳብ ደግመዋል። አክለውም የኢራን ተደራዳሪዎች ከነዳጅ እና ጋዝ ጋር በተያያዘ “እጅግ ትልቅ ሽልማት” ሰጥተውናል ብለዋል።

    “በትናትናው ዕለት እጅግ አስገራሚ ነገር አድርገዋል። ስጦታ ሰጥተውናል እናም ስጦታው ዛሬ ደርሷል። እጅግ ከፍተኛ የሆነ ገንዘብ የሚያወጣ በጣም ትልቅ ስጦታ ነው” ሲሉ ለጋዜጠኖች ተናግረዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ሽልማት ሲሉ የጠሩት ነገር ከሆርሙዝ ወሽመጥ ጋር የሚያያዝ እንደሆነ ቢጠቅሱም ዝርዝር መረጃ አልሰጡም። ይህ ሽልማት ከኢራን መሰጠቱ “ከትክክለኛዎቹ ሰዎች ጋር እየተነጋገሩ” መሆኑን እንደሚያሳይም ገልጸዋል።

    “አመራሮቻቸውን በሙሉ ገድለናል፤ ከዛም ተሰብስበው አዲስ መሪዎችን መረጡ፤ እነሱንም በሙሉ ገደልናቸው” በማለት የተናገሩት ትራምፕ፤ የአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃቶች በኢራን “የአገዛዝ ለውጥ” አምጥቷል ብለዋል። አክለውም ግን “ማንንም አላምንም” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ትራምፕ ይህንን ካሉ በኋላ የወጡ ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት አሜሪካ 15 የመደራደሪያ ነጥቦችን አቅርባለች። ስለ እቅዱ በቅድሚያ የዘገበው የአሜሪካው ኒው ዮርክ ታይምስ ጋዜጣ፤ በፓኪስታን በኩል የተላከው እቅድ ወደ ኢራን ባለሥልጣናት ስለመድረሱ እንዲሁም ተቀባይነት ስለማግኘቱ እንዳልተረጋገጠ ገልጿል።

    የእስራኤሉ ቴሌቪዥን ጣቢያ “ቻናል 12” በበኩሉ በአሜሪካ እቅድ ውስጥ ከተካተቱት ነጥቦች መካከል የኢራንን የኒውክሌር ፕሮግራም ሙሉ በሙሉ ማጥፋት የሚል እንደሚገኝበት ዘግቧል። ኢራን ተቀጽላ ለሆኑ ታጣቂ ቡድኖች የምትሰጠውን ድጋፍ እንድታቆም ማድረግ እንዲሁም የሆርሙዝ ወሽመጥን መክፈትም ከመደራደሪያ ነጥቦች መካከል ናቸው ተብሏል።

    ሁለቱ አገራት ድርድር እንዲያካሂዱ የአንድ ወር የተኩስ አቁም እንዲደረግ የሚጠይቀው የትራምፕ እቅድ፤ ኢራን በአንጻሩ ሁሉም ማዕቀቦች እንዲነሳላት እንደሚያደርግ የእስራኤሉ መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

  5. ኢራን “ሁሉን አቀፍ ተኩስ አቁም እንጂ ጊዜያዊ ስምምነትን አትቀበልም” የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራግቺ

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ አገራቸው ከአሜሪካ ጋር ሁሉን አቀፍ የተኩስ አቁም እንጂ ጊዜያዊ ስምምነት ማድረግ እንደማትፈልግ ተናገሩ።

    የውጭ ጉዳይ ሚስትሩ ይህንን የተናገሩት ከቻይናው አቻቸው ዋንግ ይ ጋር ባደረጉት ውይይት ላይ መሆኑን የቻይና መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    አራግቺ “ኢራን ለጊዜያዊ ሳይሆን ለሁሉን አቀፍ የተኩስ አቁም ስምምነተ ዝግጁ ናት” በማለት ለመላው ዓለም አሳሳቢ የሆነው የሆርሙዝ ወሽመጥም ከጠላቶቻቸው በስተቀር ለሌሎች ክፍት መሆኑን ተናግረዋል።

    በዚህም ከኢራን ጋር “ጦርነት ውስጥ ከገቡት አገራት በስተቀር ሆርሙዝ በአሁኑ ወቅት ሁሉም መርከቦች ምንም ችግር ሳይገጥማቸው ማለፍ ይችላሉ” ብለዋል።

    የቻይና መንግሥት መገናኛ ብዙኃን በኢራን እና በቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች መካከል የተደረገውን ውይይት በተመለከተ መግለጫ ያቀረበ ሲሆን፣ የቻይናው ሚኒስትር በኢራን እና በተቀናቃኞቿ መካከል ያለውን አለመግባባት ለመፍታት ንግግር ዋነኛ መንገድ መሆን አለበት ብለዋል።

    ዋንግ ይ “ሁሌጊዜም መነጋገር ከመዋጋት የተሻለ ነው” በማለት ሁሉም ወገኖች “ለሰላም እና ለንግግር የተከፈቱ አጋጣሚዎችን በፈጥነት” እንዲጠቀሙ ጥሪ አቅርበዋል።

  6. ሆርሙዝ ወሽመጥን ለመጠበቅ አገራት ጥምረት ሊመሠርቱ ነው

    ግዙፍ የጭነት መርከቦች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዩናይትድ ኪንግደም እና ፈረንሳይ በፋርስ ባሕረ ሰላጤ “ያለው ሁኔታ ሲፈቅድ” ወሳኙ የባሕር መተላለፊ መስመር የሆነውን ሆርሙዝ ወሽመጥን ለመጠበቅ የሚያስችል የአገራት ጥምረት ለመመሥረት እየጣሩ መሆናቸውን የመከላከያ ባለሥልጣናት አስታወቁ።

    ለዚህም ዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) ለዓለም የነዳጅ እንቅስቃሴ ወሳኝ የሆነውን ሆርሙዝ ወሽመጥን ለመጠበቅ የሚያስችሉ ዕቅዶችን ለማዘጋጀት የሚያስችል የደኅንነት ጉባዔ ለንደን ወይም ፖርትስማውዝ ከተማ ውስጥ በቅርቡ ለማስተናገድ ፈቃደኛ መሆኗን አሳውቃለች።

    ባለሥልጣናት እንዳሉት በሆርሙዝ በኩል ለሚያልፉ የንግድ መርከቦች ጥበቃ ለማድረግ የተለያዩ አገራት ባሕር ኃይሎች ጥምረት ያስፈልጋል። በተለይ ደግሞ ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን ማጀብ በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ ደረጃ እንደደረሰው ዓይነት ስጋት ላይ የሚወሰን ይሆናል።

    ባለሥልጣናቱ እንደሚሉት በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል በሰላም ለመተላለፍ እና የባሕር ላይ ፈንጂዎችን ለማስወገድ በርካታ አገራት የሚሳተፉበት መፍትሄ ሊገኝ ይገባል።

    አሜሪካ እና አስራኤል በኢራን ላይ የከፈቱትን ጦርነት ተከትሎ በተፈጠረው የደኅንነት ስጋት 20 ከመቶ በላይ የሚሆነው የነዳጅ ምርት የሚተላለፍበት ሆርሙዝ ከሞላ ጎደል ተዘግቶ ቆይቷል። በዚህም ሳቢያ በዓለም ገበያ የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ አሳይቷል።

    ባለፈው ሳምንት ፕሬዝዳንት ትራምፕ የኔቶ አጋሮቻቸው የሆርሙዝ ወሽመጥን ደኅንነት በመጠበቅ እንዲተበባሩ ቢጠይቁም ተቀባይነት ሳገያኙ ቀርተዋል።

    በጦርነቱ ሳቢያ በተስተጓጎላው የነዳጅ ምርት ምክንያት አገራት ሌሎች አማራጮችን እየፈለጉ ሲሆን፣ ጦርነቱ እንዲቆም ግፊት እየተደረገ ነው።

  7. ኢራን ባለፈው ሳምንት ለተገደሉት የብሔራዊ ደኅንነት ዋና ፀሐፊ ተተኪ ሾመች

    ሞሐመድ ባግሄር ዞልጋሃር

    የፎቶው ባለመብት, More

    የምስሉ መግለጫ, አዲሱ ተሿሚ ሞሐመድ ባግሄር ዞልጋሃር

    የኢራኑ ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ባለፈው ሳምንት በእስራኤል ጥቃት ለተገደሉት የአገሪቱ ብሔራዊ ደኅንነት ጠቅላይ ምክር ቤት ዋና ፀሐፊ አሊ ላሪጃኒ ተተኪ ሰየሙ።

    ከፕሬዝዳንቱ ጽህፈት ቤት የወጡ መረጃዎችን ጠቅሰው የኢራን መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት በተለያዩ የመንግሥት እና ወታደራዊ ሥልጣን ላይ የቆዩት ሞሐመድ ባግሄር ዞልጋሃር ኃላፊነቱን ተረክበዋል።

    በኢራን መንግሥት ውስጥ ከፍተኛ ልምድ እና ተሰሚነት የነበራቸው የብሔራዊ ደኅነንት ምክር ቤቱ ዋና ፀሐፊ አሊ ላሪጃኒ ዋና ከተማዋ ቴህራን ውስጥ በተፈጸመባቸው የእስራኤል ጥቃት ከልጃቸው ጋር መገደላቸው ይታወሳል።

    አዲሱ ተሿሚ ዞልጋሃር በእስላማዊው አብዮታዊ ዘብ ምክትል አዛዥነትን ጨምሮ በከፍተኛ ኃላፊነቶች ላይ የሠሩ ሲሆን፣ በተጨማሪም በአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር የደኅንነት ምትል ሚኒስትር እንዲሁም በተለያዩ መንግሥታዊ ምክር ቤቶች ውስጥ በከፍተኛ ኃላፊነት ሠርተዋል።

    የቀድሞው ዋና ፀሐፊ ከተገደሉ ከሳምንት በኋላ የተሾሙት ሞሐመድ ባግሄር ዞልጋሃር በኢራን አብዮታዊ ዘብ ውስጥ የብርጋዲየር ጄነራልነት ማዕረግ እንደነበራቸው ተዘግቧል።

    አስራኤል የኢራኑን ጠቅላይ መሪን ጨምሮ በርካታ ባለሥልጣናትን የገደለች ሲሆን፣ የኢራን ወታደራዊ እና ፖለቲካዊ መሪዎችን ዒላማ ማድረጓን አንደምትቀጥል አስታውቃለች።

  8. የኢራን አብዮታዊ ዘብ በእስራኤል ላይ የሚፈጽመውን ጥቃት መቀጠሉን አስታወቀ

    የጥቃት ቦታ ላይ የሚታዩ ወታደሮች
    የምስሉ መግለጫ, እስራኤል ውስጥ የተፈጸመ ጥቃት

    አሜሪካ እና ኢራን ለድርድር እየተዘጋጁ ባለበት በአሁኑ ሰዓት እስራኤል እና ኢራን አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ የሚፈጽሙትን ጥቃት ቀጥለዋል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በዛሬው ዕለት የፈጸማቸውን ጥቃቶች በተመለከተ ባወጣው መግለጫ በተለያዩ የእስራኤል ክፍሎች ላይ የሚሳዔሎች ጥቃት መፈጸሙን አስታውቋል።

    በመግለጫው መሠረት ከፍተኛ የማውደም አቅም ያላቸውን የተለያዩ ዓይነት ሚሳዔሎችን እና ድሮኖችን በመጠቀም በተፈጸሙት ጥቃቶች ዒላማ የተደረጉትን የእስራኤል ይዞታዎችን ዘርዝሯል። በዚህም መሠረት

    • በሰሜን እና ማዕከላዊ ቴል አቪቭ የሚገኙ ጥበቃ የሚደረግላቸው የደኅንነት ተቋማት
    • ራማት ጋን እና ኔጌቭ ውስጥ የሚገኙ የንግድ እና ወታደራዊ ድጋፍ ማዕከላት
    • ቤርሼባ ውስጥ የሚገኝ የወታደራዊ አቅርቦት እና የአስተዳደር ዋነኛ ማዕከላት ይገኙባቸዋል ብሏል።
  9. የእስራኤል ባለሥልጣናት አሜሪካ ከኢራን ጋር የምታደርገው ድርድር የሚሳካ አይደለም አሉ

    የአሜሪካ እና የኢራን ባንዲራዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የእስራኤል ባለሥልጣናት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር ለማድረግ ያሰቡት ድርድር ውጤታማ ይሆናል ብለው እንደማያስቡ ተናገሩ።

    በኢራን እና በእስራኤል መካከል የሚፈጸሙት ጥቃቶች በቀጠሉበት በአሁኑ ሰዓት በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ድርድር ይጀመራል ተብሎ እየተጠበቀ ነው።

    በጦርነቱ ዋነኛ ተዋናይ የሆነችው የእስራኤል ባለሥልጣናት ግን ምንም እንኳን ትራምፕ ከኢራን ጋር ከስምምነት የመድረስ ቁርጠኝነቱ ቢኖራቸውም በኢራን ላይ ጥርጣሬ እንዳላቸው ለሮይተርስ ተናግረዋል።

    ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈቀዱ ሦስት የእስራኤል ባለሥልጣናት ለዜና ወኪሉ እንደገለጹት ኢራን ከአሜሪካ በኩል የሚቀርበውን ጥያቄ በመመለስ ከስምምነት ይደረሳል የሚል ዕምነት የላቸውም።

    አንድ ወር ሊሞላው ጥቂት ቀናት የቀሩት አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የከፈቱት ጦርነት የቀጠለ ሲሆን፣ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከስምምነት ካልተደረሰ ከባድ ጥቃት በኢራን ላይ ለመፈጸም የአምስት ቀናት ቀነ ገደብ አስቀምጠዋል።

    የኢራን እና የአሜሪካ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ፓኪስታን ውስጥ በዚህ ሳምንት ውስጥ እንደሚገናኙ የሚጠበቅ ሲሆን፣ አሜሪካ በኢራን የኒውክሌር እና የባሊስቲክ ሚሳዔል መረሃ ግብሮች ላይ ዕቀባዎች እንዲደረጉ ትፈልጋለች።

  10. ኢራን አስከ አውሮፓ ደርሰው ሊመቱ የሚችሉ ሚሳዔሎች አሏት?

    ኢራን በሕንድ ውቅያኖስ ዲያጎ ጋርሲያ ደሴት ላይ ወደሚገኘው የዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) እና የአሜሪካ የጋራ ወታደራዊ ሰፈር ላይ የረዥም ርቀት ባለስቲክ ሚሳዔሎችን ማስወንጨፏ በመካከለኛው ምሥራቅ ያለውን ግጭት እየተባባሰ መምጣቱን ያሳያል።

    በእርግጥ ሚሳዔሎቹ ወደታቀደላቸው ዒላማ ሳይደርሱ ቀርተዋል። ነገር ግን የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት ጦርነቱ ከተጀመረ ወዲህ እንዲህ ዓይነት የረዥም ርቀት ሚሳዔሎች ጥቅም ላይ ሲውሉ ይህ የመጀመሪያው እንደሆነ ተናግሯል።

    ባለሙያዎች አሁን የከሸፈው ጥቃት እንዲሁም በርቀት ለሚገኙ ዒላማዎች ይህ ምን ማለት እንደሆነ ጨምሮ የራሳቸውን ትንታኔ እየሰጡ ነው።

    የእስራኤል ባለሥልጣናት ኢራን ከመካከለኛው ምሥራቅ አልፈው አስከ አውሮፓ በመድረስ ውድመትን የሚያደርሱ ሚሳዔሎችን ታጥቃለች እያሉ በማስጠንቀቅ ላይ ናቸው።

    በእርግጥ ኢራን ወደ ታላላቆቹ የአውሮፓ ከተሞች ሊደርሱ ሚሳዔል ታጥቃለች? ዝርዝሩን ሊንኩን ተጭነው ያንብቡ።

    ሥዕል
  11. በመካከለኛው ምሥራቅ እየተካሄደ ባለው ጦርነት ዛሬ መነጋገሪያ የሆኑ አምስት ነጥቦች

    እስራኤል ሌሊቱን በቤይሩት ደቡባዊ ክፍል በቢር አል አቤድ ጥቃት ፈጽማ የደረሰ ጉዳት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, እስራኤል ሌሊቱን በቤይሩት ደቡባዊ ክፍል በቢር አል አቤድ ጥቃት ፈጽማ የደረሰ ጉዳት
    • በአሜሪካ እና በኢራን መካከል እየተካሄደ ነው ስለተባለው ንግግር አሁንም እርግጠኛ ሆኖ መናገር አይቻልም። ሰኞ ዕለት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት አገራቱ “ገንቢ” ውይይት ማድረጋቸውን ሲናገሩ፤ የኢራን ባለሥልጣናት ደግሞ ምንም ዓይነት ንግግር አለመጀመሩን በመግለጽ አስተባብለዋል። በኋላ ላይም ዋይት ሐውስ ሁኔታው “እርግጠኝነት የሌለው” መሆኑን ግለጿል።
    • ሰኞ ዕለት በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ከፍተኛ የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባለሥልጣንን ጠቅሶ “በአደራዳሪዎች በኩል የመወያያ ነጥቦች ደርሰውናል፤ እየተመለከትነው ነው” ማለታቸውን ዘግቧል።
    • የትራምፕ የመካከለኛው ምሥራቅ ልዩ መልዕክተኛ ስቲቭ ዊትኮፍ በዚህ ሳምንት ከኢራን ባለሥልጣናት ጋር በፓኪስታን እንደሚገናኙ መረጃዎች ወጥተዋል። ፓኪስታን ጥያቄ ከቀረበላት ውይይቶችን ለማስተናገድ ደስተኛ መሆኗን ገልጻለች።
    • ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን ጋር ንግግር መጀመራቸውን ከገለፁ በኋላ የነዳጅ ዘይት ዋጋ ቀንሶ የነበረ ቢሆንም ዛሬ በበርሜል ከ100 ዶላር በላይ እየተሸጠ ይገኛል።
    • ኢራን ሌሊቱን በርካታ ሚሳዔሎችን ወደ እስራኤል ያስወነጨፈች ሲሆን፣ በቴል አቪቭ እና በደቡባዊ እስራኤል የመኖሪያ ሕንጻዎች ላይ ጉዳት ደርሷል። እስራኤል እንዲሁ በቤይሩት በሄዝቦላህ መሠረተ ልማቶች ላይ ሁለት ድብደባዎችን መፈጸሟን አስታውቃለች።
  12. በማዕከላዊ እስራኤል የኢራን ጥቃት ያደረሰው ጉዳት

    ኢራን በማዕከላዊ እስራኤል በፈጸመችው ጥቃት በመኖሪያ ሕንጻዎች ላይ ጉዳት የደረሰ ሲሆን የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ወደ ሥፍራው ተሰማርተዋል።

    በጉዳቱ ምን ያህል ጉዳት እንደደረሰ እስካሁን ድረስ የታወቀ ነገር የለም።

    ከዚህ ቀደም ብሎ በደቡባዊ እስራኤል ኢራን ሚሳዔል ተኩሳ በፍንጥርጣሪው አንድ ነዋሪ ጉዳት እንደደረሰባት ተገልጾ ነበር።

    በማዕከላዊ እስራኤል ኢራን ፈጽማዋለች የተባለን ጥቃት ተከትሎ ጭስ ታይቷል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በማዕከላዊ እስራኤል ኢራን ፈጽማዋለች የተባለን ጥቃት ተከትሎ ጭስ ታይቷል
    በኢራን ጥቃት ጉዳት የደረሰበት ሕንጻ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በኢራን ጥቃት ጉዳት የደረሰበት ሕንጻ
    ጥቃት በተፈጸመበት አካባቢ የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ጥቃት በተፈጸመበት አካባቢ የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች
    በኢራን ጥቃት ጉዳት የደረሰበት ሕንጻ በከፊል ወድሟል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በኢራን ጥቃት ጉዳት የደረሰበት ሕንጻ በከፊል ወድሟል
  13. ፓኪስታን አሜሪካ እና ኢራን የሚያደርጉትን ድርድር ልታስተናግድ ነው

    የአሜሪካ እና የኢራን ባለሥልጣናት በፓኪስታን ተገናኝተው እንደሚወያዩ የተለያዩ መረጃዎች እየወጡ ነው።

    የፓኪስታን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ “ተደራዳሪዎች የሚፈልጉ ከሆነ “ አገራቸው “ውይይቶችን ለማስተናገድ ሁሌም ፈቃደኞች ናት” ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    ታሂር አንድራቢ ለቢቢሲ እንደገለጹት “ፓኪስታን በቀጣናው ሰላም እና መረጋጋት እንዲሰፍን በተደጋጋሚ ስለ ውይይት እና ዲፕሎማሲ ስትወተውት” እንደነበር ተናግረዋል።

    አንድራቢ ከየትኛውም አካል ጋር ስለ ውይይቶች መነጋገራቸውን አላረጋገጡም ወይም አላስተባበሉም።

    ዋይት ሐውስ ቀደም ሲል ሁኔታውን “እርግጠኛ የሆነ ጉዳይ” አለመሆኑን አስጠንቅቆ በኢራን እና በአሜሪካ ከፍተኛ ባለሥልጣናት መካከል መደበኛ ስብሰባ አለመደረጉን አስታውቋል።

    የፓኪስታን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ከአሜሪካ ሹማምንት ጋር ስለመነጋገራቸው የተሰጠ ይፋዊ መግለጫ የለም።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ሰኞ ዕለት ለጋዜጠኞች ሲናገሩ ከኢራን ጋር በ15 ነጥቦች ዙሪያ መወያየታቸውን ገልጸው ቀዳሚዎቹ የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ጉዳይ እንደሚሆን አብራርተዋል።

    ትራምፕ ከኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣን ጋር በነበራቸው ውይይት ወቅት አማካሪያቸው ስቲቭ ዊትኮፍ እና አማቻቸው ጃሬድ ኩሽነር አብረዋቸው እንደነበሩ ገልጸዋል።

    ስቲቭ ዊትኮፍ እና ኩሽነር ዩናይትድ ስቴትስ በእስራኤል እና በሐማስ መካከል ያደራደረችውን የተኩስ አቁም እንዲሁም ውጤት ያላመጣውን የዩክሬን እና ሩሲያ የሰላም ንግግር በበላይነት መርተዋል።

    ትራምፕ አክለውም ቴህራን የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ፕሮግራሟን ለመተው ፈቃደኛ ትሆናለች የሚል ሃሳብ አንዳላቸውም ገልጸዋል።

  14. ጃፓን ከብሔራዊ የመጠባበቂያ ነዳጅ ክምችቷን በማውጣት ለአገልግሎት ልታቀርብ ነው

    የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ሳናኤ ታካኢቺ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የጃፓኗ ጠቅላይ ሚኒስትር ሳናኤ ታካኢቺ አገራቸው ሐሙስ ዕለት ከብሔራዊ የነዳጅ መጠባበቂያ ክምችቷ እንደምትለቅ አስታውቀዋል።

    ጃፓን እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰችው የነዳጅ አቅርቦት እጥረት ስጋት እያደገ በመምጣቱ ነው።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጦርነት መክፈታቸውን ተከተሎ ቴህራን ሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥን በመዝጋቷ የዓለም የነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ ዋጋ አሻቅቧል።

    ታካኢቺ በኤክስ ገጻቸው ላይ “ከሐሙስ ጀምሮ ከብሔራዊ ክምችታችን ነዳጅ መልቀቅ እንጀምራለን” ብለዋል።

    ጃፓን ባለፈው ሳምነት “ለአገሪቱ በአጠቃላይ የሚያስፈልጋትን” ነዳጅ ለማቅረብ በሚል ከግል ክምችቶቿ መጠቀም ጀምራለች። ጃፓን የምትጠቀመው 95 በመቶ ነዳጅ የሚመጣው በሆርሙዝ ወሽመጥ ኩል ነው።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ዛሬ ማክሰኞ በእስያ የአንድ በርሜል ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት ዋጋ ከ100 ዶላር በላይ እየተሸጠ ነው።

  15. በደቡባዊ እስራኤል የኢራን ጥቃት ያደረሰው ጉዳት በምሥል

    ትናንት ሰኞ ሌሊት ኢራን ወደ እስራኤል ያስወነጨፈችው ሚሳዔል በደቡባዊ የአገሪቱ ክፍል በሃይፋ ክልል አንድ ሕንጸ መምታቱ ተገልጿል።

    ቀደም ሲል የአገሪቱ መከላከያ ከኢራን አቅጣጫ ሚሳዔል መወንጨፉን በመግለጽ አስጠንቅቆ ነበር።

    የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች አንዲት ወደ መጠለያዎች እየሄደች የነበረች ሴት በፍንጥርጣሪዎች ተመትታ ጉዳት እንደደረሰባት ገልጸዋል።

    በሃይፋ ክልል ኔሼር በተባለ አከባቢ ጥቃት የደረሰበት ሕንጻ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በሃይፋ ክልል ኔሼር በተባለ አከባቢ ጥቃት የደረሰበት ሕንጻ
    ጥቃቱ በተፈጸመበት ስፍራ የደረሱ የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ጥቃቱ በተፈጸመበት ስፍራ የደረሱ የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች
  16. ትራምፕ ለመፈጸም ያሰቡትን ጥቃት ሲያራዝሙ አሜሪካ እና ቴህራን የሚጣረሱ መረጃዎችን እየሰጡ ነው

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በመካከለኛው ምሥራቅ የሚካሄደው ጦርነት አሁንም እንደቀጠለ ነው። በትናንትናው ዕለት ፕሬዚዳንት ትራምፕ በኢራን እና አሜሪካ መካከል ንግግር ስለመጀመሩ ቢናገሩም ቴህራን ግን ያስተባበለችው ወዲያው ነበር።

    ቅዳሜ ዕለት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥን በ48 ሰዓታት ውስጥ የማትከፍት ከሆነ የኃይል ማመንጫዎቿን ለማውደም ዝተው ነበር።

    ይሁን እንጂ ሰኞ ዕለት ትራምፕ ከቴህራን ጋር “ውጤታማ” ንግግር ካደረጉ በኋላ የጥቃት ዕቅዳቸውን ማራዘማቸውን ተናግረዋል። ነገር ግን የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ 'ንግግር ተደርጓል' መባሉን አስተባብለው “የፈጠራ ወሬ" ብለውታል።

    ከፍተኛ የኢራን ባለሥልጣን ግን ለቢቢሲ የአሜሪካ አጋር ሲቢኤስ ኒውስ “በአደራዳሪ በኩል የመነጋገሪያ ነጥቦች ደርሰውናል፤ እየተመለከትናቸው ነው” ብለዋል።

    ሲቢኤስ "ይህ ለንግግር ቅድመ ሁኔታ እንጂ ምንም ዓይነት ድርድር እየተካሄደ ስለመሆኑ ወይንም እንደሚኖር አያሳይም" ሲል ዘግቧል።

    ዋይት ሐውስ በበኩሉ ሁኔታው ገና ያልጠራ መሆኑን በመግለጽ ጥንቃቄ እንደሚያስፈልግ አስታውቋል።

    "በዋይት ሐውስ በይፋ እስካልተገለጸ ድረስ ስለ ንግግሮች የሚሰነዘረው መላምት የመጨረሻ ተደርጎ ሊወሰድ አይገባም" ብሏል።

  17. ኢራን በአደራዳሪዎች በኩል "የመነጋገሪያ ነጥቦች" እንደ ደረሷት ገለጸች

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዩናይትድ ስቴትስ እና ኢራን እያደረጉ ስላለው ንግግር እርስ በእርሱ የሚጣረስ መረጃ እየሰጡ ባሉበት ወቅት የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከፍተኛ ባለሥልጣን ለቢቢሲ የአሜሪካ አጋር ሲቢኤስ ኒውስ “በአደራዳሪ በኩል ከአሜሪካ የመነጋገሪያ ነጥቦች ደርሰውናል፤ እየተመለከትናቸው ነው” ብለዋል።

    ሲቢኤስ ይህ “ለንግግር ቅድመ ሁኔታ እንጂ ድርድር እንደሚኖር ወይንም እየተካሄደ መሆኑን አያረጋግጥም" ሲል ዘግቧል።

    ይህ አስተያየት የተሰማው ፕሬዚዳንት ትራምፕ አሜሪካ እና ኢራን ጦርነቱን ለማቆም የሚያስችል ንግግር እያደረጉ መሆናቸውን በተናገሩበት ወቅት ነው።

    ከቴህራን በኩል ድርድሩን ይመራሉ ተብሎ ስማቸው የተነሳው የኢራን የፓርላማ አፈ ጉባዔ ግን መረጃውን ውድቅ አድርገዋል።

    ትራምፕ ቴህራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ካልከፈተች የኃይል ማመንጫዎቿን ለመደብደብ የያዙትን ዕቅድ ለሌላ ጊዜ አስተላልፈው። ግጭቱን ለማስቆም የሚያስችል ስምምነት ላይ መድረስ እንደሚቻልም ተናግረው ነበር።

  18. የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ ከአሜሪካ ጋር ድርድር ተጀምሯል መባሉን አስተባበሉ

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ ሞሐመድ ባግሄር ጋሊባፍ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ ሞሐመድ ባግሄር ጋሊባፍ

    ኢራን ከአሜሪካ ባለሥልጣናት ጋር ንግግር እያደረገች መሆኑ ከተገለጸ በኋላ የኢራን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ የድርድሩ መሪ መሆናቸው መገለጹን ተከትሎ ማስተባበያ ሰጡ።

    ትራምፕ በኢራን ላይ ከባድ ጥቃት ለመፈጸም ያስቀመጡት የጊዜ ገደብ ከመጠናቀቁ ከሰዓታት በፊት ከኢራን ጋር ንግግር መጀመሩን በመጥቀስ አምስት የንግግር ቀናት መስጠታቸውን አስታውቀዋል።

    ነገር ግን የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ከአሜሪካ ጋር የተጀመረ ንግግር እንደሌለ በመግለጽ ሲያስተባብሉ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ግን ተስፋ ሰጪ ንግግር መጀመሩን ጠቅሰዋል።

    ይህንንም ተከትሎ በርካታ የመገናኛ ብዙኃን ከፕሬዝዳንት ትራምፕ ልዩ መልዕክተኛ ስቲቭ ዊትኮፍ እና ልጃቸው ባል ጃሬድ ኩሽነር ጋር እየተደራደሩ ያሉት የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ ሞሐመድ ባግሄር ጋሊባፍ መሆናቸው በስፋት እየተዘገበ ነው።

    ነገር ግን አፈ ጉባዔው በኤክስ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባወጡት ጽሁፍ ከአሜሪካ ጋር ምንም ዓይነት ድርድር እየተደረገ አለመሆኑን አስተባብለዋል።

    ጨምረውም “ሐሰተኛ ዜና” ያሉት የድርድር መጀመር ጉዳይ ዓላማው በነዳጅ ዘይት ገበያ ዋጋ ላይ ተጽእኖ ለመፍጠር መሆኑን እና ኢራናውያን የሚፈልጉት “ወራሪዎቹ ላይ ሙሉ እና የሚያጸጽት ቅጣትን ነው” ብለዋል።

  19. ዩኬ በትራምፕ እና በኢራን መካከል ንግግር መጀመሩን እንደምታውቅ ስታርመር ተናገሩ

    ሰር ኪር ስታርመር

    የፎቶው ባለመብት, House of Commons/UK Parliament/PA

    የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር በአሜሪካ እና በኢራን መካከል እየተካሄደ ስላለው ንግግር አገራቸው እውቅናው እንዳላት ገለፁ።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን ያሉት ለፓርላማ የኮሚቴ አባላት ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ነው።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ሰር ኪር ስታርመር ውጥረቶች ረግበው እንዲሁም “በተቻለ ፍጥነት” ጦርነቱ ቆሞ ማየት እንደሚፈልጉ ተናግረዋል።

    “ለዚህም ሲባል በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተጀመረውን ድርድር በደስታ እቀበላለሁ" ሲሉ አክለዋል።

    ስታርመር “በድርድር የሚደረስበት ስምምነት” በኢራን ላይ “በተለየ ደግሞ ከኒውክሌር ጦር መሣሪያዎች ጋር በተያያዘ ጠንካራ ሁኔታዎችን ማስቀመጥ አለበት” ብለዋል።

    ቀደም ሲል ጽሕፈት ቤታቸው አሜሪካ ከኢራን ጋር የጀመረችውን ንግግር አስመልክቶ በሰጠው መግለጫ አድናቆቱን ገልጿል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ከቴህራን ጋር ንግግር መጀመራቸውን ተከትሎ በኢራን የኃይል መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት ለመፈጸም አስቀምጠውት የነበረውን የ48 ሰዓታት የጊዜ ገደብ ወደ አምስት ቀን አራዝመዋል።

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በበኩሉ ምንም ዓይነት ድርድር እንደሌለ በመግለጽ አስተባብሏል።

    ትራምፕ ሁለቱ አገራት ጦርነቱን ለማቆም በ15 ነጥቦች ላይ መነጋገራቸውን ገልጸው፣ ኢራን የኒውክሌር ጦር መሣሪያዎቿን እንድትተው የሚለው ቀዳሚው መሆኑን ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

  20. ትራምፕ ኢራን የኒውክሌር ፕሮግራሟን ለመተው ልትስማማ እንደምትችል ተናገሩ

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ለሰላም ሲባል የኒውክሌር ፕሮግራሟን ለመተው ልትስማማ እንደምትችል ተናገሩ።

    "ነገ ጠዋት፤ በእነርሱ የሆነ ሰዓት ላይ፣ ለመገንባት 10 ቢሊዮን ዶላር የወጣበትን ትልቁን የኤሌትሪክ ማመንጫ ፋብሪካቸውን ለማፈንዳት እየጠበቅን ነበር” ሲሉ ተናግረዋል።

    "በጣም ጥሩ ነበር፤ የገንዘብ እጥረት አልነበረም፤ በአንድ ተኩስ ይወድማል፤ ይፈራርሳል። ለምን ይህን ይፈልጋሉ?

    “እነርሱ ናቸው የደወሉት፤ እኔ አልደወልኩም። እነርሱ ደወሉ። ስምምነት ላይ መድረስ ፈልገዋል” ሲሉ ተናግረዋል።

    “እኛ ከስምምነት ላይ ለመድረስ በጣም ፈቃደኞች ነን። ጥሩ ስምምነት መኖር አለበት፤ እና ሌላ ጦርነት ሊኖር አይችልም፤ የኒውለክሌር ጦር መሣሪያ አይኖርም።

    “ከእንግዲህ በኋላ የኒውክሌር ጦር መሣሪያ አይኖራቸውም። በዚያ ይስማማሉ። ያለዚያ ግን ስምምነት አይኖርም” ሲሉ ተናግረዋል።