ተጨማሪ ወታደሮቿ እና የጦር መርከቧ ወደ ባሕረ ሰላጤው የደረሱት አሜሪካ የእግረኛ ዘመቻ ለማካሄድ መዘጋጀቷ ተነገረ

ቅዳሜ ዕለት በሺዎች የሚቆጠሩ ተጨማሪ ወታደሮች እና አንድ የጦር መርከቧ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ የደረሱት የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስቴር ፔንታገን በኢራን ውስጥ ለሳምንታት የሚቆይ የእግረኛ ሠራዊት ዘመቻ ለማካሄድ እየተዘጋጀ መሆኑ ተገለጸ።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. እስራኤል ከየመን ሚሳዔል እንደተተኮሰባት ገለጸች

    የየመን ሁቲዎች ኢራንን በመደገፍ ጦርነቱን እንደሚቀላቀሉ አስታውቀው ነበር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የየመን ሁቲዎች ኢራንን በመደገፍ ጦርነቱን እንደሚቀላቀሉ አስታውቀው ነበር

    የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት ከየመን ሚሳዔል መተኮሱን እንደለየ አስታወቀ። የዜና ወኪሎቹ ሮይተርስ እና አጃንስ ፍራስ ፕሬስ (ኤኤፍፒ)፤ አንድ ወር የሞላው የኢራን ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ ከየመን ወደ እስራኤል ሲተኮስ ይህ የመጀመሪያው እንደሆነ ዘግበዋል።

    የእስራኤል ጦር በቴሌግራም ገጹ ባሰፈረው መልዕክት፤ መከላከያ ሠራዊቱ ከየመን ወደ እስራኤል ግዛት ሚሳዔል መተኮሱን ለይቷል፤ የአየር መከላከያ ስርዓቶች ስጋቱን ለመቀልበስ እየሰሩ ነው” ብሏል። ከ15 ደቂቃ ካነሰ ቆይታ በኋላም በመላ አገሪቱ የሚገኘው ሕዝብ ጥብቅ ከሆኑትን ስፍራዎች መውጣት እንደሚችሉ አስታውቋል።

    እስራኤል ሚሳዔል እንደተተኮሰባት የገለጸችው በኢራን የሚደገፈው የየመኑ ሁቲ ቃል አቀባይ ቴህራን ላይ የሚፈጸመው ጥቃት የሚቀጥል ከሆነ አማጺው ቡድን የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነትን እንደሚቀላቀል ከተናገሩ በኋላ ነው።

    የመኑ ጦር ኃይሎች የተባለው የሁቲ ወታደራዊ ክንፍ ቃል አቀባይ የሆኑት ያህያ ሳሪ ቴሌግራም ላይ ባወጡት መግለጫ፤ ሦስት ሁኔታዎች የሚፈጸሙ ከሆነ “ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት ለማድረግ ጣቶቻችን ቃታው ላይ ናቸው” ብለዋል።

    ቃል አቀባዩ የገለጿቸው ሦስት ሁኔታዎች የሚከተሉት ናቸው፦

    • አሜሪካ እና እስራኤል ኢራን ላይ የከፈቱትን ጦርነት ሌላ አገር የሚቀላቀል ከሆነ
    • አሜሪካ እና እስራኤል “ቀይ ባሕርን በኢራን እስላማዊ ሲፐብሊክ እና ማንኛውም ሙስሊም አገር ለሚፈጸመው ጠበኛ ዘመቻ የሚጠቀሙ ከሆነ”
    • ኢራን ላይ የሚካሄደው “ግጭት የሚባባስ” ከሆነ

    መግለጫው አክሎም፤ ይህ እርምጃ "ጠላቶቹ አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ፣ በፍልስጤም እና ጋዛ፣ በኢራቅ እንዲሁም በሊባኖስ ላይ ለሚፈጽሙት የቀጠለ ጥቃት" የተሰጠ ምላሽ መሆኑን ገልጿል።

  2. አንድ ወር በሞላው የኢራን ጦርነት ምን ያህል ሰላማዊ ሰዎች ተገደሉ?

    በኢራን በተፈጸመ ጥቃት የፈረሰ የመኖርያ ሕንጻ

    የፎቶው ባለመብት, Shutterstock

    የምስሉ መግለጫ, በኢራን በተፈጸመ ጥቃት የፈረሰ የመኖርያ ሕንጻ

    መቀመጫውን አሜሪካ ያደረገው የሰብዓዊ መብቶች አክቲቪስቶች ዜና ወኪል ሃራና፣ አንድ ወሩን ዛሬ በያዘው የኢራን ጦርነት 217 ሕጻናትን ጨምሮ 1464 ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸውን ዘግቧል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በቴህራን ላይ ጦርነት የከፈቱት የካቲት 21 2018 ዓ.ም. ነበር።

    የእስራኤል መከላከያ ከ12ሺህ በላይ ቦምቦችን በመላ ኢራን መጠቀሙን ሲገልጽ በቴህራን ብቻ 3,600 ተጠቅሞ ድብደባ ፈጽሟል።

    አሜሪካ እንዲሁ በመላ ኢራን ከ9ሺህ በላይ ዒላማዎችን በመለየት ድብደባ መፈጸሟን ገልጻለች።

    አሜሪካ እና እስራኤል ዒላማ አድርገው ድብደባ የፈጸሙባቸው አብዛኛዎቹ ፖሊስ ጣቢያዎች፣ ወታደራዊ እና ፖሊስ ዩኒቨርስቲዎች፣ የፖሊስ ዋና መሥሪያ ቤት፣ የመጠለያ ቤቶች፣ የአብዮታዊ ዘብ ቤቶች፣ እንዲሁም ኬላዎች እና የጦር መሣሪያ ማከማቻዎች ይሆናሉ ተብለው የሚታሰቡ ስፈራዎች እንደሆኑ ዘገባው ያስረዳል።

    እነዚህ ዒላማዎች ብዙ ጊዜ የሚገኙት ሰላማዊ ሰዎች በሚኖሩባቸው እና እንቅስቃሴዎች በሚበዛባቸው አካባቢዎች ነው።

    በኢራን ጥቃት ሲፈጸም የተመለከተ ነዋሪ ለቢቢሲ እንደተናገረው በሰላማዊ ሰዎች መኖሪያ የሚፈጸሙ ድብደባዎች የመንግሥት ተቃዋሚ የነበሩትን ሁሉ ያስቆጣ ነው።

    ቢቢሲ በሪፖርቱ ላይ ስለተገለጹት የሰላማዊ ሰዎች መኖሪያዎች ለእስራኤል ጦር ጥያቄ ቢያቀርብም ጥቃቶቹ መፈጸማቸውን ከማረጋገጥ ውጪ ተጨማሪ ምላሽ ሳይገኝ ቀርቷል።

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር ለጥያቄዎቹ ምላሽ አልሰጠም።

    ኢራን በጦርነቱ ውስጥ የአሜሪካ አጋር በሆኑት የባሕረ ሰላጤው አገራት የሚገኙ አውሮፕላን ማረፊያዎችን፣ ሆቴሎችን እንዲሁም የሰላማዊ ዜጎች መኖሪያዎችን እና ሌሎች መሠረተ ልማቶችን አጥቅታለች።

    በኢራን የኢንተርኔት እና የኮሚኒኬሽን አገልግሎት በተቋረጠበት ሁኔታ በርካቶች ቀጣዩ የጥቃት ዒላማ የቱ እንደሚሆን ለማወቅ እንደማይችሉ በመግለጽ ፍርሃታቸውን ያስረዳሉ።

  3. በሳዑዲ አረቢያ የጦር አውሮፕላን ማረፊያ ላይ በተፈጸመ ጥቃት ቢያንስ 12 የአሜሪካ ወታደሮች ተጎዱ

    ኢራን በሳዑዲ አረቢያ ልዑል ሱልጣን የጦር አውሮፕላን ማረፊያ ላይ በፈጸመችው ጥቃት ቢያንስ 12 የአሜሪካ ወታደሮች ላይ ጉዳት መድረሱን በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ዘገበ።

    ጥቃቱ ሲፈጸም በሕንጻው ውስጥ ነበሩ የተባሉ ቢያንስ ሁለት ወታደሮች “በጣም ከባድ ጉዳት” እንደ ደረሰባቸው ዎል ስትሪት ጆርናል ዘግቧል።

    ጥቃቱ የተፈጸመው በአንድ ሚሳዔል እና በበርካታ ድሮኖች ሲሆን በርካታ አየር ላይ ነዳጅ የሚሞሉ አውሮፕላኖችም ጉዳት ደርሶባቸዋል ሲሉ ኒው ዮርክ ታይምስ እና ዎል ስትሪት ጆርናል ዘግበዋል።

    ፔንታጎን እና የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ መገናኛ ብዙኃን ላቀረቡላቸው ጥያቄዎች እስካሁን ድረስ ምላሽ አልሰጡም።

  4. ቴህራን ውስጥ በመኖሪያ ሕንጻ ላይ ጥቃት ተፈጸመ

    ጥቃት የደረሰበት ሕንጻ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዛሬ አርብ በኢራን ዋና ከተ ማቴህራን ውስጥ በሚገኝ የመኖሪያ ሕንጻ ላይ የተፈጸመ ጥቃትን የሚያሳዩ ፎቶግራፎች እየወጡ ነው።

    ከጥቃቱ በኋላ የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች በፍርስራሾች ውስጥ የተቀበሩ ሰዎችን ለማውጣት ከስፍራው ደርሰው ጥረት ሲያደርጉ ታይተዋል።

    በኢራን ውስጥ ባለው የኢንተርኔት መቋረጥ ምክንያት ፎቶዎችን እና ዝርዝር መረጃዎችን ለማግኘት አዳጋች ሆኗል።

    በተጨማሪም ዓለም አቀፍ የዜና ድርጅቶች ወደ አገሪቱ ገብተው ለመዘገብ የሚያስፈልጋቸውን ቪዛ እና ፈቃድ ማግኘት ስለማይችሉ ከኢራን ዜና እና መረጃ ማግኘት አዳጋች ነው።

    ጥቃት በተፈጸመበት ቦታ የተገኙ ነዋሪዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች በጥተቱ ስፍራ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በፍርስራሽ አካባቢ የሚታዩ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

  5. የዓለም የነዳጅ ዋጋ በማን ነው የሚወሰነው?

    ነዳጅ ማምረቻ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ነዳጅ በዓለም ምጣኔ ሀብት ላይ ከፍተኛ የሆነ ተጽእኖ አለው። የነዳጅ ዋጋ ሲቀንስ የምርቶች ዋጋ እንዲቀንስ እና የአገራት ምጣኔ ሀብት እንዲነቃቃል የማድረጉን ያህል፣ ዋጋው ሲጨምር ደግሞ በሁሉም ዘርፎች ላይ መናጋትን ያስከትላል።

    አሁን እንዳጋጠመው ዓይነት በነዳጅ ምርት እና አቅርቦት ላይ የሚታይ መስተጓጎል የነዳጅ ዋጋ መጨመርን በማስከተል በዓለም ዙሪያ ቀውስን ያስከትላል። ለመሆኑ የነዳጅ ዋጋን ማን ነው የሚወስነው?

    የነዳጅ ዋጋ የሚወሰነው “በገበያ” ነው። በገበያ ሲባል ደግሞ ነዳጅ የሚያመርቱ አገራት እና ኩባንያዎች እንዲሁም የነዳጅ ነጋዴዎች ይገኙበታል።

    አገራት የሚባሉት ነዳጅ አምራች የሆኑ 23 አገራት የነዳጅ ዋጋን ለመቆጣጠር እና ለመወሰን ለገበያ የሚያቀርቡትን ምርት በጋራ ለመወሰን የመሠረቱት ድርጅት ኦፔክ ከፍተኛ ተጽእኖ አለው።

    አገራቱ የነዳጅ ዋጋ በዓለም ገበያ ላይ ዋጋው እንዲጨምር ሲፈልጉ ምርታቸውን ይቀንሳሉ። ዋጋው እንዲወርድ ከስምምነት ሲደርሱ ደግሞ ለገበያ የሚያቀርቡትን ምርት ይጨምራሉ።

    በአሜሪካ መረጃ መሠረት በ2022 የኦፔክ አባል አገራት 59 በመቶውን የዓለም የነዳጅ ፍላጎት ያቀርባሉ። ነገር ግን የነዳጅ ዋጋን ሙሉ ለሙሉ አይቆጣጠሩም።

    በተጨማሪም ሼልን የመሳሰሉ ግዙፍ የነዳጅ ኩባንያዎች እና አሜሪካንን የመሳሰሉ ከኦፔክ ውጪ ያሉ ታላላቅ ነዳጅ አምራቾችም በዋጋው ላይ የራሳቸው ተጽእኖ አላቸው።

    በዋጋው ላይ ሚና ያላቸው ሌሎቹ ደግሞ ግለሰቦች እና የኢንቨስትመን ኩባንዎች ወይም ነዳጅ ገዝተው በገበያ ላይ የሚሸጡ አካላት የሚገኙበት የነዳጅ ነጋዴዎች ናቸው።

    እነዚህ ነጋዴዎች ለወደፊት በሚል ስምምነት በተደረሰበት ዋጋ እና ኮንትራ መሠረት አስቀድመው ከአምራቾች ላይ ነዳጅ ለመግዛት ይስማማሉ። በሌላ አባባል በተንበያ ላይ በመመሥረት ዋጋ ተምነው ነዳጅ ለመግዛት ከጊዜው በፊት ይወስናሉ።

  6. በኢራን ወሳኙ ሥልጣን ያላቸው እነማን ናቸው? የትኞቹስ ተገደሉ?

    ባለፈው አንድ ወር በርካታ የኢራን ከፍተኛ ወታደራዊ እና ፖለቲካዊ መሪዎች በአሜሪካ እና በእስራኤል በፈጸሙባቸው ጥቃቶች ተገድለዋል።

    ነገር ግን ፕሬዝዳንት ትራምፕ እንዳዘዙት ኢራን እጇን ሳትሰጥ ከአሜሪካ ጋር ለመደራደር የራሷን ቅድመ ሁኔታ አቅርባለች።

    አገሪቱን አርባ ዓመታት ለሚጠጋ ጊዜ በበላይነት ያስተዳደሩት ጠቅላይ መሪው አያቶላህ አሊ ኻሜኒን ጨምሮ ቁልፍ መሪዎቿ የተገደሉባት ኢራን ተተኪዎችን በመሰየም ቀጥላለች።

    በኢራን ሥርዓት ውስጥ ወሳኙ ሥልጣን ያላቸው እነማን ናቸው? የትኞቹስ ባለፈው አንድ ወር ውስጥ ተገደሉ? ተጨማሪ እዚህ ያንብቡ አሜሪካ እና እስራኤል ብዙዎቹን የኢራን መሪዎችን ገድለዋል፤ ትራምፕ ከማን ጋር ሊደራደሩ ይችላሉ?

    ፎቶግራፎች
  7. የተባበሩት መንግሥታት በኢራን ትምህርት ቤት ላይ የተፈጸመው ጥቃት እንዲመረምር ጠየቀ

    ከፍርስራሽ ውስጥ ሰዎችን ለማውጣት የሚሞክሩ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ጥቃቱ የተፈጸመበት ሚናብ ውስጥ የሚገኘው ትምህርት ቤት

    የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር ቮልከር ተርክ በኢራን ላይ ጥቃት በተከፈተበት በመጀመሪያው ዕለት በደቡብ ኢራን በሴቶች ትምህር ቤት ላይ የተፈጸመው ጥቃት ላይ አስቸኳይ ምርመራ እንዲደረግ ጠየቁ።

    በትምህርት ቤቱ ላይ በተፈጸመው ጥቃት አብዛኞቹ ልጆች የሆኑ 168 ሰዎች መገደላቸውን ባለሥልጣናት የገለጹ ሲሆን፣ የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን መርማሪዎች የአሜሪካ ኃይሎች “ባላሰቡት ሁኔታ” ትምህርት ቤቱን ዒላማ አድርገዋል ብለው እንደሚያምኑ ዘግበዋል።

    የመንግሥታቱ ድርጅት ባለሥልጣን ቮልከር ተርክ በጦርነት ውስጥ ልጆችን በመጠበቅ ዙሪያ በተደረገ ስብሰባ ላይ በትምህርት ቤቱ ላይ “ጥቃቱን የፈጸሙት አስቸኳይ፣ ገለልኛ፣ ግልጽ እና ተጠያቂነት የሚያሰፍን ምርመራ” እንዲየደርጉ ጠይቀዋል።

    ባለሥልጣኑ ጥቃቱ “ከባድ የሆነ አስፈሪ ሁኔታን የፈጠረ በመሆኑ” ምርመራው በአስቸኳይ ተደርጎ ውጤቱም ይፋ እንዲደረግ ባሳሰቡበት ንግግር “ከፍተኛ የአሜሪካ ባለሥልጣናት ጥቃቱ ላይ ምርመራ እየተደረገ መሆኑን” እንደተናገሩ ገልጸዋል።

    ተርክ ጨምረውም "በአገራት መካከል የቱንም ዓይነት ልዩነት ቢኖርም፣ እነዚህ ልዩነቶች ተማሪ ልጆችን በመግደል እንደማይፈቱ ሁላችንም እንስማማለን” ብለዋል፥

    የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እና አሜሪካ በትምህርት ቤቱ ላይ በተፈጸመው ጥቃት ዙሪያ ምርመራ እያደረጉ መሆናቸውን በተናጠል አሳውቀዋል።

  8. ኢራን በሆርሙዝ በኩል ሊያልፉ የነበሩ ሦስት መርከቦችን መመለሷን አሳወቀች

    በሆርሙዝ በኩል የሚያልፍ በኩል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ዛሬ ጠዋት በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ሊያልፉ የነበሩ ሦስት የጭነት መርከቦችን ማስመለሱን አስታወቀ።

    "የተለያዩ አገራት ንብረት የሆኑ ኮንቴይነር የጫኑ ሦስት መርከቦች፤ እንዲያልፉ የተፈቀደላቸው መርከቦች በሚጓዙበት የተለየ መስመር በኩል ለማለፍ ሞክረው ነበር። የአብዮታዊ ዘቡ ባሕር ኃይል ማስጠንቀቂያ ከሰጣቸው በኋላ ወደ መጡበት ተመልሰዋል” ይላል የወጣው መግለጫ።

    የአብዮታዊ ዘቡ መግለጫ ጨምሮም "የሆርሙዝ ወሽመጥ የተዘጋ በመሆኑ የትኛውም ለማለፍ የሚሞክር መርከብ ጠንካራ ምላሽ ይጠብቀዋል” ብሏል።

    “የአሜሪካ እና የእስራኤል አጋሮች እና ደጋፊዎች ከሆኑ አገራት ወደቦች የሚነሱ እና ወደዚያ የሚያመራ የትኛውም ዓይነት መርከብ በሆርሙዝ በኩል እንዳያልፍ ተከልክሏል” ብሏል መግለጫው።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ለአገሪቱ ቴሌቪዥን “ከቻይና፣ ከሩሲያ፣ ከፓኪስታን፣ ከኢራቅ እና ከሕንድ” መርከቦቻቸው በሆርሙዝ በኩል እንዲያልፉ ጥያቄ እንደቀረበላቸው ተናግረዋል።

    ጨምረውም በኢራን ዕይታ ሆርሙዝ “ሙሉ ለሙሉ አልተዘጋም ነገር ግን ለጠላቶቻችን ዝግ ነው” ብለዋል።

  9. ኢራን በመካከለኛው ምሥራቅ ከአሜሪካ ጦር አቅራቢያ ያሉ ነዋሪዎች አካባቢዎቹን ለቅቀው እንዲወጡ አስጠነቀቀች

    የኢራን ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በመካከለኛው ምሥራቅ አካባቢ የአሜሪካ ጦር ባለባቸው ቦታዎች የሚኖሩ ሰዎች አካባቢውን ለቅቀው እንዲወጡ አስጠነቀቀ።

    ከአብዮታዊ ዘቡ ጋር ግንኙነት ያለው የፋርስ የዜና ወኪል የወጣው የወታደራዊ ኃይሉ መግለጫ፤ አሜሪካ እና እስራኤል "የሲቪል ቦታዎችን እና ንፁኃን ሰዎችን እንደ ሰብአዊ ጋሻ ተጠቅመዋል" ሲል ከስሷል። መግለጫው በተጨማሪ አሜሪካ ሲቪሎችን እና የኢራን ባለሥልጣናትን ገድላለች በማለት ክስ አቅርቧል።

    ጦርነቱ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ አብዮታዊ ዘቡ በርካታ ማስጠንቀቂያዎችን ሰጥቷል። ከዚህ ቀደም በመካከለኛው ምሥራቅ በአሜሪካ የኢንዱስትሪ ቦታዎች አቅራቢያ የሚኖሩ ነዋሪዎች ለቅቀው እንዲወጡ አስጠንቅቆ ነበር።

    አሁን ባወጣው ማስጠንቀቂያው ላይ ግን ምንም ዓይነት ቦታዎችን በግለጽ ሳይጠቅስ አጠቃላይ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል።

    አንድ ወር በሞላው ጦርነት አብዮታዊ ዘቡ ከፍተኛ አዛዦቹ ተገድለውበታል።

    ምንም እንኳን ኢራን ከቅርብ ቀናት ወዲህ የሟቾችን ቁጥር በይፋ ባታሳውቅም በአሜሪካ የሚገኘው የሰብአዊ መብት ተሟጋች የዜና ወኪል (ህራና) እንደዘገበው፤ እስካሁን 1,492 ሕጻናትን ጨምሮ 221 ኢራናውያን ሲቪሎች ተገድለዋል። 1,167 የኢራን ጦር ሠራዊት አባላት መገደላቸውንም የዜና ወኪሉ ዘግቧል።

  10. እስራኤል የኢራንን ‘ዋነኛ’ የሚሳዔል እና የባሕር ላይ ፈንጂዎች ማምረቻን መምታቷን አስታወቀች

    ሆርሙዝ ወሽመጥ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ተመታ የተባለው ተቋም በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ስጋት የፈጠሩ የባሕር ላይ ፈንጂዎችን የሚያመርት ነው

    አንድ ወር በሞላው አሜሪካ እና እስራኤል ከኢራን ጋር እያደረጉት ባለው ጦርነት የእስራኤል ጦር ዛሬ አርብ በኢራን ውስጥ በፈጸመው ጥቃት ወሳኝ የአገሪቱን የጦር መሣሪያ ማምረቻ መምታቱን አስታወቀ።

    የእስራኤል አየር ኃይል በፈጸመው ጥቃት የኢራን “ዋነኛ የሚሳዔሎች እና የባሕር ላይ ፈንጂዎች ማምረቻ” ተቋም መመታቱን የአገሪቱ ጦር ገልጿል።

    በማዕከላዊ ኢራን ያዝድ በተባለው ግዛት ውስጥ የሚገኘው ጥቃት የተፈጸመበት ቦታ የአገሪቱ ባሕር ኃይል አብዛኞቹን ሚሳዔሎች እና ባሕር ላይ የሚጠመዱ ፈንጂዎችን የሚያመርትበት መሆኑን እስራኤል አስታውቃለች።

    ኢራን በሺዎች የሚቆጠሩ ባሕር ላይ የሚጠመዱ ፈንጂዎች እንዳላት ይታመናል። ምንም እንኳ እነዚህን ፈንጂዎች በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ አጥምዳቸው ስለመሆኑ ግልጽ ባይሆንም ፈንጂዎቹ በግዙፍ የንግድ መርከቦች ላይ ሊያደርሱ የሚችሉትን ከባድ ጉዳት በመፍራት የመርከቦች እንቅስቃሴ ተገትቷል።

  11. አንድ መኪና እስራኤል ውስጥ በኢራን ሚሳዔል የተመታበትን ቅጽበት የሚያሳይ ቪዲዮ

    ኢራን ለተከፈተባት ጥቃት አጸፋ በእስራኤል እና በሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ ያልተቋረጠ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን እየፈጸመች ነው። አገራቱ ሚሳዔሎችን በፀረ ሚሳዔል ለማክሸፍ እየሞከሩ ቢሆንም በሁሉም ላይ ግን አልተሳካላቸውም።

    በዚህም ሳቢያ በሰው እና በንብረት ላይ ጉዳት እየደረሰባቸው ነው። በዚህ ቪዲዮ ላይ የእስራኤል ሠራዊት ከኢራን የተተኮሰ ነው ያለው ሚሳዔል አንድ መኪና ሲመታ ይታያል።

  12. በእስራኤል የተገደሉት የኢራን አብዮታዊ ዘብ ባሕር ኃይል አዛዥ ማን ናቸው?

    አሊሬዛ ታንግሲሪ

    የፎቶው ባለመብት, Tehran Times

    እስራኤል በሆርሙዝ ባሕር ወሽመጥ ላይ ያለውን አጠቃላይ እገዳ የሚቆጣጠረውን የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የባሕር ኃይል አዛዥ መግደሏን አስታወቀች።

    የእስራኤል የመከላከያ ሚኒስትር ኢዝራኤል ካትዝ እንዳሉት፣ የኢራን የባሕር ኃይል አዛዥ የሆኑት አሊሬዛ ታንግሲሪ "በቀጥታ የሽብር ተግባር የቦምብ ጥቃት በመፈጸም እና የሆርሙዝ ወሽመጥን በመዝጋት በቀጥታ ተጠያቂ ነበር" ብለዋል። አሁን "ተወግዷል" ሲሉም ተናግረዋል። ሙሉውን ዘገባ እዚህ ያንብቡ እስራኤል ገደልኳቸው ስላለቻቸው የኢራን ባሕር ኃይል አዛዥ ምን ይታወቃል?

  13. ዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኤነርጂ የኒውክሌር ተቋማት ጥቃት ከቀጠለ “ትልቅ የራዲዮሎጂ አደጋ” እንደሚከሰት አስጠነቀቀ

    የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ተቋም

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኤነርጂ ኤጀንሲ፤ በኢራን የኒውክሌር ተቋማት አቅራቢያ የሚፈጸም ጥቃት የሚቀጥል ከሆነ “ትልቅ የራዲዮሎጂ አደጋ” ያስከትላል ሲል አስጠነቀቀ።

    የተባበሩት መንግሥታቱ ተቋም ማስጠንቀቂያ የሰጠው በኢራን ደቡብ ምዕራባዊ ክፍል የሚገኘው የቡሼራ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ተቋም አቅራቢያ ማክሰኞ ዕለት በድጋሚ ጥቃት እንደተፈጸመ ከተገለጸ በኋላ ነው።

    የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ራፋኤል ግሮሲ በኢራኑ የኒውክሌር ተቋም አቅራቢያ እየተደጋገመ ያለው “ሰሞነኛው ወታደራዊ ጥቃት እጅግ እንዳሳሰባቸው” ገልጸዋል።

    ዋና ዳይሬክተሩ “ትልቅ ቁጥር ያለው የኒውክሌር ቁስ ይዞ የሚሰራ የኔውክሌር ኃይል ማመንጫ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ፤ በተቋሙ ላይ የሚደርስ ጉዳት ትልቅ የራዲዮሎጂ አደጋ ሊያስከትል እንደሚችል” ማስጠንቀቃቸውን በተቋሙ የኤክስ ገጽ ላይ የወጣው ጽሁፍ ያስረዳል።

    በዚህ ስፍራ የሚከሰት የራዲዮሎጂ አደጋ “ኢራን ውስጥ እና ከዚያም ባሻገር ሰፊ አካባቢን” ሊጎዳ እንደሚችልም ገልጸዋል።

    ይህንን አይነቱን የኒውክሌር አደጋ ስጋት ለማስወገድ ሲባል የጦርነቱ ተፋላሚ አገራት ወታደራዊ እርምጃዎችን ከመውሰድ እንዲቆጠቡ ዋና ዳይሬክተሩ ጠይቀዋል። “በግጭት ወቅት ሰባቱን የኒውክሌር ደኅንነት ማረጋገጫ አምዶች መጠበቅ አስፈላጊ” እንደሆነም አጽንኦት ሰጥተዋል።

  14. ዶናልድ ትራምፕ 10 ሺህ ወታደሮችን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ለማሰማራት እንዳሰቡ ተዘገበ

    የአሜሪካ ወታደሮች

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተጨማሪ 10 ሺህ ወታደሮችን በግጭት ውስጥ አንድ ወር ወዳስቆጠረው መካከለኛው ምሥራቅ ለመላክ እያሰቡ መሆናቸው ተዘገበ።

    ዎል ስትሪት ጆርናል እንደዘገበው ትራምፕ በሺዎች የሚቆጠሩትን እግረኛ ወታደሮች ወደ ቀጣናው የሚያሰማሩት በአካባቢው ባሉ ግዙፍ መርከቦችን እና ጦር ሰፈሮች ከሚገኙት የአገሪቱ ወታደሮች በተጨማሪ ነው።

    ወታደሮቹን የማሰማራቱ ሃሳብ ትራምፕ “ከኢራን ጋር የሰላም ንግግር ለማካሄድ እየተዘጋጁ ባለበት ጊዜ መሆኑ ተጨማሪ ወታደራዊ አማራጭን” የሚሰጣቸው እንደሚሆን ጋዜጣው ጨምሮ ጽፏል።

    ወደ መካከለኛው ምሥራቅ የሚላከው ጦር እግረኛ ሠራዊት እና ብረት ለበስ ተሽከርካሪዎችን የሚካትት ይሆንል ተብሎ እንደሚጠበቅ የተዘገበ ሲሆን፣ ይህም ወደ አካባቢው ቀድሞውንም ከተላኩት አምስት ሺህ የአሜሪካ ባሕር ኃይል ወታደሮች ተጨማሪ ነው።

    ነገር ግን ፕሬዝዳንቱ ወደ ባሕረ ሰላጤው አካባቢ ለማሳመራት ያሰቧቸው እነዚህ ወታደሮች በትክክል ወደ የት እንደሚላኩ የተገለጸ ነገር የለም።

    ቢቢሲ በጉዳዩ ላይ የፕሬዝዳንቱን ጽህፈት ቤት እና የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስቴር ፔንታገን አስተያየት እንዲሰጡ ጥያቄ አቅርቧል።

  15. የእስራኤል ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ መንግሥት ሠራዊቱን “ያለ ስትራቴጂ ወደ ጦርነት”እያስገባ ነው በማለት ተቹ

    የእስራኤል ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ የሆኑት ያኢር ላፒድ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የእስራኤል ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ የሆኑት ያኢር ላፒድ የአገሪቱ መንግሥት ያለ ስትራቴጂ እና በጥቂት ወታደሮች ብቻ ሠራዊቱን ወደ ጦርነት እየላከ ነው ሲሉ ከሰሱ።

    ላፒድ በቪዲዮ ባስተላልፉት መልዕክት፤ “የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት እስከ መጨረሻው እና ከዚያም በላይ ተወጥሯል። መንግሥት ሠራዊቱን ጦር ሜዳ ላይ እንደቆሰለ ትቶታል” ብለዋል።

    የእስራኤል መንግሥት ሠራዊቱን “ያለ ስትራቴጂ፣ አስፈላጊው ሁኔታ ሳይኖር፣ እጅግ አነስተኛ በሆነ የወታደር ቁጥር ወደ ባለ ብዙ ግንባር ጦርነት" እያስገባው ነው በማለትም ተናግረዋል።

    የሠራዊቱ ተጠባባቂ ኃይል “ደክሟል፣ ዝሏል፤ ከዚህ በላይ የደኅንነት ተግዳሮቶችን መቋቋም አይችልም" ሲሉም ተደምጠዋል።

    የተቃዋሚ ፓርቲ መሪው አክለውም መንግሥት፤ ሙሉ ጊዜያቸውን የአይሁድ ቅዱሳን መጻሕፍትን በማጥናት የሚያሳልፉት እና እስራኤል በአውሮፓውያኑ 1948 ከተመሠረተች ጀምሮ ከግዴታ ውትድርና ነፃ ከተደረጉት "ሃሬዲ" ኦርቶዶክስ አይሁዳውያን ማኅበረሰብ አባላትን በተጠባባቂ ወታደርነት እንዲመለምል ጥያቄ አቅርበዋል።

    ላፒድ ይህንን የተናገሩት የሠራዊቱ ወታደራዊ አዛዥ ሌተናንት ጄነራል ኢያል ዛሚር ሐሙስ ዕለት በደኅንነት ካቢኔ ስብሰባ ላይ “የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት ለመውደቅ ጫፍ ላይ” ደርሷል እንዳሉ ከተዘገበ በኋላ ነው።

  16. ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራን ኃይል ማመንጫዎችን ለመምታት ያስቀመጡትን ቀነ ገደብ በ10 ቀናት አራዘሙ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን እስከ አርብ ድረስ የማትከፍት ከሆነ የኃይል ማመንጫዎቿን እንደሚደበድቡ ዝተው የነበሩት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የሰጡትን ቀነ ገደብ በአስር ቀናት አራዘሙ።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለመጀመሪያ ጊዜ የ48 ሰዓታት ቀነ ገደብ ያስቀመጡት ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ ነበር። የተቀመጠው ጊዜ እየተቃረበ ሲመጣ ፕሬዝዳንቱ ከኢራን ጋር ንግግር እየተካሄደ መሆኑን በመጥቀስ ተጨማሪ አምስት ቀናት መስጠታቸው ይታወሳል።

    ትራምፕ ትናንት ምሽት በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት፤ ከኢራን ጋር የሚደረገው ንግግር “በጣም በጥሩ ሁኔታ እየሄደ” መሆኑን ገልጸዋል።

    “ንግግሮቹ በመካሄድ ላይ ናቸው፤ በሀሰተኛ መገናኛ ብዙኃን እና በሌሎችም ከሚሰራጩት የተሳሳቱ መግለጫዎች በተቃራኒ ንግግሩ በጣም በጥሩ ሁኔታ ላይ ይገኛል” ብለዋል።

    አክለውም “በኢራን መንግሥት ጥያቄ መሠረት” የያዙትን “የኤነርጂ ማመንጫ የማውደም” እቅድ እስከ መጋቢት 28/2018 ዓ.ም. ማራዘማቸውን አስታውቀዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ከዚህ መልዕክታቸው በኋላ ከፎክስ ኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ፤ ኢራን በሰባት ቀናት እንዲራዘምላት ብትጠይቅም 10 ቀናት እንደሰጡ ሲናገሩ ተደምጠዋል። በዚህም ቴህራን “እጅግ አመስጋኝ” ሆናለች ብለዋል።

    “በሰዎቼ በኩል፣ በጣም በትህትና 'ተጨማሪ ጊዜ ማግኘት እንችላለን?' አሉኝ” ሲሉ ከፎክስ ኒውስ ጋር በስልክ ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ገልጸዋል።

    "የጠየቁት ሰባት [ቀናት] ነበር። እኔ ግን መርከቦችን ስለሰጡኝ 'አስር እሰጣችኋለሁ' አልኳቸው። ታውቃለህ፤ ስለ ስምንቱ መርከቦች ተነጋግረናል። ባለፈው ቀን ስናገር የነበረው ‘ስጦታ’ ማለት ነው” ሲሉም ተደምጠዋል።

    ትራምፕ ከቀናት በፊት ኢራን “እጅግ ከፍተኛ ገንዘብ የሚያወጣ ትልቅ ስጦታ” እንዳቀረበችላቸው ሲናገሩ ነበር። በወቅቱ ‘ስጦታው’ ከሆርሙዝ ወሽመጥ ጋር የሚያያዝ እንደሆነ ቢጠቅሱም ዝርዝር መረጃ ከመስጠት ተቆጥበው ነበር።

    አሁን ይህ ስጦታ ኢራን በተዘጋው ወሽመጥ በኩል መርከቦች እንዲያልፉ ማድረጓ እንደሆነ ጠቅሰዋል። ፕሬዝዳንቱ ትናንት በዋይት ሀውስ ባደረጉት የካቤኒ ስብሰባ ላይም ኢራን 10 መርከቦች እንዲያልፉ መፍቀዷን ሲናገሩ ነበር።

    ኢራን በበኩሏ ከአሜሪካ ጋር ንግግር እየተካሄደ ነው መባሉን አስተባብላለች። አንድ የሰላም ንግግር አሸማጋይ ደግሞ ኢራን በኃይል ማመንጫዎች ላይ ይፈጸማል የተባለው ጥቃት እንዲራዘምላት እንዳልጠየቀች መናገራቸውን ዎል ስትሪት ጆርናል ዘግቧል።

  17. የየመኑ ሁቲ ኢራንን በመደገፍ እርምጃ ለመውሰድ ዝግጁ መሆኑን አስታወቀ

    መሳሪያ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, ከዚህ ቀደም ሁቲዎች በቀይ ባሕር በሚያልፉ መርከቦች እና እስራኤል ላይ ጥቃቶችን ፈጽመው ነበር

    የኢራን አጋር የሆነው የየመኑ ታጣቂ ቡድን ሁቲ አስፈላጊ በሚሆን ጊዜ ኢራንን በመደገፍ በጦርነቱ ውስጥ ለመሳተፍ ዝግጁ መሆኑን አንድ የቡድኑ መሪ ለሮይተርስ ተናገረ።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት ከከፈቱ በኋላ ድምጹን አጥፍቶ የነበረው የየመኑ ቡድን፤ ወደ ጦርነቱ የሚገባ ከሆነ ከዚህ ቀደም እንዳደረገው በቀይ ባሕር የመርከቦች እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ አደጋ የሚደቅን ይሆናል።

    ስሙ እንዳይገለጽ የጠየቀው የሁቲ መሪ፤ "በሁሉም አማራጮች ሙሉ ለሙሉ ወታደራዊ ዝግጅት አድርገናል። የሚሆነውን በሙሉ እየተከታተልን ነው፣ መቼ እርምጃ መውሰድ እንዳለብን እናውቃለን” ሲል ለሮይተርስ በሰጠው ቃል የቡድኑን አቋም አሳውቋል።

    እስራኤል በጋዛ ላይ ጥቃት በከፈተችበት ጊዜ ሁቲዎች ሚሳዔሎችን ወደ እስራኤል ከማስወንጨፋቸው በተጨማሪ በቀይ ባሕር በኩል የሚያልፉ መርከቦችን በመምታት አስጥመው ነበር። በዚህ ጥቃታቸውም የባሕር እንቅስቃሴውን አስተጓጉለው ነበር።

    አሁንም ለኢራን ያላቸውን አጋርነት ለማሳየት በወሳኙ የቀይ ባሕር መተላለፊያ መስመር ላይ ጥቃት እንደሚሰነዝሩ ዝተዋል። ይህም በሆርሙዝ ሰርጥ መዘጋት የተቃወሰውን የባሕር ላይ እንቅስቃሴ የበለጠ በማወሳሰብ የነዳጅ እና የሸቀጦች ዝውውርን አዳጋች እንደሚያደርገው ይታመናል።

    በኢራን ላይ የተከፈተውን ጥቃት ተከትሎ የሊባኖሱ ሄዝቦላህ እና በኢራቅ የሚገኙ ቡድኖች ኢራንን ደግፈው ጥቃት እየፈጸሙ ሲሆን፣ ከፍተኛ ወታደራዊ አቅም ያለው የሁቲ ታጣቂ ቡድን ግን እስካሁን ምንም ዓይነት እርምጃ ሳይወስድ በዝምታ ቆይቶ ነበር።

  18. ኢራን ከትራምፕ ተቃራኒ የሆኑ የድርድር ነጥቦችን ማቅረቧ ተነገረ

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን እና የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚካሄደውን ጦርነት ለማቆም ያስችላል በማለት ለመደራደሪያነት ላቀረቡት ባለ 15 ነጥብ ዕቅድ ከኢራን በኩል ምላሽ መሰጠቱን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    ለኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ቅርብ የሆነው ታስኒም የዜና ወኪል እንደዘገበው ኢራን ለትራምፕ የድርድር ቅድመ ሁኔታ የራሷን ሃሳብ አቅርባ ምላሽ እየጠበቀች ነው።

    የዜና ወኪሉ አንድ ጉዳዩን “የሚያውቁ ባለሥልጣንን” በመጥቀስ እንደዘገበው ኢራን ካቀረበቻቸው ነጥቦች መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል፦

    • በጠላት የሚፈጸሙ ጥቃቶች እና ግድያዎች መቆም አለባቸው
    • ጦርነት መልሶ እንደማይቀሰቀስ የሚያረጋግጥ ሁኔታ መፈጠር አለበት
    • ማካካሻ እና የጦርነት ካሳ በግልጽ ተወስኖ መሰጠት አለበት
    • በኢራን ብቻ ሳይሆን በአጋሮቿ ላይ የተከፈተው ጦርነት መቆም አለበት

    ኢራን ከራሷ በተጨማሪ በሌሎች ቦታዎች የሚካሄድ ጦርነት በማለት የጠቀሰችው እስራኤል ሊባኖስ ውስጥ የቴህራን ዋነኛ አጋር በሆነው ሄዝቦላህ ላይ የከፈተችውን መጠነ ሰፊ ጦርነት ነው።

    በተጨማሪም ኢራን በወሳኙ የሆርሙዝ ወሽመጥ መተላለፊያ ላይ “ተፈጥሯዊ እና ሕጋዊ መብቷን” በማክበር ያላት ሉዓላዊነቷን እንዲጠበቅ ትፈልጋለች።

    ከኢራን በኩል የቀረቡት ነጥቦች ከሞላ ጎደል በፕሬዝዳንት ትራምፕ ከቀረቡት የንግግር ዕቅዶች ጋር የሚቃረኑ ሲሆን፣ ከዚህም የተነሳ ለድርድር ያለው ዕድል ጠባብ ሊሆን ይችላል የሚል ስጋት አለ።

  19. ኢራን፤ አገራት አስቀድመው በማሳወቅ መርከቦቻቸውን በሆርሙዝ በኩል እንዲያሳልፉ ፈቀደች

    ካርታ

    የመርከቦችን እንቅስቃሴ ቀደም ብሎ ለኢራን በማሳወቅ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ማለፍ እንደሚችሉ በደቡብ ኮሪያ የኢራን አምባሳደር ተናገሩ።

    አምባሳደር ሳኢድ ኮዜቺ በደቡብ ኮሪያ ዋና ከተማ ሴዑል ውስጥ እንደተናገሩት “አስቀድሞ ከኢራን ጋር በሚደረግ ግንኙነት” የአገሪቱ መርከቦች በባሕር መተላለፊያው በኩል ያለ ችግር ማለፍ እንደሚችሉ አመልክተዋል።

    ለዚህም ሁኔታዎችን ለማመቻቸት ደቡብ ኮሪያ ስለመርከቦቿ እንቅስቃሴ ያላትን መረጃ ለኢራን ቀደም ብላ እንድታሳውቅ መጠየቋንም አምባደሳሩ ገልጸዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የማሌዢያው ጠቅላይ ሚኒስትር አንዋር ኢብራሂም ከኢራን ባለሥልጣናት ጋር ንግግር ከተደረገ በኋላ የአገራቸው መርከቦች በሆርሙዝ በኩል እንዲያልፉ እንደተፈቀደላቸው አሳውቀዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጨምረውም ለዚህም ሲባል ከኢራን፣ ከግብፅ፣ ከቱርክ እና ከሌሎች የቀጣናው አገራት ጋር ንግግር መደረጉን ጠቅሰዋል።

    ከፍተኛ መጠን ያለው የነዳጅ ምርት ከፋርስ ባሕረ ሰላጤው አገራት በሚተላለፍበት የሆርሙዝ ሰርጥ፤ እየተካሄደ ባለው ጦርነት ምክንያት የመዘጋት ስጋት ካጋጠመው በኋላ በሺዎች የሚቆጠሩ ግዙፍ መርከቦች ባሕር ላይ እየተጉላሉ ይገኛሉ።

    አሁን ከኢራን ጋር እየተደረጉ ባሉ ግንኙነቶች አማካኝነት በመተላለፊያው በኩል የማሌዢያ፣ የደቡብ ኮሪያ፣ የሕንድ፣ የቻይና እና የጃፓን የጭነት መርከቦች ያለ ችግር ማለፍ እንደቻሉ ተነግሯል።

    የኢራን ባለሥልጣናትም ጠላት ካሏቸው አገራት መርከቦች ውጪ የሌሎች አገራት መርከቦች ችግር እንደማይገጥማቸው እየተናገሩ ነው።

  20. ኔታንያሁ የኢራን ባሕር ኃይል አዛዥ መገደል ከአሜሪካ ጋር ያለን ትብብር ማሳያ ነው አሉ

    ኔታኒያሁ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ የኢራን አብዮታዊ ዘብ የባሕር ኃይል አዛዥ ግድያ በጦርነቱ ውስጥ በአገራቸው እና በአሜሪካ መካከል ያለው ቅንጅት ማሳያ መሆኑን ተናገሩ።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአዛዡ አሊሬዛ ታንግሲሪ መገደል አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የሚያካሂዱት ጦርነት ላይ ያላቸው “ትብብር ሌላ ማሳያ ምሳሌ ነው” ሲሉ ገልጸዋል።

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር በእብራይስጥ ቋንቋ በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት፤ አገራቸው ኢራን ውስጥ የሚገኙ ዒላማዎችን “በኃይል መምታቷን” ትቀጥላለች ብለዋል።

    ኔታኒያሁ በንግግራቸው ላይ የኢራን ባሕር ኃይል አዛዥን በተመለከተ የመከላከያ ሚኒስትራቸው ቀደም ሲል ያሉትን በመድገም አዛዡ በሆርሙዝ ወሽመጥ መዘጋት ላይ የመሪነት ሚና ነበራቸው በማለት ከስሰዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጨምረውም "ይህ ሰው የበርካቶች ደም በእጁ ላይ ነበረ” በማለት የተወሰደው እርምጃ “ዓላማችንን ከግቡ ለማድረስ እና ጦርነቱን ግቡ ለማሳካት ከወዳጃችን ከአሜሪካ ጋር ያለንን ትብብር የሚያሳይ ምሳሌ ነው” ሲሉ የአሜሪካንን ሚና ጠቅሰዋል።