ተጨማሪ ወታደሮቿ እና የጦር መርከቧ ወደ ባሕረ ሰላጤው የደረሱት አሜሪካ የእግረኛ ዘመቻ ለማካሄድ መዘጋጀቷ ተነገረ

ቅዳሜ ዕለት በሺዎች የሚቆጠሩ ተጨማሪ ወታደሮች እና አንድ የጦር መርከቧ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ የደረሱት የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስቴር ፔንታገን በኢራን ውስጥ ለሳምንታት የሚቆይ የእግረኛ ሠራዊት ዘመቻ ለማካሄድ እየተዘጋጀ መሆኑ ተገለጸ።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያልፉ መርከቦችን የምታስከፍልበት ሕግ ልታወጣ ነው

    በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚጓዝ ግዙፍ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚጓዝ ግዙፍ መርከብ

    የኢራን ፓርላማ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ከሚያልፉ መርከቦች ክፍያ ለመሰብሰብ የሚያስችል ረቂቅ ሕግ ሊወጣ መሆኑን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    የፓርላማው የኮንስትራክሽን ኮሚቴ ኃላፊ፤ “ረቂቅ ተዘጋጅቷ ነገር ግን ወደ ሙሉ አዋጅነት ደረጃ አልደረሰም” ብለዋል። ሕጉ የተዘጋጀው “ለሚያልፉ መርከቦች የደኅንነት ጥበቃ ለማቅረብ” እንደሆነም ተናግረዋል።

    አንድ የአገሪቱ ሕግ አውጪ ደግሞ “ፓርላማው ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ያላትን ሉዓላዊነት፣ ቁጥጥር እና የበላይነት በሕጋዊ መንገድ ለማረጋገጥ የተያዘውን እቅድ እየተከተለ ነው፤ በዚያውም ክፍያ በመሰብሰብ የገቢ ምንጭ ይፈጥራል” ማለታቸውን አሶሺዬትድ ፕሬስ የኢራን የዜና ወኪሎችን ዋቢ አድርጎ ዘግቧል።

    “ሸቀጦች በሌሎች ኮሪደሮች ሲያልፉ የትራንዚት ክፍያ እንደሚከፍሉ ሁሉ ይህ ሙሉ በሙሉ ተፈጥሯዊ ነው፤ የሆርሙዝ ወሽመጥም መተላለፊያ ነው” ብለዋል።

    “እኛ ጥበቃ እናቀርባለን፤ መርከቦች እና የነዳጅ ጫኞች ይህንን አይነት ክፍያ መክፈላቸውም ተፈጥሯዊ ነው” ሲሉ የረቂቁን መነሻ አስረድተዋል።

    በወሽመጡ ከሚያልፉ መርከቦች የሚሰበሰበው ክፍያ ምን ያህል እንደሚሆን እስካሁን አልታወቀም።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ትናንት ምሽት በቴሌቪዥን በተላለፈ ንግግራቸው፤ ቴህራን እስካሁን እንደ “ቻይና፣ ሩሲያ፣ ፓኪስታን፣ ኢራቅ እና ህንድ” ካሉ አገራት የቀረበላትን የመርከቦች ይለፉ ጥያቄ መቀበሏል ገልጸዋል።

    ከኢራን አንጻር ሲታይ የሆርሙዝ ወሽመጥ “ሙሉ ለሙሉ አልተዘጋም፤ ለጠላቶች ግን ዝግ ነው” ብለዋል።

  2. ፕሬዝዳንት ትራምፕ፤ የኢራን አመራሮች “ጊዜው ሳይረፍድ በፊት” ድርድሩን “በቁም ነገር እንዲይዙት” አሳሰቡ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የኢራን አመራሮች “አንዴ ከሆነ በኋላ ወደ ኋላ መመለስ ስለማይኖር፤ ጊዜው ሳይረፍድ በፊት” ድርድር እንዲያደርጉ አሳሰቡ።

    ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ይህንን ያሉት ከኢራን ጋር የሚደረገው ድርድር እየተቃረበ መሆኑን ከገለጹ ከአንድ ቀን በኋላ ነው።

    የኢራን አመራሮች ከአሜሪካ ጋር ለመስማማት “እየለመኑ ነው" በማለት የጻፉት ፕሬዝዳንቱ፤ የአገሪቱ ጦር “እንደተደመሰሰ” እንዲሁም “ወደ ኋላ የመመለስ ምንም እድል እንደሌለ” ተናግረዋል።

    የኢራን አመራሮች “አሁንም በአደባባይ የሚናገሩት 'የእኛን እቅድ እየተመለከቱት’ እንደሆነ ብቻ ነው። ስህተት!” ሲሉ በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ጽፈዋል። የኢራን የተደራዳሪዎችንም “እጅግ የተለዩ” እና “እንግዳ” ሲሉ ጠርተዋል።

    “ጊዜው እጅግ ሳይረፍድ በፊት በቶሎ ጉዳዩን በቁም ነገር ቢይዙት ይሻላል፤ ምክንያቱም አንዴ ከሆነ በኋላ ወደ ኋላ መመለስ የለም፤ ጥሩም አይሆንም!” ብለዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አግራቺ፤ ኢራን “ለአሁኑ ምንም የመደራደር ፍላጎት እንደሌላት” ረቡዕ ዕለት ተናግረው ነበር።

    “በወዳጅ አገራት በኩል” መልዕክት መድረሱን የገለጹት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፤ ነገር ግን ይህ የመልዕክት ልውውጥ “ንግግርም፣ ድርድር ወይም ለዚያ የቀረበ ነበር” እንዳልሆነ አስገንዝበዋል።

  3. እስራኤል የኢራን አብዮታዊ ዘብ የባሕር ኃይል አዛዥን መግደሏን አስታወቀች

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የባሕር ኃይል አዛዥ የነበሩት አሊሬዛ ታንጋሲሪን

    የፎቶው ባለመብት, Tasnim

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የባሕር ኃይል አዛዥ የነበሩት አሊሬዛ ታንጋሲሪን

    እስራኤል፤ ወሳኙን የሆርሙዝ ወሽመጥ መተላለፊያን የሚቆጣጠረው የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የባሕር ኃይል አዛዥ የሆኑትን አሊሬዛ ታንጋሲሪን መግደሏን አስታወቀች።

    የእስራኤል የመከላከያ ሚኒስትር ኢዝራኤል ካትዝ፤ አዛዡ "በሽብር የቦምብ ጥቃቶች እና የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥን በመዝጋት በቀጥታ ተጠያቂ” ናቸው በማለት ከስሰዋል።

    ሚኒስትሩ ጨምረውም ከዋና አዛዡ ባሻገር በርካታ ሌሎች የኢራን “ከፍተኛ የባሕር ኃይል ዕዝ ባለሥልጣናት” በእስራኤል ጥቃት መገደላቸውን አመልክተዋል።

    ግድያውን በተመለከተ እስራኤል እስካሁን ማረጋገጫም ሆነ ማስተባበያ አልሰጠችም።

    አሊሬዛ ታንግሲሪ የእስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የባህር ኃይል አዛዥ ሆነው የተሾሙት እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2018 ነበር።

    ከዚያ በፊት እአአ ከ2010 ጀምሮ የአብዮታዊ ዘብ የባህር ኃይል ምክትል አዛዥ በመሆን አገልግለዋል።

    እርሳቸው አንደሚገለገሉበት የሚገለጽ የኤክስ አካውንት እአአ ከመጋቢት 10 ጀምሮ የኢራን መገናኛ ብዙኃን በምንጭነት ይጠቀሙበት ነበር።

    በዚህ የኤክስ ገጽ ላይ ስለ ሆርሙዝ ወሽመጥ ብዙ ጊዜ አጋርተዋል።

    በዚህ ገጽ ላይ “ኢራን ላይ ጥቃት ከሚፈጽሙ ጋር ግንኙነት ያለው ማንኛውም መርከብ የማለፍ መብት የለውም” የሚል መልዕክት ሰፍሯል።

    ታንግሲሪ የሚሰማቸውን በመናገር የሚታወቁ ወታደራዊ አዛዥ ሲሆኑ ቀደም ሲል በአሜሪካ እና በእስራኤል ላይ ብዙ መግለጫዎችን ሰጥተዋል።

    እአአ በ2019 ኢራን ወደ ውጭ የምትልካቸው የነዳጅ ዘይት ምርቶች ከተስተጓጎሉ የሆርሙዝ ባህር ወሽመጥን እንደሚዘጉ ዝተው ነበር።

  4. በኢራን እና አሜሪካ መካከል የሚደረገው ውይይት እርግጠኛ ባልሆነበት ዕለት ጥቃቶች መፈጸማቸው ቀጥለዋል

    ረቡዕ ዕለት እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ ናባቴህ በፈጸመችው ጥቃት የመኖሪያ ሕንጻ ፈራርሷል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ረቡዕ ዕለት እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ ናባቴህ በፈጸመችው ጥቃት የመኖሪያ ሕንጻ ፈራርሷል

    ዶናልድ ትራምፕ በኢራን ላይ የከፈቱትን ጦርነት የሚያስቆም ንግግር መጀመሩን ቢናገሩም ኢራናውያን ግን ምንም ነገር የለም ሲሉ ማስተባበላቸውን ቀጥለዋል።

    የሚካሄዱ ንግግሮች ላይ እርግጠኛ ባልተሆነበት ዕለት በቀጣናው የሚፈጸሙ ጥቃቶች ቀጥለዋል።

    እስራኤል ሐሙስ ዕለት በኢስፋሃን እና በሌሎች “በርካታ” አካባቢዎች “መጠነ ሰፊ” ጥቃት መክፈቷን ተናግራለች።

    የዩናይትድ ስቴትስ ማዕከላዊ ዕዝ ሌሊቲን ከዩኤስኤስ አብርሃም ሊንከን አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ ላይ በመነሳት በኢራን በሚገኙ ዒላማዎች ላይ ጥቃቶች መፈጸሙን ገልጿል።

    በሊባኖስ የአገሪቱ ብሔራዊ ዜና ወኪል፣ ኤንኤንኤ ረቡዕ ምሽት እስራኤል በምዕራባዊ ሊባኖስ ሃሮፍ በፈጸመችው ጥቃት ሁለት ሰዎች መሞታቸውን እና ስምንት መቁሰላቸውን አስታውቋል።

    ሐሙስ ማለዳ እንዲሁ በአራብሳሊም ከተማ አቅራቢያ በተፈጸመ ጥቃት ተጨማሪ ስምንት ሰዎች መጎዳታቸውን የአገሪቱን ጤና ሚኒስቴር ጠቅሶ ዘግቧል።

    ኢራን በተባበሩት አረብ ኤሜሬትስ፣ አቡዳቢ ላይ በፈጸመችው የሚሳዔል ጥቃት ሁለት ሰዎች መገደላቸው ተገልጿል።

    በተጨማሪም ሳዑዲ አረቢያ እና ኩዌት ከኢራን የሚተኮሱ ድሮኖችን ማክሸፋቸውን ተናግረዋል።

    እስራኤል በበኩሏ በካፍር ቃሲም ከተማ በተፈጸመ ጥቃት ስድስት ሰዎች ተጎድተው ሆስፒታል መግባታቸውን ይፋ አድርጋለች።

    ባህሬን ሐሙስ ማለዳ የተተኮሰ ሚሳዔልን ተከትሎ ነዋሪዎች ደኅንነቱ ወደ ተጠበቀ መጠለያ እንዲገቡ ማስጠንቀቂያ አስተላልፋለች።

  5. እስራኤል የኢራን አፈ ጉባኤ እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ልትገድላቸው ከምትፈልጋቸው ባለሥልጣናት ዝርዝር እንዲወጡ አደረገች

    አፈ ጉባኤ ሞሐመድ ባገር ጋሊባፍ እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ
    የምስሉ መግለጫ, አፈ ጉባኤ ሞሐመድ ባገር ጋሊባፍ እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    እስራኤል የኢራን የፓርላማ አፈ ጉባኤን እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩን ልትገድላቸው ከምትፈልጋቸው የኢራን ባለሥልጣናት ዝርዝር ውስጥ ማስወጣቷን አንድ የፓኪስታን ባለሥልጣን ተናገሩ።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺን እና የአፈ ጉባኤ ሞሐመድ ባገር ጋሊባፍ ስም እስራኤል ከጥቃት ዒላማዋ ዝርዝር እንድታስወጣ ፓኪስታን በአሜሪካ በኩል ጥያቄ በማቅረቧ ተቀባይነት ማግኘቱን ባለሥልጣኑ ለሮይተርስ ዜና ወኪል ገልጸዋል።

    "አስራኤል ሁለቱ ባለሥልጣናት የሚገኙባቸውን ስፍራዎች መረጃ ነበራት...እነሱም ሊገድሏቸው ይፈልጋሉ። ነገር ግን እኛ ለአሜሪካኖች እነዚህ ሰዎች ከተገደሉ ለድርድር የሚቀመጥ ሌላ ሰው እንደማይኖር ስለነገርናቸው እስራኤላውያኑ ዕቅዳቸውን እንዲተዉ አድርገዋል” ሲሉ ባለሥልጣኑ ተናግረዋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት ከከፈቱበት ዕለት አንስቶ በርካታ የኢራን ከፍተኛ ፖለቲካዊ እና ወታደራዊ መሪዎች በእስራኤል ጥቃት የተገደሉ ሲሆን፣ እስራኤል ባለሥልጣናቱን ማደኗን እንደምትቀጥል በተደጋጋሚ ገልጻለች።

    አንድ ወር ሊሞላው የተቃረበውን ጦርነት ለማስቆም በኢራን እና በአሜሪካ መካከል ሊካሄድ የታሰበውን ድርድር ፓኪስታን ታስተናግዳለች ተብሎ ይጠበቃል።

    በዚህ ድርድር ላይ ኢራንን በመወከል በእስራኤል ዒላማ መደረጋቸው እየተነገረ ያሉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ እንዲሁም በአሜሪካ በኩል ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ በዋናነት ይገኛሉ ተብሎ እየተጠበቀ ነው።

  6. ኢራን ከአሜሪካ ጋር ቀጥተኛ ንግግር መደረጉን ካስተባበለች በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አገራቸው ከአሜሪካ ጋር አሁን የመደራደር ፍላጎት እንደሌላት ከተናገሩ በኋላ ዓለም አቀፉ የነዳጅ ገበያ በእስያ ጭማሪ አሳይቷል።

    ረቡዕ ዕለት የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ለአገር ውስጥ ሚዲያዎች እንደገለጹት፣ “ንግግሩ እየተደረገ ያለው በወዳጅ አገራት በኩል ነው። ይህ ደግሞ እንደ ድርድር አይወሰድም” ብለዋል።

    ኢራን ንግግር አለመኖሩን መናገሯን ተከትሎ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “ኢራን ድርድር መጀመሩን መግለጽ ያስፈራታል” ብለዋል።

    ውዝግቡ እየቀጠለ ባለበት ሁኔታ የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ መጨመሩ ተስተውሏል። በተለያዩ የገበያ ቦታዎች ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት በበርሜል ከ1.4 እስከ 1.6 በመቶ ታይቶበታል።

    የነዳጅ ዋጋ መጨመር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

  7. ዋይት ሐውስ ከኢራን ጋር እየተደረገ ነው ስላለው ድርድር ምን አለ?

    የዋይት ሐውስ ፕሬስ ኃላፊ ካሮላይን ሌቪት

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ረቡዕ ምሽት በነበረ ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት የዋይት ሐውስ ፕሬስ ኃላፊ ካሮላይን ሌቪት በኢራን ጉዳይ ላይ ሰፋ ያለ ማብራሪያ ሰጥተዋል።

    • ኃላፊዋ ፕሬዚዳንት ትራምፕ “ውጤታማ ውይይት” ከኢራን ጋር ማድረጋቸውን ቢገልጹም ቴህራን ግን ይህንን አስተባብላለች።
    • ሌቪት በማኅበራዊ ሚዲያ እየተዘዋወረ ያለው ባለ 15 ነጥብ ዕቅድ “ግምት ናቸው” ካሉ በኋላ ነገር ግን “እውነታውን የሚያሳዩ ነጥቦች ይዘዋል” ብለዋል። በሁለቱ አገራት መካከል ተደረገ የተባለው ንግግር በምን መልክ እንደተጠናቀቀ በሚመለከት “ዝርዝር ጉዳዮች ላይ" ለመግባት ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል።
    • የፕሬስ ኃላፊዋ ትራምፕ በኢራን የሥርዓት ለውጥ ተሳክቷል ሲሉ የተናገሩትን ሀሳብ በመደገፍ ተናግረዋል። ሌቪት ለጋዜጠኞች የኢራን አመራሮች መገደላቸው በመግለጽ ሞጅታባ ኻሜኒን “ማንም አላያቸውም ወይም በእርግጠኝነት አልሰማቸውም” ብለዋል።
    • ሌቪት አሜሪካ በመካከለኛው ምሥራቅ እግረኛ ጦሯን ታሰማራ እንደሆን ተጠይቀው ለመመለስ ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል። ነገር ግን ጦሩን ለማሰማራት የኮንግረስ ይሁንታን ማግኘት አስፈላጊ ላይሆን ይችላል ብለዋል።
    • ጦርነቱ የሚያበቃበት ትክክለኛ ጊዜ ይታወቅ እንደሆን ተጠየቀው፣ ሌቪት አሜሪካ አንኳር ዓላማዎቿን ለማሳካት “በጣም ተቃርባለች” በማለት ቁርጥ ያለ ቀን ከመናገር ግን ተቆጥበዋል።
  8. ኢራን ከአሜሪካ ጋር የሚደረግን ውይይት ውድቅ ማድረጓ ጥልቅ አለመተማመን እንዳለ ያሳያል

    የኢራንን ባንዲራያዙ ሰልፈኞች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዋሺንግተን ንግግር እየተደረገ መሆኑን ስትገልጽ ቴህራን በበኩሏ ወዲያውኑ ውድቅ አድርጋለቸ። ይህ አለመግባባት የሚያሳየው ሁለቱ አገራት ከዚህ በፊት ባደረጓቸው ድርድሮች ወቅት የተፈጠረን ጥልቅ አለመተማማን ነው።

    ከዚህ ቀደም በሁለቱ አገራት መካከል ሁለት ጊዜ ውጥረትን ያረግባሉ የተባሉ ንግግሮች ተጀምረው ነበር።

    ነገር ግን ሁለቱም ንግግሮቹ በሂደት ላይ እያሉ አሜሪካ እና እስራኤል በቴህራን ላይ ወታደራዊ ጥቃት ከፍተውባታል።

    ከኢራን አንጻረ ንግግር መጀመር ጦርነት ይከፈታል የሚለውን ዕድል አይቀንሰውም።

    እንዲያውም ጦርነቶቹ የተጀመሩት ንግግሮቹ እየተካሄዱ ባለበት ወቅት ነው። ለዚህም ነው የትራምፕ ንግግር በጥርጣሬ የታየው።

    ነገር ግን የኢራን ማስታባበያም ቢሆን እውነታውን አያሳይም። ከመጋረጃ ጀርባ በርካታ ነገሮች የተከናወኑ ነው።

    ዲፕሎማሲን የሚደግፉ ባለሥልጣናት ሳይቀር ጫና ውስጥ ናቸው። በድጋሚ ድርድር መጀመር አደገኛ ሊሆን ይችላል።

    አሁን የሚደረግ ድርደር ከዚህ ቀደም ከተካሄዱት የተለየ የሚሆንበትን መንገድ የሚጠቁም ምንም ነገር የለም። ለዚህም ነው የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባሰ አራጋቺን ጨምሮ ሊሎች የአገሪቱ ባለሥልጣናት ጠንካራ ድምጸት ባለው ቃል ንግግርን ውድቅ የሚያደርጉት።

  9. ኢራን እና አሜሪካ ድርድርን በሚመለከት ምን እያሉ ነው?

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በመካከለኛው ምሥራቅ የሚካሄደውን ጦርነት ያስቆማል ተብሎ ተስፋ የተጣለበት የአሜሪካ እና ኢራን ንግግርን በተመለከተ የሚወጡ መረጃዎች አሁንም እርስ በእርሳቸው የሚጣረሱ ናቸው።

    • የዋይት ሐውስ የፕሬስ ኃላፊ ካሮላይን ሌቪት ሐሙስ ዕለት ፕሬዚዳንት ትራምፕ ባለፉት ሦስት ቀናት ከኢራን ጋር “ውጤታማ ንግግር” ማድረጋቸውን ገልጻለች።
    • ኃላፊዋ አክላም ዘመቻው “ከተያዘለት ጊዜ ቀድሞ እየተካሄደ መሆኑን" እና የኢራን አስተዳደር “መውጫ መንገድ” እየፈለገ መሆኑን ተናግራለች።
    • የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ በበኩላቸው ከዋሺንግተን ፍጹም ተቃራኒ የሆነ አስተየየት ሰጥተዋል። እንደ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከሆነ ኢራን "ለአሁኑ ምንም የመደራደር ፍላጎት የላትም”።
    • ሚኒስትሩ አክለውም ይህ መልዕክት “በወዳጅ አገራት በኩል ተላልፏል” ያሉ ሲሆን እነዚህ ልውውጦች ግን “ውይይትም አይደሉም እንደ ድርድርም አይወሰዱም፤ ምንም አድርገን ልንወስዳቸው አንችልም” ብለዋል።
    • ትራምፕ ግን አሁንም ኢራን “እየተደራደረች ነው” በሚለው አቋማቸው እንደጸኑ ናቸው። አክለውም “በራሳቸው ሕዝብ እንገደላለን ብለው ስለፈሩ ለማመን ፈርተው ነው እንጂ” እየተደራደሩ ነው ሲሉ ተደምጠዋል። አክለውም “እኛም አንዳንገላቸው ይፈራሉ” ብለዋል።
    • ሌላው አሜሪካ ጦርነቱ እንዲያበቃ በሚል ያቀረበችው ባለ 15 ነጥብ ምክረ ሃሰብ ራሱን የቻለ አወዛጋቢ ሆኗል። ረቡዕ ዕለት ኢራን 15 ነጥቦችን የያዘ ምክረ ሃሳብ ከአሜሪካ እንደደረሳት ተገልጾ ነበር።
    • የኢራኑ ፕሬስ ቲቪ የአገሪቱን “ከፍተኛ የፖለቲካ እና ጸጥታ ባለሥልጣን” ጠቅሶ ጦርነቱን ለማስቆም አገሪቱ የራሷ ቅድመ ሁኔታ እንዳላት ዘግቧል። ዕህም “ጦርነቱ ላደረሰው ውድመት እና የገንዘብ ካሳ” ክፍያ የሚጨምር ባለ አምስት ነተዕብ ቅድመ ሁኔታ ነው። ከዚህም በተጨማሪ ጦርነቱን በሁሉም ግንባሮች ማቆምም ተካትቶበታል።
    • ይህ በእንዲህ አንዳለ በመካከለኛው ምሥራቅ የሚካሄደው ጦርነት ዐዕንደቀጠለ ሲሆን ኢራን አደረሰችው የተባለ የሚሳዔል ጥቃትን ተከትሎ ከእስራኤለ የኃይል ማመንጫ ጣቢያ ጭስ ሲወጣ ታይቷል። እስራኤል በበኩሏ በቴህራን የምታደርገውን ድብደባ ቀጥላበታለች።
  10. አሜሪካ በኢራን የምታካሄደውን ጦርነት "እያጠናቀቀች" መሆኑን አፈ ጉባዔዋ ተናገሩ

    የአሜሪካ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ማይክ ጆንሰን

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ማይክ ጆንሰን

    የአሜሪካ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ማይክ ጆንሰን አገራቸው ከኢራን ጋር የምታካሄደውን ጦርነት “እያጠናቀቀች” ነው አሉ።

    ጆንሰን በዋሽንግተን ዲሲ ለአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን "ኦፕሬሽን ኤፒክ ፊዩሪን እያጠቃለልን ያለን ይመስለኛል። እኔ የማስበው ይህንኑ ነው። እኔ እንደማስበው በአጭር ትዕዛዝ ይከናወናል እና ይህ በታቀደለት ጊዜ የሚከናወን ይሆናል" ብለዋል።

    አፈ ጉባዔው ይህንን ያሉት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደራቸው “ስምምነት ላይ መድረስ ትፈልጋለች” ካሏት ኢራን ባለሥልጣናት መካከል “ከሚመለከተው ሰው” ጋር እየተነጋገረ መሆኑን ከተናገሩ በኋላ ነው።

    ኢራን አሜሪካ ያቀረበችውን የሰላም ዕቅድ “ከልክ ያለፉ ናቸው” በማለት ውድቅ አድርጋለች።

  11. አሜሪካ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አየር ወለዶቿን መላኳን አረጋገጠች

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር ፔንታገን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ የእግረኛ እና የአየር ወለድ አባላት የተካተቱበት ጦር መላኩን ለቢቢሲ አረጋገጠ።

    የፔንታገን ቃል አቀባይ ለቢቢሲ እንዳረጋገጡት የተወሰኑ የ82ኛው አየር ወለድ ዋና ዕዝ፣ የተወሰኑ “ልዩ ኃይሎች” እና የአንደኛ ብርጌድ አባላት በመካለኛው ምሥራቅ ይሰማራሉ።

    ቃል አቀባዩ ለደኅንነት በሚል ዝርዝር መረጃ ከመስጠት ተቆጥበዋል።

    ወደ መካከለኛው ምሥራቅ እያመሩ ያሉት ኃይሎች የተወጣጡባቸው ክፍሎች በጦርነቱ ውስጥ ምን ዓይነት ተሳትፎ ሊኖራቸው እንደሚችል ያሳያል።

    በኖርዝ ካሮላይና መቀመጫውን ያደረገው 82ኛው አየር ወለድ በመደበኛ ውጊያ ውስጥ ዋነኛው ጥቃት ፈጻሚ ቡድን እንደሆነ ይታመናል። የተወሰኑ የቡድኑ አባላት በ18 ሰዓት ውስጥ በየትኛውም ዓለም ክፍል ለመሰማራት ሁሌም በተጠንቀቅ ላይ ናቸው።

    እነዚህ ወታደሮች ዒላማ ወደሚደረጉ አካባቢዎች በፓራሹት በመውረድ ወይንም በሂሊኮፕተር በመሄድ ተልዕኳቸውን ይፈጽማሉ።

    ይህም በኢራን የኻርግ ደሴትን ወይንም ሌላ ቁልፍ ግዛትን በቁጥጥር ስር ለማዋል ያስችላል።

    ነገር ግን ጦሩ በእንቅስቃሴ ውስጥ የሚፈጸም ጥቃት ላይ ስለሚያተኩር ቀጣይነት ላለው ውጊያ የሚያገለግል ከባድ ጦር መሣሪያ አይታጠቅም።

    መቀመጫውን ኒው ዮርክ ያደረገው አንደኛ ብርጌድ የጥቃት ቡድን ደግሞ በተራራማ አካባቢዎች በሚደረግ ጦርነት የተካነው 10ኛው ዲቪዥን አባል ሲሆን፣ ለተራዘመ ጦርነት የሚያገለግሉ ከባድ መሣሪያዎችን ይታጠቃል።

  12. ኢራን በትራምፕ የቀረቡትን የድርድር ሀሳቦች ውድቅ በማድረግ የራሷን ቅድመ ሁኔታ አቀረበች

    ሰንደቅ ዓላማዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን መንግሥት በፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በኩል የቀረበውን የድርድር ዕቅድን ውድቅ ማድረጉን የአገሪቱ የመገናኛ ብዙኃን አመለከቱ።

    የኢራን መንግሥት የቴሌቪዥን ጣቢያ የሆነው ፕሬስ ቲቪ የአገሪቱን “ከፍተኛ የፖለቲካ እና የደኅንነት ባለሥልጣናትን” ጠቅሶ እንደዘገበው፤ እየተካሄደ ያለውን ጦርነት ለማስቆም በማለም በአሜሪካ በኩል የቀረበውን ሃሳብ ኢራን ውድቅ አድርጋዋለች።

    የቴሌቪዥን ጣቢያው የባለሥልጣኑን ስም እና የሥራ ኃላፊነት ሳይጠቅስ እንደዘገበው “ኢራን ጦርነቱን የምታበቃው ራሷ ስትወስን እና የራሷ ቅድመ ሁኔታዎች ሲሟሉ ነው” ሲሉ ባለሥልጣኑ መናገራቸውን አመልክቷል።

    የኢራን ባለሥልጣናት እስካሁን ድርድር አለመጀመሩን እንዲሁም ጦርነቱ የሚቆም ከሆነ የተኩስ አቁም ሳይሆን ሙሉ ለሙሉ መሆን እንዳላበት በተደጋጋሚ ሲናገሩ ቆይተዋል።

    የኢራን መንግሥት ቴሌቪዥን ፕሬስ ቲቪ እንዳመለከተው፣ ባለሥልጣኑ ኢራን መሟላት አለበት ያለቻቸውን የሚከተሉትን ቅድመ ሁኔታዎች ገልጸዋል።

    • በጠላት የሚፈጸመው “ወረራ እና ግድያ” ሙሉ ለሙሉ መቆም
    • ጦርነቱ በድጋሚ በኢራን ላይ እንደማይከፈት የሚያረጋግጥ አስተማማኝ ሁኔታ መፍጠር
    • የተረጋገጠ እና በግልጽ የሚታወቅ በጦርነቱ ለደረሰው ጉዳት እና ካሳ መክፈል
    • በቀጣናው ባሉ ቡድኖች ላይ የተከፈቱት ሁሉም ጦርነቶች እንዲቆሙ ማድረግ
    • ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ያላትን መብት እና ሉዓላዊነት ዓለም አቀፍ ዕውቅና መስጠት የሚሉ ናቸው።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኢራን በኩል ከቀረቡት ቅድመ ሁኔታዎች በአብዛኛው ተቃራኒ የሆኑ ባለ 15 ነጥብ የድርድር ዕቅድ ማቅረባቸው የተነገረ ሲሆን፣ የኢራን ባለሥልጣናት ግን ነጥቦቹ “ከልክ ያለፉ ናቸው” በማለት መቃወማቸውን ፕሬስ ቲቪ ዘግቧል።

  13. በመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት እስካሁን ምን ያህል ሰዎች ተገደሉ?

    ኢራን ወደ እስራኤል ባስወነጨፈችወ ሚሳዔል በቴል አቪቭ የደረሰ ጉዳት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ኢራን ማክሰኞ ዕለት ወደ እስራኤል ባስወነጨፈችው ሚሳዔል በቴል አቪቭ የደረሰ ጉዳት

    በመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት የሞቱ ሰዎች ምን ያህል እንደሆኑ ከገለልተኛ ወገን ማጣራት ባይቻልም በአጠቃላይ የሟቾች ቁጥር ግን ከ4500 ማለፉ ተገልጿል።

    ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎች የተገደሉት በኢራን ሲሆን መቀመጫውን አሜሪካ ያደረገው የሰብዓዊ መብቶች ቡድን እስካሁን ድረስ 3,291 ሰዎች መሞታቸውን እና ከእነዚህም መካከል 1,455 ሰላማዊ ዜጎች መሆናቸውን አስታውቋል።

    እስራኤል በሄዝቦላህ መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት እየፈጸመች ባለበት ሊባኖስ ደግሞ 1072 ሰዎች መገደላቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።

    ኢራቅ ባለሥልጣናት ደግሞ 81 ሰዎች መገደላቸውን እና አብዛኞቹ ከኢራን ጋር ግንኙነት ያለው የሃሼድ አል ሻቢ አባላት መሆናቸወን አስታውቀዋል።

    እስራኤል በሚሳዔል ጥቃት ምክንያት 18 ሰዎች መሞታቸው ተዘግቧል። የእስራኤል መከላከያ ሚኒስቴር ሁለት ወታደሮች በደቡባዊ ሊባኖስ መገደላቸውን ይፋ አድርጓል።

    አሜሪካ 13 ወታደሮቿ መሞታቸውን ስታስታውቅ ስድስቱ የሞቱት ነዳጅ የሚመላ አውሮፕላን በኢራቅ በመከስከሱ መሆኑ ተጠቅሷል።

    ኳታር ደግሞ “በመደበኛ ስምሪት ላይ የነበረ” ሂሊኮፕተር ተከስክሶ ሰባት ሰዎች መሞታቸውን የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስቴር አስታውቋል።

    የተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ መከላከያ ሚኒስቴር ዘጠኝ ሰዎች መሞታቸውን ሲገልጽ ሦስቱ የጦሩ አባላት ስድስቱ ደግሞ ሰላማዊ ዜጎች መሆናቸውን አስታውቋል።

    በኩዌት ሁለት የአገር ውስጥ ሚኒስቴትር ባልደረቦች እና ሁለት ወታደሮችን ጨምሮ ስድስት ሰዎች መሞታቸው ታውቋል።

    ሶሪያ በተፈጸመ ጥቃት አራት ሰዎች ሲሞቱ፣ በዌስት ባንክ አራት፣ በባሕሬን ሁለት፣ በኦማን ሁለት እንዲሁም በሳዑዲ አረቢያ ሁለት ተገድለዋል።

  14. ፔንታጎን የጦር መሣሪያ ምርትን እና አቅርቦትን ለመጨመር መወሰኑን ገለጸ

    የመከላከያ ሚኒስትሩ ፒት ሄግሴት

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ፔንታጎን በርካታ የመከላከያ ሥርዓቶችን እና የጦር መሳሪያዎችን ምርት እንደሚያሳድግ አስታወቀ።

    መምሪያው በድረ ገጹ ላይ ባወጣው መግለጫ "ዒላማቸውን ለይተው የሚመቱ ሚሳዔሎችን" እንዲሁም ከፍ ብለው የሚምዘገዘጉ ሚሳዔሎችን ለማክሸፍ የሚያገለግለው መሣሪያ ምርትን ለማፍጠን መወሰኑን አስታውቋል።

    የመከላከያ ሚኒስትሩ ፒት ሄግሴት "የመከላከያው የኢንዱስትሪ ማዕከል የጦር መሣሪያዎችን በፍጥነት እንዲያመርት” ይፈልጋሉ ሲል መምሪያው አስታውቋል።

    ፔንታጎን ረቡዕ ዕለት የጦር መሣሪያ ምርቶችን እና ሥርዓቶችን ምርት ለመጨመር ከሦስት የጦር መሣሪያ አምራች ኩባንያዎች ጋር ስምምነት ተፈራርሟል።

    ይህም የአሜሪካ ጦር መሣሪያ ክምችትን ለማሳደግ እንደሚያግዝ ፔንታጎን አስታውቋል።

    ፔንታጎን ይህንን ውሳኔውን ይፋ ያደረገው ፕሬዚዳንት ትራምፕ ከእስራኤል ገር በመሆን ኢራን ላይ ጦርነት ከከፈቱ ሦስት ሳምንት በኋላ ነው።

  15. ኢራን የአሜሪካ ወታደሮችን እንቅስቃሴ “በቅርበት እየተከታተለች” መሆኑን የፓርላማው አፈ ጉባዔ ተናገሩ

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ መሐመድ ባገር ጋሊባፍ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ መሐመድ ባገር ጋሊባፍ

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ መሐመድ ባገር ጋሊባፍ ቴህራን "በአካባቢው ያለውን የአሜሪካ እንቅስቃሴ በተለይም የጦር ሠራዊቱን በቅርበት እየተከታተለች ነው" አሉ።

    “አገራችንን ለመከላከል ያለንን ቁርጠኝነት አትፈትኑ” ሲሉ በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ኒውስ እንደዘገበው ፔንታገን ከ82ኛው የአየር ወለድ ክፍል፣ የምድር ጦሩን እና ዕዙን ጨምሮ ወታደሮችን ወደ ስፍራው እንደሚልክ ይጠበቃል።

    ያልተረጋገጡ ሪፖርቶች የትራምፕ አስተዳደር ጋሊባፍን እንደ ሁነኛ አጋር እና ምናልባትም የወደፊት የአገሪቱ መሪ አድርጎ ይመለከታቸዋል ብለዋል።

  16. የእስራኤሉ ሚኒስትር አሜሪካ ባቀረበችው ዕቅድ ኢራን ላትስማማ ትችላለች አሉ

    የእስራኤል ኢኮኖሚ ሚኒስትር ኒር ባራካት
    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል ኢኮኖሚ ሚኒስትር ኒር ባራካት

    የእስራኤል ኢኮኖሚ ሚኒስትር ኒር ባራካት ቴህራን የአሜሪካ አስተዳደር ባዘጋጀው ባለ 15 ነጥብ ዕቅድ “ምናልባት“ ላትስማማ ትችላለች ሲሉ ተናገሩ።

    ሚኒስትሩ ዕቅዱን “በወረቀት ላይ ውብ ነው” ያሉ ሲሆን፣ ተግባራዊ የሚሆን ከሆነ ግን ዋስትና ያስፈልጋል ብለዋል።

    አክለውም የኢራን አስተዳደር “አይለወጥም” በማለት እስራኤል በጦርነቱ ላይ ያላት ዋና ዓላማዎች ኢራን “ያለ ምንም ኒውክሌር፣ ያለ ምንም ሚሳዔል እና ያለ ምንም ወኪሎች” እንድትቀር ማድረግ ነው ብለዋል።

    “እነሱ ነጭ ባንዲራ ካውለበለቡ ወይም ስምምነቱን ከፈረሙ እና ለዚያ ተገዢ ሆነው ነገ ወደ ግባችን ከደረስን፤ ወይም የኢራን መንግሥት ላይ ተጨማሪ ድብደባዎችን ማድረግ ካስፈለገን. . . እኔ እንደማምነው ፕሬዝዳንት ትራምፕ ያቀዱትን ጨምሮ… በእነዚህ ግቦች ላይ ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታንያሁ ወጥ አቋም አንዳላቸው አምናለሁ፤ እና እነሱን በአንድ ወይም በሌላ መንገድ እናሳካቸዋለን” ብለዋል ።

    “በአንድ በኩል ምናልባት ትራምፕ ንግግሮችን እያስጀመሩ ይሆናል፤ ነገር ግን ወደ ቀጣናው ወታደሮችን እያመጡም ነው፤ እናም ለኢራን ሕዝብ ይህንን ስንል ከልባችን ነው እያሏቸው ነው” ሲሉ ተናግረዋል።

    “ከዚህ ዙር በኋላ ስምምነት ተደረሰም አልተደረሰም ግቦቻችንን እናሳካለን” ሲሉም ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በ15 ነጥቦች ዕቅድ ዙሪያ በጋራ እየሠሩ መሆኑን ሲጠየቁ “ለጊዜው ክፍት አድርገን እንተወው” በማለት ምላሽ ሰጥተዋል።

    እስራኤል አሜሪካ ያቀረበችውን ምክረ ሃሳቦች በማርቀቅ ላይ ተሳትፋ አንደሆነ ሲጠየቁ ምንም ምላሽ ሳይሰጡ ቀርተዋል።

  17. በኢራን እና በአሜሪካ መካከል “የተካሄደ ድርድር የለም” የኢራን አምባሳደር

    የኢራን ዋና ከተማ ቴህራን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ዋና ከተማ ቴህራን

    በፓኪስታን የኢራን አምባሳደር ሬዛ አሚሪ ሞግሃዳም በአገራቸው እና በአሜሪካ መካከል ምንም ዓይነት ድርድር እንዳልተደረገ ለኢራን መንግሥት የዜና ወኪል ተናገሩ።

    አምባሳደሩ ኢራን ከአሜሪካ ጋር “ምንም ዓይነት ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ድርድር” እንዳልተካሄደ ኢርና ለተባለው የአገሪቱ ዜና ድርጅት አረጋግጠዋል።

    ነገር ግን አምባሳደር ሬዛ አሚሪ ሞግሃዳም “ወዳጅ አገራት በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ለሚደረግ ንግግር ሁኔታዎችን ለማመቻችት እንደሚፈልጉ እና ይህም የተከፈተብንን ጦርነት ለማስቆም እንደሚያስችል ተስፋ እናደርጋለን” ብለዋል።

    ቀደም ብሎ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደራቸው በኢራን ውስጥ ከሚገኙ “የሚመለከታቸው ሰዎች ጋር እየተነጋገረ” መሆኑን በመጥቀስ “ከስምምነት ላይ ለመድረስ አጥብቀው ይፈልጋሉ” በማለት ኢራናውያን ንግግሩን እንደሚፈልጉት ተናግረዋል።

    ነገር ግን የኢራን ጦር ሠራዊት ቃል አቀባይ ደግሞ አሜሪካ “ከራሷ ጋር እየተደራደረች ነው” በማለት ኢራን ድርድር ውስጥ እንደሌለች አመለክተዋል። የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይም እንዲሁ እየተካሄደ ያለ ድርድር እንደሌለ አሳውቀዋል።

    የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሻሪፍ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ባሠራጩት መልዕክት አገራቸው ለጦርነቱ መፍትሄ ለማምጣት የሚደረግን ንግግር ለማስተናገድ ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል።

  18. ‘ኢራን በአሜሪካ ዲፕሎማሲ ላይ እምነት የላትም’

    ኢስማኤል ባጋይ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ኢስማኤል ባጋይ

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለኢራን ባለሥልጣናት የድርድር ዕቅዳቸውን መላካቸውን እየገለጹ ባለበት ጊዜ ኢራን በአሜሪካ ላይ እምነት እንደሌላት ገለጸች።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ ለሕንዱ ጋዜጣ ‘ኢንዲያ ቱዴይ’ በሰጡት ቃለ ምልልስ “ማንም በአሜሪካ ዲፕሎማሲ ላይ ዕምነት ሊጥል አይችልም” በማለት ያላቸውን ጥርጣሬ ገልጸዋል።

    ጨምረውም “የአሜሪካንን ዲፕሎማሲ በተመለከተ ኢራን በጣም መጥፎ ልምድ አላት” በማለት በዘጠኝ ወራት ውስጥ ድርድሮች እየተካሄዱ ሁለት ጊዜ ጥቃት እንደተፈጸመባት በማብራራት ድርጊቱን “የዲፕሎማሲ ክህደት” ብለውታል።

    ቃል አቀባዩ እንዲሁም “በአሜሪካ እና በኢራን መካከል እየተካሄደ ያለ ድርድር እንደሌለ” አጽንኦት በመስጠት አስተባብለው፤ በአሁኑ ጊዜ የኢራን ጦር ኃይሎች ትኩረታቸውን ያደረጉት “የአገሪቱን ግዛት በመከላከል” ላይ መሆኑን ተናግረዋል።

    አንድ ወር ሊሞላው የተቃረበውን አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የሚያካሂዱት ጦርነትን ለማብቃት ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአምስት ቀናት የጊዜ ገደብ አስቀምጠው የድርድር ነጥቦችን ማቅረባቸውን ገልጸዋል።

    አስካሁን ግን ከኢራን በኩል ስለድርድሩ በይፋ የተባለ ነገር ካለመኖሩ በተጨማሪ የተለያዩ የአገሪቱ ባለሥልጣናት የተጀመረ ንግግር እንደሌለ እየተናገሩ ነው።

  19. የሻኪራ የዶሃ እና የአቡ ዳቢ ኮንሰርቶች በጦርነቱ ምክንያት ወደ ሌላ ጊዜ ተላለፉ

    ሻኪራ በመድረክ ላይ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ታዋቂዋ የላቲን ሙዚቃ ኮከብ ሻኪራ በባሕረ ሰላጤዋ የደሴት አገር ኳታር ዋና ከተማ ዶሃ በሚቀጥለው ሳምንት ልታቀርብ የነበረው ኮንሰርት ወደ ሌላ ጊዜ ተላለፈ።

    ቀደም ተብሎ ተይዞ የነበረው ይህ መረሃ ግብር ለመሰረዙ ምክንያት “በቀጣናው ያለው ወቅታዊ ሁኔታ” መሆኑን የኳታር የቱሪዝም ድረ ገጽ በማኅበራዊ ሚዲያው ላይ አስታውቋል።

    በተጨማሪም “አፍሊኒትዝ” የተባለው በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ አቡ ዳቢ ውስጥ ይካሄዳል የተባለው የሙዚቃ ፌስቲቫልም እንዲሁ አስከ ኅዳር ድረስ እንዲዘገይ ተደርጓል።

    ሻኪራ እና ጆናስ ብራዘርስ የተባሉት ሙዚቀኞች ያቀርቡት የነበረው ይህ ዝግጅት በሚቀጥለው ሳምንት ያስ በተባለችው የአቡ ዳቢ ደሴት ውስጥ የሚካሄድ ነበር።

  20. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለኢራን ያቀረቡት ባለ 15 ነጥብ ዕቅድ ምን ይዟል?

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ትራምፕ

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ 15 ነጥቦችን የያዘ ዕቅድ ለኢራን መላካቸው ተዘግቧል። ምንም እንኳን የስምምነት ነጥቦቹ ይፋ ባይወጡም የአሜሪካ እና የእስራኤል መገናኛ ብዙኃን የዕቅዱን ይዘት እየዘገቡ ነው።

    ቻናል 12 የተባለው የእስራኤል የቴሌቪዥን ጣቢያ በትራምፕ ዕቅድ ውስጥ የተካተቱ ናቸው ያላቸውን የሚከተሉትን ነጥቦች አስቀምጧል፡

    • በናታንዝ፣ ኢስፋሃን እና ፎርዶ የሚገኙ የኒውክሌር ተቋማት ሥራ እንዲያቆሙ እና እንዲወድሙ እንዲደረጉ
    • በኢራን ውስጥ የሚከናወኑ የኒውክሌር መረሃ ግብሮች ግልጽ እና ዓለም አቀፍ ቁጥጥር እንዲደረግባቸው
    • ኢራን በቀጣናው ያሉ ታጣቂ ቡድኖችን መርዳት እና ማስታጠቅ እንድታቆም
    • የተከማቹ የኒውክሌር ቁሶችን በሙሉ ማውደም
    • ኢራን የኒውክሌር ጦር መሳሪያ ባለቤት ለመሆን ፈጽሞ ላለመሞከር ቃል እንድትገባ
    • ምንም ዓይነት የኒውክሌር ቁስ በኢራን ውስጥ እንዳይዳብር፣ የዳበሩትም ለዓለም አቀፉ ተቋም እንዲሰጡ
    • የሆርሙዝ ወሽመጥ ክፍት እንዲሆን እና “ነጻ የባሕር ቀጣና” እንዲሆን ማድረግ
    • የኢራን ሚሳዔል በመጠን እና በሚደርስበት ርቀት ውስን እንዲሆን እና እራስን ለመከላከል ላይ ብቻ እንዲውል

    በዚህ ዕቅድ ውስጥ ኢራን የሚከተሉትን ድጋፎች ከስምምነቱ የምታገኝ ይሆናል፡

    • ኢራን ቡሽሄር ውስጥ ለኤሌክትሪክ ማመንጫነት ለምታካሂደው የኒውክሌር ግንባታ አሜሪካ ድጋፍ ታደርጋለች
    • በኢራን ላይ የተጣሉ ሁሉም ማዕቀቦች እንዲነሱ ይደረጋሉ
    • አዲስ ሊጣሉባት የሚችሉ ማዕቀቦች ይቀራሉ

    በተጨማሪም በሁለቱ ወገኖች መካከል ድርድር በሚደረግበት ጊዜ ለአንድ ወር የሚቆይ የተኩስ አቁም ይኖራል ተብሏል፤ ነገር ግን ከዋይት ሐውስ አስካሁን ምንም ዓይነት ዝርዝርም ሆነ ማረጋገጫ አልተሰጠም።