"የአሜሪካ ጥቃት ኢራንን የማንበርከክ እንጂ ከኒውክሌር ጋር ምንም ግንኙነት የለውም"- አያቶላህ ኻሜኒ

አሜሪካ በኢራን የፈጸመችው ጥቃት "ኢራንን እጅ የማሰጠት" እንጂ በጭራሽ ከኒውክሌር ማበልጸግ ጋር ፍጹም ግንኙነት እንደሌለው የአገሪቱ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ ኻሜኒ ተናገሩ።ከሳምንት በኋላ የታዩት ጠቅላይ መሪው “ሁልጊዜም ቢሆን አንድ ነገር ብቻ ነው ፍላጎታቸው፤ ኢራን እጇን እንድትሰጥ” ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

  • እስራኤል በፈጸመችው ጥቃት የአገሪቱ ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ ሳኢድ ኢዛዲ መገደላቸውን የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ማረጋገጡን የአገሪቱ ሚዲያ ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።
  • የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ ኢራን ከአሜሪካ ጥቃት በፊት የበለጸገ የዩራኒየም ክምችቷን ከፎርዶ የኒውክሌር ጣቢያ አዛውራለች የሚለውን ሪፖርት አስተባበሉ።
  • በኳታር የአሜሪካ የጦር ሰፈርን ለመከላከል የቀሩት 44 ወታደሮች ብቻ እንደነበሩ አሜሪካ ገለጸች
  • አሜሪካ 'ኦፕሬሽን ሚድናይት ሐመር' በሚል ስያሜ በኢራን ላይ የፈጸመችው ጥቃት ለ15 ዓመታት የታቀደበት እንደሆነ የአገሪቱ ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄነራል ዳን ኬይን ገለጹ።
  • በኢራን ላይ የተፈጸመው "የተሳካ ታሪካዊ ጥቃት ነበር" ሲሉ የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት ገለጹ
  • አሜሪካ በኢራን የፈጸመችው ጥቃት ኢራንን እጅ የማሰጠት እንጂ በጭራሽ ከኒውክሌር ማበልጸግ ጋር ፍጹም ግንኙነት እንደሌለው የአገሪቱ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ ኻሜኒ ተናገሩ
  • ትራምፕ፤ የአሜሪካ ጥቃት የኢራን ኒውክሌር ይዞታዎችን አላወደመም የሚለውን የደህንነት ግምገማ ውድቅ አደረጉ
  • የአሜሪካ ጥቃት የኢራን ኒውክሌር ይዞታዎችን እንዳላወደመ የደህንነት ግምገማ አሳየ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የኢራን የጦር ጄነራሎች ለአሜሪካ ጥቃት “ቆራጥ ምላሽ” እንደሚሰጥ አስጠነቀቁ

    በቴህራን ተቃውሞ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በርካታ የኢራን የጦር ጄነራሎች አሜሪካ በአገራቸው ላይ ለፈጸመችው ጥቃት “ቆራጥ ምላሽ” እንደሚሰጥ አስጠነቀቁ።

    የኢራን ጦር ዋና አዛዥ አሚር ሃታሚ የጦር መኮንኖቻቸውን በወታደራዊ ክፍል ሲያነጋግሩዋቸው የሚያሳዩ ቪዲዮ የአገሪቱ ሚዲያዎች አውጥተዋል።

    አሜሪካ ከዚህ ቀደም በኢራን ላይ በፈጸመቻቸው “ወንጀሎች ቆራጥ ምላሽ ሰጥተኛል እናም የአሁኑም ተመሳሳይ ይሆናል" ብለዋል።

    የኢራን ጦር ኃይሎች ዋና ኢታማዦር ሹም አብዶልርሃም ሞሳቪ በበኩላቸው አሜሪካ በፈጸመችው ጥቃት በቀጣናው ባሉ ወታደሮቿ ላይ ጦራቸው “ማንኛውንም እርምጃ” ሊወስዱ የሚችሉበትን እድል ከፍታለች ብለዋል።

    ኢታማዦር ሹሙ አክለውም ኢራን “በፍጹም ወደ ኋላ አትመለስም” ብለዋል።

  2. የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና ፕሬዚዳንት ፑቲን ሊወያዩ ነው

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አርጋቺ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ወደ ሞስኮ ያቀኑት የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አርጋቺ ከሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር ሊወያዩ መሆኑ ተገለጸ።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከፕሬዚዳንቱ ጋር የሚያደርጉት ውይይት መሰረታዊ እንደሆነ ገልጸው “በተለመዱ ተግዳሮቶች እና ስጋቶች” ላይ ያተኩራል ብለዋል።

    በተባበሩት መንግሥታት የሩሲያ ተወካይ አሜሪካ በኢራን የኒውክሌር ይዞታዎች ላይ የፈጸመችውን ጥቃት አውግዘው አሜሪካ በዚህም “አዙሪቱ የማያልቅ” ሁኔታን ከፍታለች ብለዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከፑቲን ጋር የሚገናኙ ከሆነ ጠንካራ የቃላት ድጋፍ ሊቸራቸው እንደሚችል ቢታመንም ከሩሲያ ወታደራዊ እርዳታ የማይመስል ነው ተብሏል።

    ለዚህም ምክንያቱ ሩሲያ ትኩረቷ ከዩክሬን ጋር የምታደርገው ጦርነት መሆኑ ነው።

    ምንም እንኳን ሩሲያ እና ኢራን የስትራቴጂክ አጋርነት ስምምነት ቢኖራቸው ይህ የመከላከያ ስምምነት አይደለም።

    ይህም ለኢራን ወታደራዊ ድጋፍ እንድትሰጥ የሚያስገድድ አይደለም።

    ባለፈው ሳምንት ኢራን ከሩሲያ ወታደራዊ እርዳታ አለመጠየቋን ፕሬዚዳንት ፑቲን ተናግረው ነበር። ፑቲን ከኢራን እና ከእስራኤል ጋር ጥሩ ግንኙነት የመሰረቱ ሲሆን፤ ከዶናልድ ትራምፕ ጋርም ጥሩ ግንኙነት ለመፍጠር ፍላጎት አላቸው።

  3. የተባባሰው የአሜሪካ- ኢራን ውጥረት አዳዲስ ክስተቶች

    ጥቃቱን በመቃወም የተደረጉ ሰልፎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    • የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በኢራን የአገዛዝ ለውጥን በተመለከተ በሰጡት አስተያየት አሁን ያለው አገዛዝ ኢራንን እንደገና ታላቅ ማድረግ ካልቻለ ለምን የመንግሥት ለውጥ አይመጣም? የሚል አስተያየት ሰጥተዋል።
    • ትራምፕ አገራቸው በኢራን ላይ የፈጸመችውን ጥቃቶች “በሁሉም የኒውክሌር ይዞታዎች” ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደረሰ፤ እንዲሁም “ማውደም የሚለው” የሚገልጸው ነው ብለዋል። ሆኖም የተባበሩት መንግሥታት የኒውክሌር ተቆጣጣሪ አካል የደረሰውን ጉዳት በትክክል ማረጋገጥ እንዳልቻለ ገልጿል።
    • የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ወደ ሞስኮ አቅንተው ከሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር ይገናኛሉ።
    • በተባበሩት መንግሥታት ጉባኤ ላይ የእስራኤል ተወካይ አለም ሁሉ ትራምፕን ሊያመሰግነው ይገባል ሲሉ የኢራኑ ተወካይ በበኩላቸው የአሜሪካን “ጥቃት አውግዘዋል።
    • አሜሪካ በኢራን ላይ የፈጸመችውን ጥቃት በማውገዝ በተለያዩ የአለም ከተሞች የተቃውሞ ሰልፎች ተካሂደዋል።
    • በኢራን ጥቃት ለመፈጸም ተሰማርተው የነበሩት ቦምብ ተሸካሚዎቹ ቢ-2 ተዋጊ ጄቶች ወደ አሜሪካ ጦር ሰፈር መመለሳቸው ተገልጿል።
  4. እስራኤል ስድስት የኢራን አየር ማረፊያዎችን በማጥቃት 15 አውሮፕላኖችን ማውደሟን አስታወቀች

    የኢራን ተቃውሞ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የእስራኤል ጦር ስድስት የኢራን ማረፊያዎች ላይ ጥቃት በመፈጸም 15 አውሮፕላኖችን ማውደሙን አስታወቀ።

    ጦሩ በተጨማሪም የአውሮፕላን ማኮብኮቢያዎችን በጥቃቱ መጉዳቱን አክሏል።

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል በማህበራዊ ሚዲያ ገጹ ላይ ባሰፈረው ጽሁፍ ጥቃቱ የተነጣጠረባቸው አየር ማረፊያዎች በአገሪቱ ምስራቅ፣ ምዕራብ እና መካከለኛው ግዛቶች መሆኑን አክሏል።

    ጦሩ እንደገለጸው በድሮን ጥቃቱ ኤፍ 15 እና ኤፍ 15 ተዋጊ ጄቶችን፣ ነዳጅ መሙያ አውሮፕላን እንዲሁም ኤች- 1 ኮብራ ሄሊኮፕተር ወድሟል።

    በተጨማሪም የአውሮፕላን ማኮብኮቢያዎችን እና የከርሰ ምድር ታንከሮች ጉዳት ደርሶባቸዋል ብሏል።

    እነዚህ ጥቃቶች መቼ እንደተከሰተ ግልጽ ባይሆንም ኢራን ጥቃቶቹን አላረጋገጠችም።

  5. አሜሪካ በዓለም ዙሪያ ላሉ ዜጎቿ ማስጠንቀቂያ አወጣች

    የአሜሪካ ሰንደቅ ዓላማ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    አሜሪካ በኢራን ላይ የፈጸመቻቸውን ጥቃቶች ተከትሎ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚገኙ ዜጎች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ማስጠንቀቂያ አውጥቷል

    ዓለም አቀፍ የደህንነት ማስጠንቀቂያ የወጣው በአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በኩል ነው።

    “የአሜሪካ ዜጎችን እና ብሄራዊ ጥቅሞችን የሚጻረሩ የተቃውሞ ሰልፎች ሊደረጉ ይችላሉ። የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በዓለም ዙሪያ ያሉ አሜሪካውያን ዜጎች የበለጠ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ይመክራል” ብሏል።

  6. ኢራን ወሳኝ የሆነውን የነዳጅ መተላለፊያ መስመር እንዳትዘጋ ተጽእኖ ለመፍጠር አሜሪካ ለቻይና ጥሪ አቀረበች

    ኢራን የዓለማችን አንድ አምስተኛው የድፍድፍ የነዳጅ ዘይት መተላለፊያ የሆነውን የሆርሙዝ ሰርጥ እንዳትዘጋ ተጽዕኖ ለመፍጠር የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ ለቻይና ጥሪ አቀረቡ።

    አሜሪካ በኢራን ላይ የፈጸመቻቸውን ጥቃት ተከትሎ በኢራን እና በኦማን መካከል የሚገኘውን የሆርሙዝ ሰርጥ እንዲዘጋ የአገሪቱ ፓርላማ መወሰኑን የኢራን መንግሥታዊ ሚዲያዎች ዘግበዋል።

    “የቻይና መንግሥት በዚህ ጉዳይ ላይ ተጽእኖ እንዲያደርግ አበረታታለሁ። ምክንያቱም እነሱም ቢሆን ነዳጅ ለማግኘት በሆርሙዝ ሰርጥ ላይ በእጅጉ ጥገኛ ስለሆኑ” ሲሉ ሩቢዮ ለፎክስ የዜና ወኪል ተናግረዋል።

    ሩቢዮ ለኢራን ባስተላለፉት መልዕክት “ይህንን ካደረጉ ሌላ አስከፊ ስህተት ነው። ለነሱም ቢሆን ኢኮኖሚያዊ ራስን ማጥፋት ነው” የሚል አስተያየት ሰጥተዋል።

    በዚህ ወሳኝ የመተላለፊያ መስመር የነዳጅ አቅርቦት መስተጓጎል ለአለም ምጣኔ ኃብት ከፍተኛ መዘዝ ያስከትላል የተባለ ሲሆን የዓለም አቀፉን የነዳጅ ዋጋ እንዲያሻቅብ ያደርገዋል።

    በተጨማሪም በዚህ መስመር ዋነኞቹ ነዳጅ አስመጪዎች ቻይና፣ ህንድና ጃፓን ከፍተኛ ችግር ያስከትልባቸዋል ተብሏል።

    ተንታኞች የሆርሙዝን ሰርጥ የመዝጋት ስልጣን ከፓርላማው ይልቅ የጸጥታ ባለስልጣናቱ ነው ይላሉ።

    ለዚህም የሚሰጡት ምክንያት ኢራን በሰርጡ በኩል ለራሷ ወጪ ንግድ የምትጠቀምበት በመሆኑ ራሷን የሚጎዳ አጸፋዊ እርምጃ እንደሆነ ይጠቅሳሉ።

    የሆርሙዝ ሰርጥ
  7. “የኢራን የኒውክሌር ይዞታዎችን አውድመናቸዋል”- ትራምፕ

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከባለስልጣኖቻቸው ጋር

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ አገራቸው በኢራን ላይ የፈጸመችውን ጥቃቶች “በሁሉም የኒውክሌር ይዞታዎች” ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደረሰ፤ እንዲሁም “ማውደም የሚለው” የሚገልጸው ነው ብለዋል።

    ትራምፕ ትሩዝ ሶሻል በተሰኘ ማህበራዊ ሚዲያቸው ላይ በጽሁፉ ላይ ያላካፈሉትን የሳተላይት ምስል በመጥቀስ “የሚታየው ነጭ መዋቅር በድንጋይ የተከበበ ነው፤ ከእሳቱም ተከልሏል” ብለዋል።

    ሆኖም “ከፍተኛው አደጋ የደረሰው ከመሬት በታች ባለው ይዞታው ነው ብለዋል።

    አክለውም “ማዕከሉን መትተነዋል” ሲሉ ገልጸዋል።

  8. አሜሪካ ሦስቱም የኢራን የኒውክሌር ጣቢያዎች “ከባድ ጉዳት” ደርሶባቸዋል አለች

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግዝ እና የአሜሪካ ጦር ኃይል የጋራ ዕዝ ሊቀ መንበር ጄኔራል ዳን ኬይን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግዝ እና የአሜሪካ ጦር ኃይል የጋራ ዕዝ ሊቀ መንበር ጄኔራል ዳን ኬይን

    አሜሪካ በኢራን ሦስት የኒውክሌር ተቋማት ላይ ስለፈጸመችው ጥቃት የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስትር እንዲሁም የአሜሪካ ጦር ኃይል የጋራ ዕዝ ሊቀ መንበር በጋራ መግለጫ ሰጥተዋል።

    ሚኒስትሩ ዛሬ በሰጡት መግለጫ አሜሪካ በኢራን የኒውክሌር ተቋማት በፈፀመችው ጥቃት "አስደናቂ እና የማይቀለበስ ስኬት" ተገኝቷል ብለዋል።

    ፒት ሄግዝ በፔንታጎን መግለጫውን ለመከታተል ለተሰበሰቡ ጋዜጠኞች እንደተናገሩት "ከዋና አዛዣችን [ትራምፕ] የተቀበልነው ትዕዛዝ ትኩረት ያለው ነበር፤ኃይለኛ እና ግልጽ ነበር። የኢራንን የኒውክሌር መርሃ ግብርን አውድመናል” ብለዋል።

    አሜሪካ ጥቃቱን ለመፈጸም ለረዥም ጊዜ ስትዘጋጅ መቆየቷን የተናገሩት መከላከያ ሚኒስትሩ "ለወራት እና ለሳምንታት ቦታ መያዝን እና መዘጋጀትን የጠየቀ እቅድ ነው" ብለዋል።

    ለጥቃቱ ቢ-2 ቦምብ ጣይ አውሮፕላን ጥቅም ላይ መዋሉን የተናገሩት ፒት ሄግዝ “ቢ-2 ቦምብ ጣይ አውሮፕላናችን ዓለም ሳይሰማ ወደ ኒውክለር ተቋሞቹ ገብቶ መውጣት ችሏል" ብለዋል።

    ሄግዝ እንደተናገሩት አሜሪካ እኩለ ሌሊት ላይ በኢራን፣ ፎርዶ፣ ናታንዝ እና ኢስፋሃን በሚገኙ ሦስት የኒውክሌር ተቋማት ላይ ያነጣጠረ ጥቃት አድርሳለች።

    "የኢራንን የኒውክሌር መርሃ ግብርን አውድመናል፣ ነገር ግን ኦፕሬሽኑ የኢራን ወታደሮችን እና የኢራንን ሕዝብ ላይ ያነጣጠረ እንዳልሆነ ልብ ሊባል ይገባል" ሲሉ ሄግዝ አክለዋል።

    ሄግዝ አክለውም “ይህ ተልዕኮ የስርዓት ለውጥ አልነበረም፤ አይደለምም” ብለዋል።

    በፔንታጎን ከመከላከያ ሚኒስትሩ ጋር በመሆን መግለጫ የሰጡት ጄኔራል ዳን ኬይን፣ የአሜሪካ ጦር ኃይል የጋራ ዕዝ ሊቀ መንበር፣ ኢራን ላይ የተፈጸመው ጥቃት በተለያዩ የመከላከያ ክፍሎች “የታቀደ እና ተግባራዊ የሆነ” መሆኑን ተናግረዋል።

    አክለውም ቢ-2 ቦምብ ጣይ አውሮፕላን አርብ ዕለት ከአሜሪካ ተነስቶ ለ18 ሰዓታት ወደ ዒላማው መብረሩን ገልፀዋል።

    ዘመቻው “ኦፕሬሽን ሚድ ናይት ሐመር” ተብሎ እንደተጠራ የተናገሩት ጄነራሉ፣ በርካታ “የማሳሳቻ እና የማደናገርያ” ስልቶችን መጠቀማቸውን አብራርተዋል።

    ስለ ኦፕሬሽኑ ዝርዝር ሁኔታ የተናገሩት ጄነራል ኬይን ቦምብ ጣይ አውሮፕላኖቹ ከአሜሪካ ተነስተው አንዳንዶቹ ወደ ምዕራብ ፓሲፊክ ውቅያኖስ እንደ "ማታለያ" መብረራቸውን ገልጸዋል።

    ኬይን 75 “ዒላማቸውን በሚገባ አነጣጥረው የሚለዩ መሳርያዎች”፤14 "ግዙፍ ኦርዳንስ ፔኔትሬተርስ" እንዲሁም "ምሽግ ደርማሽ" በመባልም የሚታወቁት ቦምቦችን ጨምሮ ጥቅም ላይ መዋላቸውን አስረድተዋል።

    ከኢራን መከላከያ ምንም ዓይነት የመከላከል እርምጃ እንዳልገጠማቸው ሲገልፁም “ምንም የተተኮሰ ነገር የለም” ብለዋል።

    ኬይን “የኢራን ተዋጊዎች በአየር ክልሉ ላይ አልነበሩም። እናም የኢራን የሚሳዔል ስርዓቶች አላዩንም” ብለዋል።

    ቦምብ ጣይ አውሮፕላኖቹ ወደ አሜሪካ በመመለስ ላይ መሆናቸውንም አክለው ተናግረዋል።

  9. እንደ ፎርዶ ያሉ የኢራን የኒውክሌር ጣቢያዎችን ማጥቃት ምን ዓይነት አደጋዎች ሊያስከትል ይችላል?

    የኢራን ናታንዝ የኒውክሌር ጣቢያ የእራኤል የአየር ጥቃት ዒላማ ሆኗል

    የፎቶው ባለመብት, GETTY IMAGES / MAXAR TECHNOLOGIES

    እስራኤል በኢራን ላይ እየፈፀመችው ባለው ጥቃት የኒውክሌር መሠረተ ልማቷን ዒላማ አድርጋለች።

    በዋናነት ትኩረቷን ያደረገችው ደግሞ ከምድር በታች የሚገኙ የዩራኒየም ማበልጸጊያ ማዕከላቷ ላይ ነው።

    እንደ ዓለም አቀፉ የአውቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ከሆነ በአገሪቷ ማዕከላዊ ክፍል የሚገኘው ናታንዝ የኒውክሌር ጣቢያ የደረሰበትን ከባድ ጉዳት ተቋቁሟል።

    ሌላኛው ፎርዶ የሚባለው ማዕከሏ ደግሞ በተራራ ሥር ከመሬት በታች በጥልቀት የተገነባ ነው።

    አሜሪካ ዛሬ ማለዳ ላይ ጥቃት ከፈጸመችባቸው ሦስት የኒውክሌር ተቋማት መካከል አንዱ የሆነው ፎርዶን ለመምታት እጅግ ኃይለኛ የሆነ ቦምብ ጥቅም ላይ ውሏል።

    ከዚህ ቀደም ዓለም አቀፉ የአውቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ የኢራን የኒውክሌር ማዕከላት ላይ የተፈፀመውን ጥቃት "እጅግ አሳሳቢ" ሲል ገልጾታል።

    የኤጄንሲው ዋና ዳይሬክተር ራፋኤል ግሮሲ ሰኞ ዕለት እንደተናገሩት "የወታደራዊ እርምጃዎች መባባስ በሰዎች እና በአካባቢ ላይ ከባድ ጉዳት የሚያስከትሉ ጨረሮች የመለቀቅ አደጋን ይጨምራል" ብለዋል።

    የዩራኒየም ማበልጸጊያ ጣቢያዎች ወደተለያየ ቁስ አካል የመለወጥ ባህርይ ባላቸው አይሶቶፕስ ከተባሉ ኬሚካላዊ ንጥረ ነገሮች የሚሠሩ ቁሶችን ለማዘጋጀት ያገለግላሉ።

    በሰሪይ ዩኒቨርሲቲ እና በዩናይትድ ኪንግደም ብሔራዊ የፊዚክስ ቤተ ሙከራ ፕሮፌሰር የሆኑት ፓዲይ ሬጋን ዩራኒየምን ከመሬት ውስጥ ሲወጣ በሁለት መልክ እንደሚወጣ ያስረዳሉ።

    "99.3 በመቶው ዩራኒየም-238 ሲሆን 0.7 በመቶው ደግሞ ዩራኒየም-235 ነው። የኒውክሌር የጦር መሣሪያ ለመሥራት የሚያስፈልገው ደግሞ ሁለተኛው ነው" ይላሉ።

  10. የአረብ አገራት አሜሪካ በኢራን የኒውክሌር ተቋማት ላይ ስለፈጸመችው ድብደባ ምን ምላሽ ሰጡ?

    አሜሪካ በኢራን የኒውክሌር ተቋማት ላይ የፈጸመችው የቦንብ ድብደባ በሰዓታት ውስጥ በርካታ ዓለም አቀፍ ምላሽ አስከትሏል።

    ምላሻቸውን በመስጠት የቀደሙት የአረብ አገራት ናቸው።

    በዋሽንግተን እና በቴህራን መካከል የኒውክሌር ውይይቶችን እያሸማገለች የነበረችው ኦማን፤ አሜሪካ በኢራን የኒውክሌር ተቋማት ላይ የፈጸመችውን ጥቃት አጥብቃ አውግዛለች።

    የባህረ ሰላጤው ሱልጣኔቷ፤ “በዩናይትድ ስቴትስ በቀጥታ በተፈፀሙ የአየር ድብደባዎች ምክንያት የተከሰተውን እጅግ አሳሳቢ መባባስ [ኦማን] ትኮንናለች፣ ታወግዛለች” ስትል አቋሟን ገልጻለች።

    ከአሜሪካ ጋር ጠንካራ የደህንነት ትስስር ያላት እና በቀጣናው የአሜሪካ የቅርብ አጋር የሆነችው ሳዑዲ አረቢያ፤ “የኢራንን ሉዓላዊነት መጣስን” አውግዛ፤ ከእንደዚህ ዓይነት ድርጊቶች “መቆጠብ አስፈላጊ እንደሆነ አጽንኦት” ሰጥታለች።

    ዓለምኅአቀፉ ማህበረሰብም “እነዚህ እጅግ አሳሳቢ ሁኔታዎችን በተመለከተ ፖለቲካዊ መፍትሄ ላይ ለመድረስ ጥረቱን እንዲያጠናክር” ጥሪ አቅርባለች።

    የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በበኩሉ አሁን እየታየ ያለው “አደገኛ ውጥረት በቀጣናው እና በዓለም አቀፍ ደረጃ አስከፊ መዘዞችን ያስከትላል” ሲል አስጠንቅቋል።

    “በዚህ ወቅት ሁሉም ወገኖች ጥበብ እና መቆጠብን ተግባራዊ ያደርጋሉ የሚል ተስፋ” እንዳለው ገልጿል።

    ግብጽ “ቀጣናው ወደ ቀጣይ ትርምስ እና ውጥረት የመግባት አደጋ” እንደተጋረጠበት በመግለጽ አስጠንቅቃለች።

    “ከቀውሱ ለመውጣት የፖለቲካ መፍትሄዎች እና ዲፕሎማሲያዊ ድርድሮች እንጂ ወታደራዊ አማራጮች ብቸኛ መንገድ አይደሉም" ስትልም አሳስባለች።

    የሊባኖስ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ አውን በበኩላቸው፤ "የኢራን የኒውክሌር ተቋማት ድብደባ፤ ሁኔታው ከአንድ በላይ የሆኑ ቀጣና እና አገራትን ደህንነት እና መረጋጋትን አደጋ ላይ የሚጥል ውጥረት ይፈጠራል የሚለውን የፍርሃት ደረጃ ከፍ ያደርጋል" ብለዋል።

  11. አሜሪካ ለማውደም የምትፈልገው እና ከምድር በታች የሚገኘው የኢራን የኒውክሌር ተቋም

    ፎርዶ የኒውክሌር ተቋም የሚገኝበትን የሚያሳይ የሳተላይት ምስል

    ዛሬ ማለዳ አሜሪካ ሦስት የኢራን የኒውክሌር ተቋማትን በቦምብ መደብደቧን ተናግራለች። እነዚህም ፎርዶ፣ ናታንዝ እና ኢስፋሃን ናቸው።

    የእስራኤል መከላከያ በእነዚህ ተቋማት ላይ የደረሰውን ውድመት መጠን እየገመገመ መሆኑን ገልጿል።

    በአሜሪካ ጥቃት ዒላማ የነበረው ፎርዶ ከዋና ከተማዋ ቴህራን በስተደቡብ በሚገኝ ተራራማ አካባቢ ከመሬት በታች በጥልቅ ዋሻዎች ውስጥ የተሸሸገ ነው።

    ፎርዶከምድር በታች ያለው ጥልቀት እስራኤል ባሏት የጦር መሳሪያዎች ለመድረስ አስቸጋሪ ነው።

    ፎርዶንለማውደም የሚያስችል ጠንካራ እና ትልቅ "ምሽግ ደርማሽ" ቦምብ ያላት ደግሞ አሜሪካ ብቻ ናት።

    አሜሪካያላት ቦምብ ጂቢዩ-57 ማሲቭ ኦርዲናንስ ፔኔትሬተር (ኤምኦፒ) ይባላል።

    ክብደቱ 13,000 ኪ.ግ ሲሆን ባለሙያዎች ከመፈንዳቱ በፊት ወደ 18 ሜትር ኮንክሪት ወይም 61 ሜትር መሬት ውስጥ ዘልቆ መግባት ይችላል ይላሉ።

    የፎርዶዋሻዎች ከመሬት በታች ከ 80 እስከ 90 ሜትር ርቀት ላይ እንደሚገኙ ይታመናል።

    ስለዚህምኤምኦፒ ውጤታማ በሆነ መልኩ ያወድመዋል ብሎ አፍን ሞልቶ መናገር አይቻልም።

    ነገርግን ተቋሙን ለማውደም ሊቀርብ የሚችለው ብቸኛው ቦምብ ነው።

    የአሜሪካባለሥልጣናት በጥቃቱ ወቅት ኤምኦፒን ጥቅም ላይ መዋሉን ለሲቢኤስ ያረጋገጡ ሲሆን፣ ለእያንዳንዱ ዒላማ ሁለት ሁለት ቦምቦች ተጠቅመዋል።

  12. የእስራኤል ጦር የአሜሪካ ጥቃት በኢራን የኒውክሌር ተቋም ላይ ያደረሰውን ውድመት እየገመገመ መሆኑን ገለፀ

    የእስራኤል ጦር  ቃል አቀባይ ኤፊ ዴፍሪንም

    የፎቶው ባለመብት, IDF

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል ቃል አቀባይ የአሜሪካ ጥቃት በኢራን የኒውክሌር ተቋም ላይ ያደረሰውን ውድመት እየገመገሙ መሆኑን ገለፁ።

    ኢራን የበለፀገ ዩራኒየም ከአሜሪካ ጥቃት በፊት ከኒውክሌር ተቋማቱ እንዲወጣ ተደርጓል ስትል ያስተባበለች ቢሆንም፣ የማስተባበያውን እውነትነት "ለመወሰን በጣም ገና ነው" ብለዋል።

    ቃል አቀባዩ ኤፊ ዴፍሪንም በፎርዶ የኒውክሌር ተቋም ላይ የደረሰውን የጉዳት መጠን እየመረመሩ መሆኑን አስረድተዋል።

    ፎርዶ የዩራኒየም ማበልጸጊያ ማዕከል ራቅ ባለ ተራራማ ስፍራ ተሸሽጎ የሚገኝ ተቋም ነው።

    ዴፍሪን እስራኤል የጥቃት ዒላማዋን አስፍታ ሰላማዊ ዜጎች የሚኖሩባቸው አካባቢዎችን ታጠቃ እንደሆን ተጠይቀው በደፈናው "ዒላማዎችን የለየ ዕቅድ አለን እና እነዚህን ዒላማዎችን መምታታችንን እንቀጥላለን" ብለዋል።

  13. ወደ አገራቸው እስኪመለሱ "ቀናቸውን የሚቆጥሩ" በቱርክ የሚገኙ ኢራናውያን

    ከኢራን ድንበር 96 ኪሜ ርቀት ላይ በምትገኘው የቱርኳ ቫን ከተማ በሚገኝ አንድ ሆቴል ውስጥ አብዛኞቹ እንግዶች ኢራናውያን ናቸው።

    ሁሉም ስለ አገራቸው ሁኔታ ለማወቅ በመጓጓት ዓይናቸውን ከቴሌቪዥኑ ላይ መንቀል አይፈልጉም።

    አሜሪካ በኢራን የኒውክሌር ተቋማት ስለፈጸመችው ድብደባ በማንሳት ያወራሉ።

    አንድ እናት “በጣም ተናደናል” አሉ።

    “ዶናልድ ትራምፕ ልዕለ ኃያል ነኝ ብሎ በማሰብ የሚፈልገውን ሁሉ ያደርጋል” ካሉ በኋላ ሌላ ጥያቄ ከመጠየቃቸው በፊት “ለምንድን ነው ማንም እስራኤልን እና አሜሪካንን ማቆም ያልቻለው?” ሲሉ ጠየቁ።

    ከቴህራን ወደ ቱርክ ቫን ዛሬ ማለዳ ላይ የመጡት ወደ ካናዳ የምትሄደው ልጃቸውን ለመቀላቀል ነው።

    የ26 ዓመቷ ሴት ልጃቸው “ሰዎች በጣም የተጨነቁ እና የተደናገጡ ይመስለኛል፤ ምክንያቱም በአገሪቱ ውስጥ ምን እንደሚሆን ስለማያውቁ ነው” ብላለች።

    አገራቸውን ጥለው ወደ ጎረቤት አገር ቱርክ የተሰደዱት ኢራናውያን በቀጣይ የሚሆነውን ባለማወቅ ተጨንቀዋል።

    በኢራን እና በእስራኤል መካከል ግጭት በተጀመረበት ቀን ቴህራንን ለቅቆ መውጣቱን የሚናገር ሌላ ኢራናዊ ግጭቱ ቶሎ ያበቃል በሚል ከእናቱ እና ከእህቱ ጋር ሆቴል መቆየት መምረጣቸውን ይናገራል።

    አሜሪካ በኢራን ላይ ስለፈጸመችው ጥቃት ሲጠየቅ “አዝኛለሁ፤ የሚቆም አይመስልም” ብሏል።

    ቱርክ ውስጥ “ለአጭር ጊዜ” ብቻ እንደሚቆይ አስቦ መምጣቱን የሚናገረው ይህ ኢራናዊ፣ አሁን ግን “ለረዥም ጊዜ” መቆየቱ እንደማይቀር ተሰምቶታል።

    ቴህራን ውስጥ በንግድ ስራ እንደሚተዳደር የሚናገረው ግለሰቡ፣ ለመመለስ “ቀን እየቆጠርኩ ነው” ይላል።

    "ሌላ ሁለት ወይም ሦስት ሳምንትብቻ ነው መቆየት የምችለው፤ ከዚያ በኋላ ግን የያዝኩት ገንዘብ ያልቃል።አሁን በጣም አሳስቦኛል።"

    ከኢራን ወደ ቱርክ ቫን ከተማ የመጣው የ28 ዓመቱ ተማሪ ማጅድ ደግሞ በኢራን የቀሩትን ቤተሰቦቹን ማየት አለመቻሉ አስጨንቆታል።

    " ያለማቋረጥ የማስበው ነገር ነው።"

  14. የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር - እንዴት ወደ ድርድር ጠረጴዛ እንመለሳለን? ቀድሞውንስ መቼ ተውነው?

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ፤ባለፈው ሳምንት ላይ እስራኤል እና አሜሪካ የዲፕሎማሲ አማራጭን "ለማፍረስ" እንደወሰኑ ተናገሩ።

    ሚኒስትሩ በኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ ባለፈው ሳምንት ከአሜሪካ ጋር ድርድር በተካሄደበት ወቅት “እስራኤል ዲፕሎማሲውን ለማፍረስ ወስናለች” ብለዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚንስትር አባስ አራግቺ ባለፈው ሳምንት እስራኤልም ሆነ አሜሪካ ዲፕሎማሲን" ለመፍረስ" እንደወሰኑ ተናግረዋል።

    ከአውሮፓ ባለስልጣናት ጋር በተደረገው ውይይት ወቅትም ተመሳሳይ ነገር እንደተከሰተ የተናገሩት ሚኒስትሩ፤ ነገር ግን "አሜሪካ ያንን ዲፕሎማሲን ለማፍረስ ወሰነች” በማለት ጽፈዋል።

    “ምን ዓይነት ድምዳሜ ላይ ትደርሳላችሁ?” ሲሉም ጠይቀዋል።

    አራግቺ አክለውም፤ "እንደ ብሪታንያ እና ለአውሮፓ ኅብረት ከፍተኛ ተወካይ [አመለካከት]፤ ወደ ውይይቱ ጠረጴዛ መመለስ ያለበት ኢራን ናት። ግን ኢራን እንኳን [ድርድሩን] ማፍረስ ቀርቶ ጭራሹኑ ጥላው ወዳልወጣችው ነገር እንዴት መመለስ ትችላለች?” ብለዋል።

    የዩናይትድ ኪንግደም የጠቅላይ ሚኒስትር ኬር ስታርመር ኢራን ወደ ድርድር ጠረጴዛ እንድትመለስ ጥሪ ባቀረቡበት ወቅት፤ የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢራን “እንድትረጋጋ” አሳስበው ነበር።

    የኢራን ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

  15. ዩኬ የብሪታኒያ ዜጎችን ከእስራኤል ለማስወጣት ዝግጁ መሆኗን አስታወቀች

    ዩኬ የብሪታንያ ዜጎችን እና ቤተሰቦቻቸውን ከእስራኤል እና በእስራኤል ቁጥጥር ስር ከሚገኙት የፍልስጤም ግዛቶች ለማሰወጣት አውሮፕላን አዘጋጀች።

    የአገሪቱ ውጪ ጉዳይ መስሪያ ቤት የብሪታንያ ዜጎች እንዲመዘገቡ እና ፍላጎታቸውን እንዲያሳውቁ የጠየቀ ሲሆን “እንደሚኖረው ፍላጎት ታይቶ “ ተጨማሪ በረራዎች ይዘጋጃሉ ብሏል።

    የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤቱ ባወጣው መግለጫ፣ በበረራው ለመሳፈር ብቁ የሆኑ ሰዎች የቲኬት ወጪያቸውን እንዲሸፍኑ እንደሚጠበቅባቸው የገለጸ ሲሆን፣ይህም “ከዚህ ቀደም በቀጠናው ይደረጉ የነበሩ ቻርተር በረራዎች ላይ ከነበረን አሰራር ጋር የተጣጣመ ነው” ብሏል።

    መግለጫው አክሎም "የንግድ በረራዎች ከግብፅ እና ከዮርዳኖስ አሁንም እንደቀጠሉ ናቸው። ወደ እነዚህ አገራት ዓለም አቀፍ ድንበር ማቋረጫዎች ክፍት ናቸው" ሲል አስታውቋል።

  16. የአሜሪካ ጥቃት ”የዓለም አቀፍ ሕግ ጥሰት ነው” - በዩኬ የኢራን አምባሳደር

    አምባሳደር ሴይድ አሊ ሙሳቪ

    በዩናይትድ ኪንግደም የኢራን አምባሳደር፤ አሜሪካ ትናንት ምሽት ኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት የተባበሩት መንግሥታት ቻርተርን “ችላ” ብላለች በማለት ከሰሱ።

    አምባሳደር ሴይድ አሊ ሙሳቪ፤ የአሜሪካ ጥቃት "የዓለም አቀፍ ሕግ ጥሰት" ነውበማለት ለቢቢሲ የተናገሩ ሲሆን በአገሪቱ የኒውክሌር ተቋማት ላይ ስለደረሰው ጉዳት የቀረቡላቸውን ጥያቄዎች ግን ከመመለስ ተቆጥበዋል።

    ጥቃቶቹ በኢራን "ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት" የተፈጸሙ ጥሰቶች ናቸው ብለዋል።

    አሜሪካ በድጋሚ ጥቃት ከፈፀመች ኢራን የኒውክሌር ፍላጎቷን በመተው ከእስራኤል ጋር የሚደረገውን ጦርነት ታቆም እንደሆን ጥያቄ ቀርቦላቸዋል።

    አምባሳደር ሙሳቪ በሰጡት ምላሽ፤ "የእስራኤል አገዛዝ ጥቃት ሳይፈጽምብን በፊት” ኢራን እና አሜሪካ የኒውክሌር ውይይቶች እያደረጉ ነበር ብለዋል።

    ባለፈው አንድ ሳምንት ውስጥ በሁለቱም ወገኖች ንጹሃን ስለመገደላቸው የተነሳላቸው አምባሳደሩ፤“እኛ እየተከላከልን ነው” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል።

  17. የዩኬ ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ኢራን “እንድትታቀብ” ጥሪ አቀረቡ

    የዩናይትድ ኪንግደም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴቪድ ላሚ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የዩናይትድ ኪንግደም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴቪድ ላሚ አሜሪካ በኢራን ሦስት የኒውክሌር ተቋማት ላይ ባደረሰችው ድብደባ “ዩናይትድ ኪንግደም . . .አልተሳተፈችም” አሉ።

    የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ ቀደም ሲል ጠቅላይ ሚንስትር ኬይር ስታርመር የሰጡትን አስተያየት በማጠናከር "ዩናይትድ ስቴትስ በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ላይ ሊደርስ የሚችለውን ስጋት ለማቃለል እርምጃ ወስዳለች" ብለዋል።

    ኢራን “ምንም ዓይነት የኒውክሌር ጦር መሳሪያ ሊኖራት አይገባም” ያሉት ውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ፣ አገሪቱ “እንድትታቀብ እና ቀውሱን ለማስቆም ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ ላይ እንድትደርስ” ጠይቀዋል።

  18. የተባበሩት መንግሥታት የኒውክሌር ተቆጣጣሪ አስቸኳይ ስብሰባ ሊያካሂድ ነው

    የመንግሥታቱ ድርጅት የኒውክሌር ተቆጣጣሪ ኃላፊ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የዓለምአቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ በነገው ዕለት አስቸኳይ ስብሰባ እንደሚያካሂድ የመንግሥታቱ ድርጅት የኒውክሌር ተቆጣጣሪ ኃላፊ አስታወቁ።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢራን የኒውክሌር ኃላፊ መሀመድ ኤስላም ቴህራን በአሜሪካ ጥቃት ላይ ምርመራ እንዲደረግ እንደምትፈልግ እና ተቆጣጣሪው አካል የአሜሪካን እርምጃ እንዲያወግዝ ማሳሰባቸውን የኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

    ቀደም ሲል ተቆጣጣሪ ኤጀንሲው አሜሪካ በኢራን ሦስት የኒውክሌር ተቋማትን ከመታች በኋላ የጨረር መጠን " መጨመር እንደሌለ" አረጋግጧል።

  19. 'መጪዎቹ ቀናት ፈታኝ ሊሆኑ ይችላሉ' - የእስራኤል ፕሬዚደንት

    የእስራኤል ፕሬዚደንት አይዛክ ሄርዞግ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የእስራኤል ፕሬዚደንት ዶናልድትራምፕ በኢራን ላይ የፈጸሙትን ጥቃት “ታሪካዊ” ሲሉ አደነቁ።

    አይዛክ ሄርዞግ የትራምፕ ቃላት በአሜሪካ እና በእስራኤል መካከል ያለውን "ጥልቅ እና የማይበገር ጥምረት" ያሳያሉ ብለዋል።

    ነገር ግን “ዘመቻው አላለቀም” በማለት አስጠንቅቀዋል።

    “መጪዎቹ ቀናት ስሱ፣ ውስብስብ እና ፈታኝ ሊሆኑ ይችላሉ” በማለት እስራኤላውያን የባለስልጣኖችን የሕይወት አድን መመሪያዎችን እንዲከተሉ አሳስበዋል።

  20. የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ኢራን ወደ ድርድር ጠረጴዛ መመለስ አለባት አሉ

    ስታርመር

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ኬይር ስታርመር አሜሪካ የኢራን የኒውክሌር መርሃ ግብር የደቀነውን "ከባድ ስጋት" “ለመቀነስ” እርምጃ ወስዳለች አሉ።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመግለጫቸው ላይ “የኢራን የኒውክሌር መርሃ ግብር ለዓለም አቀፍ ደህንነት ትልቅ ስጋት ነው።ኢራን የኒውክሌር ጦር መሳሪያ እንድታበለጽግ በፍፁም አይፈቀድላትም፤ እናም አሜሪካ ያንን ስጋት ለመቀነስ እርምጃ ወስዳለች።

    "በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው ሁኔታ ተለዋዋጭ በመሆኑ ለአካባቢው መረጋጋት ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ነው። ኢራን ወደ ድርድር ጠረጴዛው እንድትመለስ እና ይህን ቀውስ ለማስወገድ ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ እንድትፈልግ እንጠይቃለን።"

    አሜሪካ በኢራን የኒውክሌር ተቋማት ላይ በፈጸመችው ጥቃት ዩናይትድ ኪንግደም ተሳትፎ አለማድረጓን ቢቢሲ ያገኛቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ስታርመር ጥቃት ከመፈፀሙ አስቀድሞ እንዲያውቁ መደረጉን ምንጮች ለቢቢሲ ገልፀዋል።