የኢራን መንግሥት የመገናኛ ብዙኃን አሜሪካ ለፈጸመችው ጥቃት ምላሽ ኢራን “ግዙፍ እና ድል
የሚያቀዳጅ” ጥቃት መሰንዘር መጀመሯን አስታውቀዋል።
የኢራን መንግሥት የዜና ወኪል የሆነው ‘ታስኒም’ እንደዘገበው በኳታር እና በኢራቅ ውስጥ
በሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች ላይ የኢራን አብዮታዊ ዘብ ሚሳዔሎችን ተኩሷል።
ከዚሁ ጋር በተያያዘ በኳታር ዋና ከተማ ዶሃ ውስጥ ፍንዳታዎች መሰማታቸው ሮይተርስ እና ኤኤፍፒ የዜና ወኪሎች
ዘግበዋል።
በኳታር አል ኡዳይድ በሚገኘውና በአሜሪካ በሚመራው ጥምር የአየር ኃይል ኦፕሬሽን ማዕከል
ላይ ጥቃት ሊደርስ ይችላል የሚል "ተጨባጭ ስጋት" መኖሩን ቢቢሲ መረጃ አግኝቶ ነበር።
ቀደም ሲል የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ኢራን በኳታር ውስጥ በሚገኝ የአሜሪካ ወታደራዊ ሰፈር
ላይ ሚሳዔሎችን ለመተኮስ እየተዘጋጀች ነው ብለው ነበር።
አገሪቱ አሁን ላይ በጊዜያዊነት የአየር ክልሏን የዘጋች ሲሆን የጦር ሠፈሩም በተጠንቀቅ
ላይ እንደሚገኝ የቢቢሲ የደኅንነት ዘጋቢ ተነግሮኛል ብሏል።
ስጋቱ የመጣው ኢራን በአየር ኃይል የጦር ሠፈሩ ላይ የሚሳዔል ጥቃት ትሰነዝራለች ከሚል
ነው።
አሜሪካ በኢራን የኒውክሌር ማዕከላት ላይ ጥቃት ከፈፀመች በኋላ ኢራን “ተመጣጣኝ እርምጃ”
እንደምትወስድ ዝታለች።
የአሜሪካን ጨምሮ በኳታር የሚገኙ የተለያዩ አገራት ኤምባሲዎችም ዜጎቻቻው እንዲጠነቀቁ እያሳሰቡ
ነው።
አል ኡዳይድ ከኳታር መዲና ዶሃ ወጣ ብሎ የሚገኝ ግዙፍ የጦር ሰፈር ሲሆን፣ አሜሪካ በመካከለኛው
ምሥራቅ ለምታደርጋቸው የአየር ዘመቻዎች የማዕከላዊ ዕዝ ዋና መሥሪያ ቤት መገኛ ነው። የብሪታንያ ወታደሮችም በዚሁ የጦር ሰፈር
እየተቀያየሩ ያገለግላሉ።