"የአሜሪካ ጥቃት ኢራንን የማንበርከክ እንጂ ከኒውክሌር ጋር ምንም ግንኙነት የለውም"- አያቶላህ ኻሜኒ

አሜሪካ በኢራን የፈጸመችው ጥቃት "ኢራንን እጅ የማሰጠት" እንጂ በጭራሽ ከኒውክሌር ማበልጸግ ጋር ፍጹም ግንኙነት እንደሌለው የአገሪቱ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ ኻሜኒ ተናገሩ።ከሳምንት በኋላ የታዩት ጠቅላይ መሪው “ሁልጊዜም ቢሆን አንድ ነገር ብቻ ነው ፍላጎታቸው፤ ኢራን እጇን እንድትሰጥ” ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

  • እስራኤል በፈጸመችው ጥቃት የአገሪቱ ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ ሳኢድ ኢዛዲ መገደላቸውን የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ማረጋገጡን የአገሪቱ ሚዲያ ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።
  • የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ ኢራን ከአሜሪካ ጥቃት በፊት የበለጸገ የዩራኒየም ክምችቷን ከፎርዶ የኒውክሌር ጣቢያ አዛውራለች የሚለውን ሪፖርት አስተባበሉ።
  • በኳታር የአሜሪካ የጦር ሰፈርን ለመከላከል የቀሩት 44 ወታደሮች ብቻ እንደነበሩ አሜሪካ ገለጸች
  • አሜሪካ 'ኦፕሬሽን ሚድናይት ሐመር' በሚል ስያሜ በኢራን ላይ የፈጸመችው ጥቃት ለ15 ዓመታት የታቀደበት እንደሆነ የአገሪቱ ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄነራል ዳን ኬይን ገለጹ።
  • በኢራን ላይ የተፈጸመው "የተሳካ ታሪካዊ ጥቃት ነበር" ሲሉ የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት ገለጹ
  • አሜሪካ በኢራን የፈጸመችው ጥቃት ኢራንን እጅ የማሰጠት እንጂ በጭራሽ ከኒውክሌር ማበልጸግ ጋር ፍጹም ግንኙነት እንደሌለው የአገሪቱ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ ኻሜኒ ተናገሩ
  • ትራምፕ፤ የአሜሪካ ጥቃት የኢራን ኒውክሌር ይዞታዎችን አላወደመም የሚለውን የደህንነት ግምገማ ውድቅ አደረጉ
  • የአሜሪካ ጥቃት የኢራን ኒውክሌር ይዞታዎችን እንዳላወደመ የደህንነት ግምገማ አሳየ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የኢራን ፓርላማ ከተመድ የኒውክሌር ተቆጣጣሪ ጋር አገሪቷ መተባባር እንድታቆም ድምጽ ሰጠ

    የኒውክሌር ይዞታዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን ፓርላማ ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኒውክሌር ተቆጣጣሪ፣ አለም አቀፉ አቶሚክ ኤነርጂ ኤጀንሲ አገሪቷ የሚኖራት ትብብር እንዲቆም የሚያግድ ድምጽ መስጠቱን የአገሪቱ መንግሥታዊ ሚዲያዎች ዘግበዋል።

    አለም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲእስራኤል እና አሜሪካ በኢራን የኒውክሌር ይዞታዎች ላይ የፈጸሙትን ጥቃት ለማውገዝ ፈቃደኛ አልሆነም በማለት የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ መሐመድ ባገር ጋሊባ ተናግረዋል።

    በዚህም የኤጀንሲው “አለም አቀፍ ተዓማኒነቱን ለሽያጭ አቅርቧል” ሲሉ ተችተዋል።

    አፈ ጉባኤው የኢራን የኒውክሌር ባለስልጣናት የአገሪቱ “የኒውክሌር ማብላያ ይዞታዎች ደህንንት እስኪረጋገጥ ድርሰ ከኤጀንሲው ጋር ያላቸውን ትብብር ያቆማሉ” ብለዋል።

    አክለውም የኢራን “ሰላማዊ የኒውክሌር መርሃ ግብር በፈጣን ፍጥነት ወደፊት አንደሚራመድ” ተናግረዋል።

    በፓርላማ የተሰጠው ድምጽ ተምሳሌታዊ ሲሆን ውሳኔው ፖሊሲ እንዲሆን በኢራን መንግሥት ባሉ ከፍተኛ ባለሰረልጣናት መጽደቅ ይኖርበታል።

    ከአውሮፓውያኑ 1970 ጀምሮ 191 አገራት የኒውክሌር የጦር መሳሪያዎች ሥርጭት እና መስፋፋትን ለመከላከል ያለመውን 'ትሪቲ ኦን ዘ ነን ፕሮሊፈሬሽን ኦፍ ኒውክሌር ዌፐንስ' የተሰኘውን ስምምነት ፈርመዋል።

    አምስት አገራት አሜሪካ፣ ሩሲያ፣ ዩናይትድ ኪንግደም፣ ፈረንሳይ እና ቻይና የኒውክሌር የጦር መሳሪያ እንዲኖራቸው ተፈቅዶላቸዋል።

    ለዚህም ምክንያቱ ስምምነቱ ሥራ ላይ ከመዋሉ በፊት የኒውክሌር የጦር መሳሪያ ገንብተው ሙከራ አድርገው በማጠናቀቃቸው ነው።

    ኢራን የስምምነቱ ፈራሚ አባል ናት።

  2. ትራምፕ በኢራን የስርዓት ለውጥ አልፈልግም አሉ

    አያቶላህ ኻሜኒ እና ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    ከጥቂት ቀናት በፊት በኢራን የኒውክሌር ይዞታዎች ላይ ጥቃት የፈጸሙት የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በኢራን የስርዓት ለውጥ እንደማይፈልጉ ተናገሩ።

    “ሁሉም ነገር በተቻለ ፍጥነት ተረጋግቶ ማየት እፈልጋለሁ። የአገዛዝ ለውጥ ሁከት ይፈጥራል፤ እናም በእውነቱ ያን ያህል ቀውስ ማየት አንፈልግም” ሲሉ ተናግረዋል።

    ትራምፕ በተጨማሪም የሩሲያው አቻቸው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን በኢራን ግጭት ላይ እገዛ ለማድረግ መደወላቸውን ገልጸዋል።

    ከፑቲን የቀረበላቸውን እርዳታ ውድቅ አድርጌያለሁ ያሉት ትራምፕ በምላሹም “ከኢራን ጋር እርዳታ አልፈልግም፤ እገዛ የምፈልገው ካንተ ጋር ነው” ብለው ምላሽ እንደሰጡ ተናግረዋል።

  3. የጸና የሚመስለው የእስራኤል እና ኢራን የተኩስ አቁም

    በኢራን ላይ የደረሰው ጥቃት

    ከአስራ ሁለት ቀናት ገደማ በኋላ ኢራን እና እስራኤል ጸጥታ ሰፍኖባቸዋል።

    የአገራቱ ነዋሪዎችም ለሁለት ሳምንታት ያህል ሰቀቀን ሆኖባቸው ከነበረው ፍንዳታዎች፣ የጥቃት ማስጠንቀቂያዎች ድምጽ እፎይ ብለዋል።

    ለመሆኑ በትናንትናው እለት አገራቱን አስመልክቶ የተፈጠሩ አዳዲስ ክስተቶች ምንድን ናቸው?

    • የአሜሪካ የመከላከያ የደህንነት ኤጀንሲ አሜሪካ በኢራን ላይ የፈጸመችው ጥቃት የኒውክሌር ማብላያ ይዞታዎችን እንዳላወደመ እና ምናልባትም በወራት ወደኋላ ሊመልሰው እንደሚችልያደረገው ቅድመ ግምገማ ማሳየቱን የአሜሪካ ሚዲያዎች ዘግበዋል።
    • ይህንን ግምገማ የዋይት ሃውስ የፕሬስ ሴክሬታሪ ካሮሊን ሌቪት “ፍጹም የተሳሳተ” ብለውታል።
    • ዶናልድ ትራምፕ በኢራን ላይ የፈጸሙት ጥቃት የኒውክሌር ይዞታዎቿን ሙሉ በሙሉ ያወደመ ነው በሚለው አቋማቸው ጸንተዋል።
    • በእስራኤል እና ኢራን መካከል ያለው የተኩስ አቁም የጸና የሚመስል ሲሆን ሁለቱም ይህንኑ ዕውቅና ሰጥተዋል።
    • የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሁለቱም አገራት የተኩስ አቁም ስምምነት ጥሰዋል በሚል ኃይለቃል በመናገር ጣልቃ መግባታቸውን ተከትሎ መጽናቱም ተገልጿል።
    • የእስራኤል እና የኢራን መንግሥታት በቅርቡ በነበረው ጥቃት ሁለቱም ድል አድራጊነታቸውን አውጀዋል።
    • ትራምፕ በኔዘርላንድስ የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃል-ኪዳን ድርጅት (ኔቶ) ስብሰባን እየተካፈሉ ሲሆን፤ ዋነኛው አጀንዳው የጥምረቱ አባል አገራት ለመከላከያ የሚያደርጉት መዋጮ ላይ ያተኮረ ነው ተብሏል።
  4. የኢራን የኒውክሌር ይዞታዎች ጥቃት ላይ የሾለከውን የደህንነት ግምገማ የትራምፕ ልዩ መልዕክተኛ "ክህደት" አሉት

    የመካከለኛው ምስራቅ ልዩ መልዕክተኛ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን የኒውክሌር ይዞታዎች ጥቃት ላይ የአሜሪካ መከላከያ (ፔንታጎን) የደህንነት ግምገማ ሾልኮ መውጣቱን የትራምፕ የመካከለኛው ምስራቅ ልዩ መልዕክተኛ “የአገር ክህደት” ሲሉ ጠርተውታል።

    ፔንታጎን የአሜሪካ ጥቃት የኢራን ኒውክሌር ይዞታዎችን አላወደመም የሚለው ግምገማው በሚዲያዎች ሾልኮ መውጣቱን ተከትሎ ነው፤ ልዩ መልዕክተኛው ስቲቭ ዊትኮፍ ውግዘታቸውን ያሰሙት።

    “በጣም አሳፋሪ ነው፤ የአገር ክህደት ነው። ምርመራ ተካሂዶ ጥፋተኛው አካል ተጠያቂ ሊደረግ ይገባል” ሲሉ ለፎክስ የዜና ወኪል ተናግረዋል።

    ልዩ መልዕክተኛው አገራቸው በሶስቱ የኒውክሌር ማብላያ ይዞታዎች ላይ የፈጸመችውን ጥቃቶች ግምገማ ሪፖርቶች ማንበባቸውን ገልጸው “ሙሉ በሙሉ ስለመውደማቸው ምንም ጥርጥር” የለውም ብለዋል።

    የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ልዩ መልዕክተኛቸው ከፎክስ ጋር ያደረጉትን ቃለ ምልልስ በመቀነጫጨብ በትሩዝ ሶሻል ማህበራዊ ገጻቸው ላይ አጋርተዋል።

    “በፎርዶው [የኒውክሌር ማብላያ] ላይ 12 በንከር በስተር ቦምቦችን ጥለናል። የይዞታውን ጣሪያ ጥሶ እንዳለፈ እንዲሁም ሙሉ በሙሉ እንደወደመ ምንም ጥርጥር የለውም። እናም ግባችንን እንዳላሳካን እየወጡ ያሉ ሪፖርቶች እርባና ቢስ ናቸው” ሲሉ አጣጥለዋል።

  5. የአሜሪካ ጥቃት የኢራን ኒውክሌር ይዞታዎችን እንዳላወደመ የደህንነት ግምገማ አሳየ

    የፎርዶ የኒውክሌር ማብላያ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አሜሪካ በኢራን ላይ የፈጸመችው ጥቃት የኒውክሌር ማብላያ ይዞታዎችን እንዳላወደመ የአሜሪካ መከላከያ ማዕከል (ፔንታጎን) የደህንነት ግምገማ አሳየ።

    ቅድመ ግምገማው ጥቃቱ የኢራንን የኒውክሌር መርሃ ግብር ምናልባትም በወራት ወደኋላ ሊመልሰው እንደሚችል ነው ያሳየው።

    ኢራን ያበለጸገችው የዩራኒየም ክምችት አሜሪካ ቅዳሜ፣ ሰኔ 14/ 2017 ዓ፣ም በፈጸመችው ጥቃት አለመውደሙን የአገሪቱ የመከላከያ ደህንነት ኤጀንሲ ግምገማን የሚያውቁ ምንጮች ለቢቢሲ የአሜሪካ አጋር ሲቢኤስ ተናግረዋል።

    ዋይት ሃውስ በበኩሉ "ይህ ፍጹም የተሳሳተ" ግምገማ" በማይረባ የደህንንት ማህበረሰብ ሾልኮ የወጣ ነው" ሲል ውድቅ አድርጎታል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው የኢራን የኒውክሌር ይዞታዎች ሙሉ በሙሉ ወድመዋል በማለት በድጋሚ አጽንኦት ሰጥተው፤ "በታሪክ ውስጥ ስኬታማ ከሆኑ ወታደራዊ ጥቃቶች መካከል አንዱ የሆነውን ለማዋረድ" በሚዲያዎች የሚደረግ ሙከራ ሲሉ ከሰዋል።

  6. ኢራን ለእስራኤል ሲሰልሉ ነበር ያለቻቸውን ሦስት ሰዎች ሰቀለች

    የኢራን ፖሊስ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኢራን ለእስራኤል ሲሰልሉ ነበር ተብለው የተከሰሱ ሦስት ሰዎችን በስቅላት መቅጣቷን የአገሪቱ የፍትሕ ተቋማት የዜና ምንጭ አስታወቀ።

    ‘ሚዛን’ የተባለው የኢራን ፍትሕ ተቋማት የዜና ወኪል እንደዘገበው በስቅላት የተቀጡት ግለሰቦች በተጨማሪም በአገሪቱ ውስጥ ግድያዎችን ለመፈጸም የሚያስችሉ “ቁሳቁሶችን” በድብቅ ለማስገባት በመሞከር ተከስሰዋል።

    የዜና ወኪሉ በስቅላት የተቀጡት ሰዎች ስምን የዘረዘረ ሲሆን፣ እነሱም ኢድሪስ አሊ፣ አዛድ ሾጃይ እና ራሱል አሕማድ ራሱል ናቸው።

    ግለሰቦቹ እስራኤልን “የሚተባበር ድርጊት” በመፈጸም ተይዘው ነው ለስቅላት ላበቃቸው የፍርድ ሂደት የበቁት።

    እስራኤል በኢራን ላይ የከፈተችውን ጥቃት ተከትሎ ለ12 ቀናት በቆየው የሁለቱ አገራት ግጭት ወቅት የእስራኤል የሰላዮች እና ተባባሪዎቻቸው በኢራን ውስጥ የተለያዩ ተግባራት መፈጸማቸው ሲነገር ቆይቷል።

    ይህንንም ተከትሎ ኢራን ለቀናት በዘለቀው ግጭት ወቅት ከእስራኤል ጋር ግንኙነት አላቸው ተብለው የተከሰሱ 700 ሰዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ለኢራን መንግሥት ቅርበት ያለው ‘ኑር ኒውስ’ የተባለው መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

  7. ከትራምፕ ቁጣ በኋላ የእስራኤል-ኢራን የተኩስ አቁሙ የፀና ይመስላል

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ተኩስ አቁም መደረሱን ይፋ ያደረጉት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ወደ ኔቶ ስብሰባ ከመሄዳቸው በፊት

    የእስራኤልን ጥቃት ተከትሎ ለ12 ቀናት ከኢራን ጋር ሲካሄድ የነበረውን ድንበር ዘለል ግጭትን ለማስቆም የተኩስ አቁም ስምምነት መደረሱን ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ያስታወቁት ማክሰኞ ማለዳ ላይ ነው።

    ነገር ግን ከረፋድ ጀምሮ ሁለቱም አገራት ጥቃት እንደተፈጸመባቸው በመግለጽ አንዳቸው ሌላኛቸውን ሲከሱ እና የተኩስ አቁም ስምምነቱ አለመከበሩን ሲገልጹ ነበር።

    ለእስራኤል በማገዝ ዕሁድ ዕለት ከባድ የቦንብ ድብደባ በኢራን የኒውክሌር ተቋማት ላይ የፈጸመችው አሜሪካ እና ሰኞ ምሽት የተወሰኑ ሚሳዔሎች የተተኮሱባት ኳታር ያሳኩት እንደሆነ የተነገረለት የተኩስ አቁም ዕውን እየሆነ ይመስላል።

    ኢራን እና እስራኤል የተኩስ አቁሙን በመጣስ መካሰሳቸውን ተከትሎ በአገራቱ ላይ ቁጣቸውን የገለጹት ትራምፕ በተለይ በወዳጃቸው እስራኤል ላይ ጠንከር ያለ ቁጣ ከመሰንዘራቸው በተጨማሪ ከእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታኒኣሁ ጋር በስልክ ተነጋግረዋል።

    ከሁለቱ አገራት በኩል ለቀናት በዘለቀው ግጭት የመጨረሻ የነበሩት ጥቃቶች ሌሊት ላይ ኢራን ወደ እስራኤሏ ቤርሼባ የተሰነዘረው እና የሰው ሕይወት የጠፋበት ጥቃት ሲሆን፣ በእስራኤል በኩል ደግሞ በሰሜናዊ ኢራን ላይ ጥቃት ፈጽመዋል።

    የተኩስ አቁሙ በፕሬዝዳንት ትራምፕ ይፋ ከሆነ በኋላ ኢራን እና እስራኤል ጥቃቱ መቀጠሉን እና አጸፋ እንደሚመልሱ ከገለጹ በኋላ ግጭቱ እንደማይቆም ተሰግቶ የነበረ ቢሆንም፣ ከሰዓት በኋላ መጠቃቃቱ ጋብ ብሎ ተኩስ አቁሙ የያዘ መስሏል።

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ የጦር አውሮፕላኖቻቸው ጥቃት እንዲያቆሙ ያዘዙ ሲሆን፣ የኢራኑ ፕሬዝዳን ማሱድ ፔዜሽኪያን እስራኤል ጥቃቷን እስካቆመች ድረስ አገራቸው ተኩስ አቁሙን እንደምታከብር አሳውቀዋል።

  8. የመንግሥታቱ ድርጅት እስራኤል በእርስ ቤት ላይ የፈጸመችው ጥቃት የዓለም አቀፍ ሕግ ጥሰት ነው አለ

    ኤቪን እስር ቤት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ኤቪን እስር ቤት

    እስራኤል ትናንት ሰኞ ኢራን ውስጥ የሚገኘውን ኤቪን የተባለው እስር ቤት ላይ የፈጸመችው ጥቃት በዓለም አቀፍ ሕግ ላይ የተፈጸመ “ከባድ ጥሰት ነው” ሲል የመንግሥታቱ ድርጅት ወቀሰ።

    ኢራን እንዳለችው እስራኤል በእስር ቤቱ እና በተያያዥ የእስር ቤቱን ከፍሎች ላይ በፈጸመችው ጥቃት ጉዳት አድርሳለች።

    የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብአዊ መብቶች ጽህፈት ቤት ጥቃቱን አስመልክቶ በሰነዘረው አስተያየት ድርጊቱ የሕግ ጥሰት መሆኑን አመልክቷል።

    "ኤቪን እስር ቤት ወታደራዊ ተቋም አይደለም፤ ስለዚህም እስር ቤቱን ዒላማ ማድረግ የዓለም አቀፍ ሕግ ጥሰት ነው” ሲሉ የጽህፈት ቤቱ ቃል አቀባይ ታሚን አል-ኺታን ጄኔቫ ውስጥ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    ኤቪን እስር ቤት የኢራን የፖለቲካ ተቃዋሚዎችን፣ የሰብአዊ መብት ተከራካሪዎችን እና ጋዜጠኞችን ጨምሮ በሺዎች የሚቆጠሩ እስረኞች የሚገኙበት ነው።

    በኢራን መንግሥት ቴሌቪዥን የተጠቀሱት የአገሪቱ ፍትህ መሥሪያ ቤት ቃል አቀባይ አስግሃር ጃሃንጊር እንደተናገሩት በእስር ቤቱ ላይ በተፈጸመው ጥቃት ቢያንስ አንድ ሰው ተገድሏል።

  9. እስራኤል የተኩስ አቁሙን እስካልጣሰች ድረስ ኢራን እንደምታከብር ፕሬዝዳንቷ ተናገሩ

    ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን

    የኢራኑ ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን በአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ይፋ የተደረገውን የተኩስ አቁም ስምምነት አገራቸው እንደምታከብር ተናገሩ።

    ፕሬዝዳንቱ ኢራን ከእስራኤል ጋር የተደረሰውን ተኩስ አቁም የምታከብረው እስራኤልም ተገዢ ስትሆን እንደሆነ መናገራቸውን መንግሥታዊው የእስላማዊ ሪፐብሊክ ዜና ወኪል - ኢርና ዘግቧል።

    ፕሬዝዳንት ፔዜሽኪያን ከማሊዢያው ጠቅላይ ሚኒስትር አንዋር ኢብራሒም ጋር በስልክ በተወያዩበት ጊዜ፤ እስራኤል የተኩስ አቁሙን “የማትጥስ ከሆነ፣ ኢራን አትጥስም” በማለት ተኩስ አቁሙ የሚጸናው ሁለቱም አገራት ሲያከብሩት መሆኑን አመልክተዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ጨምረውም "አንዳንድ ችግሮች እና ቅሬታዎች ቢኖሩም ኢራናውያን በጠላት የሚፈጸምን ወረራ በአንድነት እስከ መጨረሻው እንደሚጋፈጡ በድጋሚ አሳይተዋል” ብለዋል።

  10. የተኩስ አቁም እና በኢራን እስራኤል ግጭት ምን ያህል ሰዎች ሞቱ?

    በኢራን ሚሳኤል ቤርሼባ ውስጥ የደረሰው ጉዳት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በኢራን ሚሳኤል ቤርሼባ ውስጥ የደረሰው ጉዳት

    ዛሬ ማከሰኞ ማለዳ ተግባራዊ የሆነ በእስራኤል እና በኢራን መካከል የተኩስ ማቆም ይፋ ሆኗል። ነገር ግን ሁለቱም ወገኖች የተኩስ አቁሙን በመጣስ እየተካሰሱ ነው። ዛሬ ጠዋት ተኩስ አቁም መደረጉ መገለጹን ጨምሮ አስካሁን ምን ተከሰተ?

    * ዶናልድ ትራምፕ በአሜሪካ እና በኳታር አማካኝነት የተደረሰውን የተኩስ አቁም በመጣስ በእስራኤል እና በኢራን ላይ ቁጣቸውን ገለጹ

    * ትራምፕ ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት ሁለቱም አገራት "የሚያደርጉትን. . . ነገር አያውቁም” ሲሉ ቁጣ በተቀላቀለበት እና መደበኛ ባልሆነ አገላለጽ ወቅሰዋል

    * ቀደም ሲል በኢራን የሥርዓት ለውጥ እንዲደረግ ሃሳብ ሲያንሸራሽሩ የቆዩት ትራምፕ፣ ዛሬ ይህንን ሃሳብ እንደማይደግፉት ተናግረዋል

    * እስራአል በዛሬው ዕለት ከቴህራን አቅራቢያ ያለ የራዳር ማዕከልን መምታቷን እና ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ ከፕሬዝዳንት ትራምፕ ጋር በስልክ ካወሩ በኋላ የጦር አውሮፕላኖቹ እንዲመለሱ መደረጋቸው ተገልጿል

    * የጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ ጽህፈት ቤት ኢራን በሚሳዔል ጥቃቶች የተኩስ አቁሙን ሦስት ጊዜ ጥሳላች በማለት ሲከስ፣ ኢራን አስተባብላለች

    * ይህ በእንዲህ እንዳለ ለ12 ቀናት በተካሄደው የእስራኤል ጥቃት 606 ሰዎች መገደላቸውን የኢራን ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል፤ ሌሎች ምንጮች ግን የሞቱት ሰዎች በሁለት እጥፍ ይጨምራል ብለዋል

    * የዛሬው ተኩስ አቁም ተግባራዊ ከመሆኑ ቀደም ብሎ ኢራን ቤርሼባ ላይ በፈጸመችው ጥቃት አራት እስራኤላውያን ሲገደሉ፣ በኢራን ጥቃት በአጠቃላይ 28 ሰዎች ተገድለዋል።

  11. ከተኩስ አቁሙ በኋላ የኢራን እና የእስራኤል ከተሞች ዛሬ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት በኢራን እና እስራኤል መካከል ሲካሄድ የሰነበተውን ጥቃት ለማስቆም የሚያስችል የተኩስ አቁም ከማክሰኞ ማለዳ ጀምሮ ተግባራዊ እንደሆነ አስታውቀዋል።

    ነገር ግን ሁለቱም አገራት አልዳቸው ሌላቸውን ጥቃቱን በመቀጠል ቢከሱም፣ እንደሰሞኑ ተከታታይ የአየር እና የሚሳዔል ጥቃት ስለመፈጸሙ በይፋ የተነገረ ነገር የለም።

    የሁለቱን አገራት ዜጎች ተኩስ አቁሙ የሰላም ተስፋን ፈጥሮላቸዋል። ከግጭቱ ጋብ ማለት በኋላ የሁለቱ አገራት ከተሞችን የሚያሳዩ ምሥሎች እነሆ. . .

    ቴህራን፣ ኢራን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ቴህራን፣ ኢራን
    ቴህራን፣ ኢራን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ቴህራን፣ ኢራን
    ቴል አቪቭ፣ እስራኤል

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ቴል አቪቭ፣ እስራኤል
    ቴል አቪቭ፣ እስራኤል

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ቴል አቪቭ፣ እስራኤል
  12. የኢራን መገናኛ ብዙኃን በሰሜናዊ ኢራን ፍንዳታዎች በመሰማታቸው ‘ተኩስ አቁሙ ተጥሷል’ እያሉ ነው

    በኢራን እና በእስራኤል መካከል የተኩስ አቁም መደረጉ ቢነገርም በሰሜናዊ ኢራን ማዛንዳራን ግዛት ውስጥ ፍንዳታዎች መሰማታቸውን ነዋሪዎች ተናግረዋል።

    ለኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጓድ ቅርብ የሆነው ‘ፋርስ’ የተባለው የዜና ወኪል እንዳለው ከዋና ከተማዋ ቴህራን በስተሰሜን ማዛንዳራን ግዛት ውስጥ በምትገኘው ባቦልሳር ከተማ ውስጥ ፍንዳታዎች ተሰምተዋል።

    ይህ እበእንዲህ እንዳለ ከፊል መንግሥታዊ የሆኑት ‘መህር’ እና ‘ኢስና’ የተባሉት የዜና ወኪሎች በሰሜናዊ ግዛት ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ ስፍራዎች ፍንዳታዎች መከሰታቸውን እና የአየር መከላከያ መሳሪያዎች ተኩስ መሳማቱን በመጥቀስ የተኩስ አቁሙ “ተጥሷል” ብለዋል።

    በተጨማሪም የኢራን መንግሥት ቴሌቪዥን ፍንዳታዎች መከሰታቸውን እና የግዛቲቱን አስተዳዳሪ ቃል አቀባይ ክስተቱን በተመለከተ ዝርዝር ጉዳዮች ገና አለመታወቃቸውን መናጋራቸው ገልጿል።

  13. ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት እንዳትፈጽም አስጠነቀቁ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በማኅበራዊ ትስስር መድረካቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸም የለባትም በማለት ማስጠንቀቂያ አስተላለፉ።

    ፕሬዝዳንቱ ትሩዝ በተባለው የራሳቸው ማኅበራዊ ሚዲያ መድረክ ላይ "እስራኤል፤ እነዚያን ቦምቦች አትጣይ። በጥቃቱ የምትቀጥይ ከሆነ ከፍተኛ ጥሰት ነው። [የጦር አውሮፕላን] አብራሪዎችሽን አሁኑኑ ወደ ቤታቸው መልሺ!" ብለዋል።

    ይህ የፕሬዝዳንቱ ማስጠንቀቂያ የመጣው ከዛሬ ጠዋት ጀምሮ ተግባራዊ የሚሆን የተኩስ አቁም በኢራን እና በእስራኤል መካከል መደረጉን ካስታወቁ በኋላ ነው። እስራኤል በትራምፕ ሃሳብ መስማማቷን ስታሳውቅ፣ ኢራን ደግሞ ጥቃቱን የምታቆመው እስራኤል ካቆመች ብቻ ነው ብላለች።

    ነገር ግን ረፋድ ላይ የእስራኤል ጦር ሠራዊት ከኢራን የተወነጨፈ ሚሳዔል አክሽፊያለሁ ቢልም ኢራን ግን ምንም ዓይነት ጥቃት አለመዘንዘሯን አስታውቃለች።

    ዶናልድ ትራምፕ ቆየት ብለው ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት ሁለቱም አገራት የተኩስ አቁሙን ጥሰዋል በሚል ከስሰዋቸዋል።

    "ሆን ብለው ማድረጋቸውን እርግጠኛ አይደለሁም" ያሉት ፕሬዝዳንቱ "ዛሬ ጠዋት የእስራኤልን ሁኔታ አልወደድኩትም፤ ይህንንም ማስቆም እችል እንደሆነ አያለሁ።”

    ፕሬዝዳንቱ ጨምረውም ኢራን "ወደፊት ፈጽሞ ኒውክሌር መሳሪያን አትገነባም” በማለት በኢራን ሁኔታም ደስተኛ አለመሆናቸውን አመልክተዋል።

  14. ኢራን በአሜሪካ ወታደራዊ ጦር ሠፈር ላይ የተፈጸመው ጥቃት “ከኳታር ጋር የሚያገናኘው የለም” አለች

    የኢራን ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ሰኞ ዕለት በአሜሪካ በሚተዳደረው አል ኡዲድ የጦር ሠፈር ላይ የተፈጸመው ጥቃት ከኳታር ጋር “የሚያገናኘው የለም” አሉ።

    የጦር ሰፈሩ የሚገኘው ኳታር ቢሆንም ቃል አቀባዩ ኢስማኤል ባጋህኢ ግን የኢራን እርምጃ “ራስን የመካለከል ነው” ብለዋል።

    ባጋህኢ በኤክስ ገጻቸው ላይ በለጠፉት ጽሑፍ "ኢራን ኳታርን እና ሌሎች ጎረቤት አገራትን በተመለከተ ለመልካም ጉርብትና ፖሊሲዋ ሙሉ በሙሉ ቁርጠኛ ነች" ብለዋል።

    "የአሜሪካ/እስራኤል የወንጀል ጥቃቶች እና በኢራን ላይ ያላቸው የተሳሳቱ ፖሊሲዎች በእኛ እና በቀጠናው ወንድማማች አገሮች መካከል መለያየት መፍጠር የለባቸውም" ብለዋል።

    የአሜሪካ የጦር ሠፈሮች በመካከለኛው ምሦራቅ
  15. ኳታር ለተባበሩት መንግሥታት በጻፋቸው ደብዳቤ ኢራን ሰኞ ዕለት የፈጸመችውን ጥቃት ኮነነች

    ኳታር ኢራን ሰኞ ዕለት በአሜሪካ አል ኡዲድ የጦር ሠፈር ላይ የፈጸመችውን ጥቃት በመኮነን ለተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሃፊ ደብዳቤ ጻፈች።

    የኳታር ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለቻ ላይ ደብዳቤው ጥቃቱ የኳታር "ሉዓላዊነት እና ግዛታዊ አንድነት" ላይ የተፈጸመ "እጅግ አደገኛ እና ግልጽ ጥሰት" መሆኑን ገልጿል።

    ደብዳቤው የኢራን አብዮታዊ ዘብ የሚሳኤል ጥቃት "ለአካባቢው ሰላም እና ደህንነት ቀጥተኛ ስጋት" መደቀኑንም ያብራራል።

    "የኳታር መንግሥት ከዚህ ግልጽ ጥቃት ተፈጥሮ እና መጠን ጋር ተመጣጣኝ በሆነ መልኩ በዓለም አቀፍ ሕግ መሠረት ምላሽ የመስጠት መብቱ የተጠበቀ መሆኑን አፅንዖት ሰጥቷል" ሲል መግለጫው አክሎ ገልጿል።

    የኳታር መንግሥት የኢራን አምባሳደርን ጠርቶ ማናገሩንም አስታውቋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሩ ሰኞ ዕለት በዩናይትድ ስቴትስ ጦር ሰፈር ላይ የተፈፀመውን የሚሳኤል ጥቃትን ሙሉ በሙሉ ማክሸፏን ገልጿል።

  16. የእስራኤል መከላከያ ኢታማዦር ሹም ለኢራን “በኃይል ምላሽ ይሰጣል” አሉ

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል ኢታማዦር ሹም

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል ኢታማዦር ሹም ኢራን “ለፈጸመችው ከባድ ጥሰት” መከላከያ “በኃይል ምላሽ ይሰጣል” ሲሉ ተናገሩ።

    የኢራን መከላከያ ኃይል ኢታማዦር ሹም አብዶልራሂም ሙሳቪ ግን ወደ እስራኤል ሚሳዔል አስወንጭፈዋል መባሉን አስተባብለዋል።

    የእስራኤል መከላከያ አዛዥ የሆኑት ኢያል ዛሚር በመከላከያ የኤክስ ገጽ ላይ “የኢራን መንግሥት የተኩስ አቁሙን በመጣስ ለፈጸመው ከባድ ጥሰት በኃይል ምላሽ እንሰጣለን” ብለዋል።

  17. የኢራን ከፍተኛ የደህንነት ምክር ቤት 'ተጨማሪ ጥቃት የሚሰነዘር ከሆነ ምላሽ እንደሚሰጥ' አስጠነቀቀ

    የኢራን ከፍተኛ ብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት በእስራኤል እና በ"አሸባሪ ደጋፊዎቿ” ላይ “ጦርነቱን ለማስቆም” ሲል መግለጫ አውጥቷል።

    ምክር ቤቱ “ለማንኛውም ተጨማሪ ጥቃት"፤ "ቆራጥ፣ ጽኑ እና ወቅታዊ ምላሽ እንደሚሰጥ” አስጠንቅቋል።

    ምክር ቤቱ በመግለጫው የኢራንን ሕዝብ ስላለው "መረዳት፣ ፅናት እና አንድነት" አወድሷል።

    አክሎም “የጠላት ሽንፈት” በኢራናውያን "ፅኑ ቁርጠኝነት፣ ስልታዊ ትዕግስት እና ውርደትን ወይም የአንድ ወገን ማመቻመችን ካለመቀበል" የመጣ ነው ብሏል።

    መግለጫው ኢራንን እና ሠራዊቷን በኢራን ላይ ለሚሰነዘረው ጥቃት "ወሳኝ እና የተሰላ" አጸፋ በመስጠታቸው አመስግኗል።

  18. ኢራን ወደ እስራኤል ሚሳዔል አስወንጭፋለች መባሉን አስተባበለች

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን ኢራን የእስራኤልን ውንጀላን ማስተባበሏን ዘገበ።

    ኢራን ወደ እስራኤል ሚሳዔል አለማሰወንጨፏን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

    በሁለቱ አገራት መካከል የተኩስ አቁም መጀመሩ የተገለፀው ከጥቂት ሰዓታት በፊት ነበር።

    ፕሬዚደንት ትራምፕ በሁለቱ አገራት መካከል የተኩስ አቁም ስምምነቱ መጀመሩን በገለፁበት የማኅበራዊ ሚዲያ ልጥፋቸው "እንዳይጥሱት" ተማጽነዋል።

  19. እስራኤል ኢራንን የተኩስ አቁም ስምምነቱን በመጣስ ወነጀለች

    የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር እስራኤል ካትዝ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር እስራኤል ካትዝ ኢራንን የተኩስ አቁም ስምምነቱን በመጣስ ወነጀሉ።

    አክለውም የእስራኤል መከላከያ ኃይል “ኢራን የተኩስ አቁሙን በመጣሷ በቴህራን ማዕከላዊ ክፍል የሚገኙ ዒላማዎች ላይ ከበድ ያለ ጥቃት በመፈፀም ምላሽ እንዲሰጥ” ማዘዛቸውን ተናግረዋል።

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል ከእስራኤል የተተኮሱ ሚሳዔሎችን የአየር መቃወሚያው ማምከኑን ተናግሮ ነበር።

  20. እስራኤል ከኢራን ጋር የተኩስ አቁም ለማድረግ ስትስማማ የነዳጅ ዋጋ ቀነሰ

    የነዳጅ ጫኝ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    እስራኤል ከኢራን ጋር ለሁለት ሳምንታት ከቆየ ግጭት በኋላ የተኩስ አቁም ስምምነት ለማድረግ ከተስማማች በኋላ የነዳጅ ዋጋ በ5 በመቶ ገደማ ቀንሷል።

    ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት በበርሜል ወደ 68 ዶላር ዝቅ ብሏል።

    ይህም እስራኤል ሰኔ 13 በኢራን የኒውክሌር ተቋማት ላይ ሚሳይሎችን ከማሰወንጨፏ በፊት ከነበረበት በታች ነው።

    በቅርብ ቀናት ውስጥ ኢራን የነዳጅ እና ጋዝ ዋና የመርከብ መስመር የሆነውን የሆርሙዝ ባህር ሰርጥን በመዝጋት የዓለም አቀፍ አቅርቦቶችን ልታስተጓጉል ትችላለች የሚል ስጋት እየጨመረ በመምጣቱ የዋጋ ጭማሪ ተስተውሎ ነበር።

    የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የተኩስ አቁም “አሁን ተግባራዊ ሆኗል” ሲሉ የእስያ የአክሲዮን ገበያዎች ተነቃቅተዋል።

    ከዚያ በኋላ እስራኤል በተኩስ አቁሙ መስማማቷን በይፋ አረጋግጣለች።

    የሚሳኤል ጥቃቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ የነዳጅ ዋጋ በበርሚል እስከ 81 ዶላር ደርሶ ነበር።