የእስራኤል እና ኢራን ግጭት “መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል” ተመድ

ስምንተኛ ቀኑን የያዘው የእስራኤል እና ኢራን ግጭት “መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል” ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አሳሰቡ።ዋና ጸሐፊው በአገራቱ መካከል ያለው ግጭት መቀጠል አለምን ወደ ቀውስ የሚከት ነው ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

  • እስራኤል እና ኢራን ግጭት "መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል" ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አሳሰቡ
  • ኢራን በእስራኤል ያልተጠበቀ ጥቃት የተፈጸመባት "ከአሜሪካ ጋር የኒውክሌር አቅምን አስመልክቶ ተስፋ ሰጪ ዲፕሎማሲያዊ ሂደት ላይ በነበረችበት ወቅት" መሆኑን አስታወቀች።
  • የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ከእስራኤል ጋር ያለውን ግጭት ለማስቆም ፈረንሳይን ጨምሮ አውሮፓውያኑ አገራት ለኢራን የዲፕሎማሲ ፕሮፖዛል እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል።
  • ዶናልድ ትራምፕ በሚቀጥሉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ ዩናይትድ ስቴትስ በኢራን እና በእስራኤል ግጭት ውስጥ በቀጥታ ጣልቃ መግባት አለመግባቷን ይወስናሉ- ዋይት ሐውስ
  • ትራምፕ በመካከለኛው ምሥራቅ ግጭት ላይ ለመወሰን ሁለት ሳምንት ጊዜ ሲሰጡ ዩኬ እና የአውሮፓ ኅብረት ከኢራን ጋር ሊነጋገሩ ነው
  • የኢራን ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ለቢቢሲ አሜሪካ በግጭቱ ውስጥ የምትሳተፍ ከሆነ ቀጠናው "ሲኦል" ይሆናል ሲሉ ተናግረው ነበር
  • ኢራን በትናንትናው ዕለት በፈጸመችው የሚሳኤል ጥቃት ከሆስፒታል አቅራቢያ ያለ ወታደራዊ ስፍራ ማነጣጠሩን ገልጽላች
  • ኢራን ባስወነጨፈቻቸው ሚሳኤሎች በደቡባዊ እስራኤል ባርሺባ ከተማ የሚገኘውና በእስራኤል ትልቁ ከሚባሉት አንዱ ሶሮካ ሆስፒታል መመታቱን እስራኤል አስታወቀች።
  • የተመድ የጸጥታው ምክር ቤት በእስራኤል እና ኢራን ግጭት አስቸኳይ ስብሰባ ሊያካሂድ ነው
  • የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራንን ለማጥቃት ዕቅድ ቢያጸድቁም ነገር ግን የመጨረሻ ውሳኔ ላይ አለመድረሳቸው ተዘገበ።
  • አሜሪካ የጦር ጄቶችን ጨምሮ የጦር መሳሪያዎችን ወደ መካከለኛው ምስራቅ እያንቀሳቀሰች ነው
  • ፑቲን በኻሜኒ ላይ የታቀደውን ግድያ አስመልክቶ "በፍጹም በዚህ ጉዳይ ላይ መወያየት አልፈልግም" አሉ
  • የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ "ኢራናውያን እጃቸውን የሚሰጡ ሕዝቦች አይደለም" ሲሉ ተናገሩ።
  • እስራኤል በኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት እስከ እሁድ ምሽት ድረስ 224 ሰዎች ሲገደሉ 1 ሺህ 277 መጎዳታቸውን ኢራን አስታውቃለች። እስራኤል በበኩሏ በጥቃቶቹ 20 ሰዎች ተገድለውብኛል ብላለች።
  • ትራምፕ ኢራን ላይ ጥቃት መፈጸምን በተመለከተ "ላደርገው ወይም ላላደርገው እችላለሁ" አሉ
  • ፎርዶ ኢራን ካሏት ሁለት ወሳኝ የኒውክሌር ማብላያ ጣቢያዎች መካከል አንዱ ሲሆን የእስራኤል መከላከያ ኃይል የአየር ጥቃት ቢያደርስበትም ጉዳት ሊደርስበት አልቻለም።

የቀጥታ ሽፋን

  1. እስራኤል በኢራን በፈጸመችው ጥቃት የተገደሉ የጦር አዛዦች እና የኒውክሌር ሳይንቲስቶች እነማን ናቸው?

    እስራኤል ሐሙስ ለአርብ አጥቢያ በመላው ኢራን ባሉ የኒውክሌር ይዞታዎች፣ ወታደራዊ ስፍራዎች እና የመኖሪያ ስፍራዎች ላይ በፈጸመቻቸው በርካታ ጥቃቶች ከፍተኛ የጦር አዛዦች እና ዘጠኝ የኒውክሌር ሳይንቲስቶች ተገድለዋል።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ አገራቸው አርብ ማለዳ የፈጸመችው ጥቃት የኢራን የኒውክሌር መሰረተ ልማት እና የባለስቲክ ሚሳኤል ፋብሪካዎችን ለመጉዳት ያለመ ነው ብለዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ራይዚንግ ላየን ኦፐሬሽን' [ የሚያንሰራራ አንበሳ ዘመቻ] ሲሉ በጠሩት ጥቃት ከተገደሉት መካከል የኢራን አብዮታዊ ዘብ ኃላፊ እና የአገሪቱ ጦር ኃይሎች ኢታማዦር ሹም ይገኙበታል።

    ህጻናትን ጨምሮ በርካታ ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸው ተዘግቧል።

  2. ለሁለተኛ ቀን የቀጠለው የእስራኤል እና የኢራን ፍጥጫ

    እስራኤል የፈጸመችውን ጥቃት ተከትሎ ኢራን አጸፋዊ ሚሳኤሎችን ያስወነጨፈችበት የሁለቱ አገራት ፍጥጫ ሁለተኛ ቀኑን ይዟል።

    • እስራኤል በድጋሚ አርብ ምሽት በፈጸመችው ጥቃት በርካታ ኢላማዎች መምታቷን አስታውቃለች።
    • በቴህራን የመኖሪያ ህንጻ ላይ በተፈጸመ ጥቃት 20 ህጻናትን ጨምሮ 60 ሰዎች መሞታቸውን የኢራን መንግሥታዊ ሚዲያ ዘግቧል።
    • በኢራን አጸፋዊ የሚሳኤል ጥቃቶች ሶስት ሰዎች ሲገደሉ በርካቶች መቁሰላቸውን ባለስልጣናት ተናግረዋል።
    • አሜሪካ ወደ ግጭቱ እንድትገባ ከተደረገች ሁኔታዎች በበለጠ ሊያገረሹ ይችላሉ ተብሏል።
    • ኢራን ሚሳኤሎችን የምታስወነጭፍ ከሆነ መዲናዋ "ቴህራን ትቃጠላለች" ሲሉ የእስራኤል የመከላከያ ሚኒስትር እስራኤል ካትዝ አስጠንቅዋል።
    • የእስራኤል መከላከያ ኃይል ዘጠኝ የኢራን የኒውክሌር ሳይንቲስቶችን እና ባለሙያዎችን ገድያለሁ አለ።ጦሩ ሐሙስ ለአርብ አጥቢያ በፈጸመው ተከታታይ ጥቃት የገደላቸው የኒውክሌር ሳይንቲስቶች ስድስት ናቸው ብሎ ነበር።
    • ኢራን በእስራኤል ላይ እየወሰደች ያለችውን አጸፋዊ እርምጃ ለማስቆም አሜሪካ፣ ፈረንሳይ እና ዩናይትድ ኪንግደም እስራኤልን የሚያግዙ ከሆነ በቀጣናው የሚገኙ የጦር ሰፈሮቻቸውን ኢላማ እንደምታደርግ ማስጠንቀቋን የኢራን መንግሥታዊ ሚዲያ ዘግቧል።
  3. የእስራኤል ጦር ዘጠኝ የኢራን የኒውክሌር ሳይንቲስቶችን መግደሉን አስታወቀ

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል ዘጠኝ የኢራን የኒውክሌር ሳይንቲስቶችን እና ባለሙያዎችን ገድያለሁ አለ።

    ጦሩ ሐሙስ ለአርብ አጥቢያ በፈጸመው ተከታታይ ጥቃት የገደላቸው የኒውክሌር ሳይንቲስቶች ስድስት ናቸው ብሎ ነበር ።

    አሁን እስራኤል በዚህ ጥቃት የገደለቻቸው ዘጠኝ መሆናቸውን አስታውቃለች።

    ከተገደሉት መካከል የኒውክሌር ሳይንቲስቱ ፍሬይዱን አባሲ አንዱ ሲሆኑ በአውሮፓውያኑ 2011 እስከ 2013 ድረስ የአገሪቱ የአቶሚክ ኢነርጂ ድርጅት ኃላፊ ነበሩ።

    ፍሬይዱን አባሲ ለኢራን የኒውክሌር ማበልጸግ የአንበሳውን ድርሻ እንደተጫወቱ ይነገርላቸዋል።

    ከሳቸው በተጨማሪ በቴህራን የሚገኘው የእስላሚክ አዛድ ዩኒቨርስቲ ፕሬዚዳንትመህዲ ቴህራንቺ፣የሻሂድ በህሽቲ ዩኒቨርስቲ የኒውክሌር ኢንጂነሪንግ ኃላፊአብዶልሃሚድ ሚኖሸር፣ በዚሁ ዩኒቨርስቲ የኒውክሌር ኢንጂነርግ ፕሮፌሰር አህመድ ረዛ ዞልፋጋሪ እና በተመሳሳይ ዩኒቨርስቲ የኒውክሌር ፕሮፌሰር የሆኑት አሚርሆሴን ፈቂ ተጠቅሰዋል።

    በተጨማሪ የእስራኤል ወታደራዊ ባለስልጣን በጥቃቶቹ የኢስፋን እና ናታንዝ የኒውክሌር ጣቢያዎች ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው ሮይተርስ ዘግቧል።

    ባለስልጣኑ በኢራን ከ150 በላይ ኢላማዎች ጥቃት እንደተፈጸመባቸው ሮይተርስ አስፍሯል። ኢራን ወደ እስራኤል ያስወነጨፈቻቸው በርካቶቹ ሰው አልባ አውሮፕላኖች (ድሮች) እና ሚሳኤሎች ከሽፈዋል ሲሉ ባለስልጣኑ መናገራቸው ሰፍሯል።

  4. ሚሳኤሎች መወንጨፍ ካላቆሙ “ቴህራን ትቃጠላለች” ሲሉ የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር አስጠነቀቁ

    ኢራን ሚሳኤል ማስወንጨፏን ከቀጠለች መዲናዋ “ቴህራን” ትቃጠላለች ሲሉ የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር እስራኤል ካትዝ አስጠነቀቁ።

    ሚኒስትሩ ከወታደራዊ ባለስልጣናት ጋር ባደረጉት ግምገማ ላይ በሰጡት አስተያየት “የኢራኑ አምባገነን የኢራን ዜጎችን ወደ ታጋችነት እየቀየረ ነው። በተለይም የቴህራን ነዋሪዎች በእስራኤል ሲቪሎች ላይ ለደረሰው ጥቃት ከፍተኛ ዋጋ የሚከፍሉበት እውነታ እየፈጠረ ነው” ብለዋል።

  5. ኢራን፤ አሜሪካ፣ ፈረንሳይ እና ዩኬ እስራኤልን የሚረዱ ከሆነ አጸፋውን እንደምትመልስ አስጠነቀቀች

    ኢራን በእስራኤል ላይ እየወሰደች ያለችን አጸፋዊ እርምጃ ለማስቆም አሜሪካ፣ ፈረንሳይ እና ዩናይትድ ኪንግደም እስራኤልን የሚረዱ ከሆነ ምላሹን እንደምትሰጥ ማስጠንቀቋን የኢራን መንግሥታዊ ሚዲያ ዘግቧል።

    ሶስቱ አገራት ለእስራኤል ድጋፋቸውን ከሰጡ ኢራን በቀጣናው የሚገኙ የጦር ሰፈሮቻቸውን እና መርከቦችን ኢላማ እንደምታደርግ ዘገባዎች ወጥተዋል።

  6. ኢራን አሜሪካን ኢላማ ካደረገች መዘዙ እንደሚከፋ የአሜሪካ ባለስልጣን አስጠነቀቀቁ

    እስራኤል በኢራን ላይ የፈጸመችውን ጥቃት በተመለከተ ከጥቃቱ በፊት አሜሪካ “ምክር ተጠይቃ” በምላሹ “ራሷን ለመከላከል መሰረታዊ ነው” የሚል ምላሽ እንደተሰጣት የአሜሪካ ባለስልጣን ተናገሩ።

    “አሜሪካ ስለ ጥቃቱ ቀድሞ ቢነገራትም በነዚህ ጥቃቶች ላይ ወታደራዊ ተሳትፎ አልነበራትም” ሲሉ የአገሪቱ የአለም አቀፍ ድርጅት ጉዳዮች ቢሮ ከፍተኛ ባለስልጣን ማኮይ ፒት ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት ተናግረዋል።

    "ዋነኛው ቅድሚያ የምንሰጠው በቀጣናው ውስጥ ያሉ የአሜሪካ ዜጎች፣ ሰራተኞች እና ኃይሎችን ጥበቃ ነው።" ብለዋል

    ኢራን በቀጣናው ያሉ የአሜሪካ ዜጎች፣ የጦር ሰፈሮችን ወይም መሰረተ ልማቶችን ዒላማ ካደረገች “የሚከተላት መዘዝ አስከፊ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።

    የአሜሪካ አቋም ኢራን ስምምነት ማድረግ አለባት የሚል እንደሆኑ ገልጸው አገራቸው “ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ” ትሻለች ብለዋል።

    “የኢራን አመራሮች በዚህ ወቅት መደራደራቸው ብልህነት ነው” ብለዋል።

  7. የኢራን እና የእስራኤል ግጭት ቢገፋ ምን ሊከሰት ይችላል?

    በእስራኤል እና በኢራን መካከል ያለው ግጭት አሁን ላይ በሁለቱ አገራት መካከል የተገደበ ይመስላል፤ ነገር ግን ሁለቱ አገራት ግጭት እንዲያቆሙ የሚቀርበውን ጥሪ አንሰማም ቢሉስ? ግጭቱ ቢባባስ እና ቢስፋፋስ ምን አስከፊ ሁኔታ ሊከሰት ይችላል?

    የሚከተሉት ሊፈጠሩ የሚችሉ አስከፊ ሁኔታዎች ናቸው።

    አሜሪካ በግጭቱ ውስጥ ትገባለች

    ምንም እንኳን አሜሪካ ብታስተባብልም ኢራን የአሜሪካ ኃይሎች ግጭቱን መደገፋቸውንና ቢያንስ ለእስራኤል ጥቃት ስልታዊ ድጋፍ እንደሚያደርጉ በግልጽ ታምናለች።

    በመሆኑም ኢራን በመካከለኛው ምሥራቅ ባሉ የአሜሪካ ኢላማዎች ላይ ጥቃት ልትሰነዝር ትችላለች። አሜሪካ ኢራቅ ውስጥ የልዩ ኃይል ካምፖች፣ በባሕረ ሰላጤው አገራት ደግሞ ወታደራዊ ሰፈሮች እና በቀጠናው የዲፕሎማሲያዊ ተልዕኮዎች አሏት።

    በኢራን የሚደገፉት ሐማስ እና ሄዝቦላህ ብዙ የተዳከሙ ቢሆንም በኢራቅ የሚገኙት ደጋፊ ሚሊሻዎቻቸው ግን አሁንም ታጥቀውና አቅማቸውን አጠናክረው ነው የሚገኙት።

    የባሕረ ሰላጤው አገራት ወደ ግጭቱ ሊሳቡ ይችላሉ

    ኢራን አስተማማኝ መከላከያ ባለው የእስራኤል ጦር እና ሌሎች ኢላማዎች ላይ ጉዳት ማድረስ ካልቻለች፣በተለይ ጠላቶቿን ለዓመታት ይደግፋሉ በምትላቸው የባሕረ ሰላጤው አገራት ላይ የሚሳኤል ጥቃት ልትሰነዝር ትችላለች።

    እነዚህ አገራት የአሜሪካ አየር ኃይል ሰፈር የሚገኝባቸው ናቸው።በመሆኑም የባሕረ ሰላጤው አገራት ጥቃት ከደረሰባቸው ራሳቸውን ለመከላከል የአሜሪካ እና የእስራኤል የጦር አውሮፕላኖችን ድጋፍ ሊጠይቁ ይችላሉ።

    የኢራን አገዛዝ ሊወድቅ ይችላል፤ ይህም ክፍተት ይፈጥራል

    እስራኤል የኢራንን እስላማዊ አብዮት ጥበቃ አገዛዝ የማፍረስ የረዥም ጊዜ ህልሟን ብታሳካስ ?

    ትናንት የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በሰጡት መግለጫ ዋና አላማቸው አገዛዙን ማፍረስ እንደሆነ በግልጽ ተናግረዋል። የኢራንን መንግሥት መፍረስ በተለይ በአንዳንድ የእስራኤል ወዳጆች ሊደገፍ ይችላል። ግን ይህ ምን ክፍተት ሊፈጥር ይችላል? ምን ዓይነት ቀውስስ ሊያስከትል ይችላል? በኢራን የእርስ በርስ ጦርነት ምን ሊመስል ይችላል?

    በርካቶች በኢራቅ እና በሊቢያ ማዕከላዊ መንግሥት ሲወድቅ ምን እንደተከሰተ ያስታውሳሉ።

    በመሆኑም የኢራን አገዛዝ ቢወድቅ ምን ሊከሰት ይችላል የሚለው በቀጣይ ቀናት በሚኖረው የግጭቱ ሁኔታ ላይ ይወሰናል።

    ኢራን እንዴት የከፋ አፀፋ ትመልሳለች ? አሜሪካስ እስራኤልን ልትደግፍ ትችላለች? በሚሉት ጥያቄዎች መልስ ላይም የሚመሰረት ይሆናል።

  8. ኢራን የእስራኤል ጥቃቶች ‘አረመኔያዊ’ ናቸው ስትል ለተመድ ገለጸች

    እስራኤል በፈጸመችው ጥቃት 78 ሰዎች መገደላቸውን እንዲሁም 320 ኢራናውያን መቁሰላቸውን ያስታወቀችው ኢራን አብዛኞቹ ሰላማውያን ዜጎች ናቸው ብላለች።

    እስራኤል የፈጸመችውን ጥቃቶች “አረመኔያዊ” እንዲሁም “ወንጀል” ነው ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኢራን ተወካይ ሰኢድ ራቫኒ ተናግረዋል።

    የእስራኤል ጥቃትን ተከትሎ ኢራን ባቀረበችው ጥያቄ በኒውዮርክ ለተሰበሰበው የተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ድርጅት ነው ተወካዩ ይህንን የተናገሩት።

    ሰኢድ ራቫኒ የእስራኤል ጥቃት በኒውክሌር ተቋማት፣ በሲቪል መሰረተ ልማቶች እና የመኖሪያ አካባቢዎች ያነጣጠሩ ናቸው ብለዋል።

    ተወካዪ አክለውም “ሆን ተብሎ የተፈጸመ ስልታዊ” ግድያ ሲሉ ጥቃቱን ጠርተው “አስደንጋጭ የተሰላ የጠብ አጫሪነት ማሳያ” ነው ብለውታል።

    "አሜሪካ ለነዚህ ወንጀሎች እርዳታ እና እገዛ በማድረጓ ተባባሪ ናት" ሲሉ ወቅሰዋል።

    “እስራኤል የአሜሪካን መሳሪያ በመጠቀም በፈጸመችው ጥቃት ህዝባችን ህይወታቸውን ማጣታቸውን አንዘነጋም” ብለዋል።

    የጸጥታው ምክር ቤት የእስራኤል ን ድርጊት እንዲያወግዝ እና ተጠያቂ እንዲያደረጋትም ጠይቀዋል።

  9. እስራኤል የአየር ክልሏን እና ዋነኛ አየር ማረፊያዋን ዘጋች

    የእስራኤል የትራንስፖርት ሚኒስቴር የአገሪቱ የአየር ክልል መዘጋቱን አስታወቀ።

    በተጨማሪም የአገሪቱ ዋነኛ አየር ማረፊያ ቤን ጉሪዮን ለየትኛውም በረራ ዝግ መሆኑን አክሏል።

    የአየር ክልሉም ሆነ የአየር ማረፊያው ከሚኒስቴሩ ትዕዛዝ እስካልመጣ ድረስ ዝግ ሆነው ይቆያሉ ተብሏል።

    የቤን ጉሪዮን የአየር ማረፊያ ድረ-ገጽ ዛሬ ጥዋት እየሰራ አልነበረም።

    ሚኒስቴሩ አርብ፣ ሰኔ 6/ 2017 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ ለመጓዝ ያቀዱ መንገደኞች “የአገሪቱ አየር ክልል እንደገና ከመከፈቱ ቢያንስ ከስድስት ሰዓታት በፊት” መረጃው በመገናኛ ብዙኃን ይደርሳቸዋል ብሏል።

    እስራኤል በኢራን እየፈጸመችው ያለውን ጥቃት ተከትሎ የአየር ክልሏን ዘግታ የነበረችው ዮርዳኖስ ከአንድ ቀን በኋላ መክፈቷን አስታውቃለች።

    በአገሪቱ በረራዎች ተቋርጠው የነበረ ሲሆን ዛሬ በአገሬው ሰዓት አቆጣጠር 1፡30 የአየር ክልሏን መክፈቷን የዮርዳኖስ ሲቪል አቪዬሽን ኮሚሽን አስታውቋል።

  10. ኢራን በቴልአቪቭ አቅራቢያ ያስወነጨፈቻቸው ሚሳኤሎች ያደረሱት ጉዳት በምስል

    የእስራኤልን ጥቃት ተከትሎ ኢራን አጸፋዊ ነው ባለችው ምላሽ ሚሳኤሎችን ወደ እስራኤል አስወንጭፋለች።

    ኢራን ባስወነጨፈቻቸው ሚሳኤሎች ቢያንስ ሁለት ሰዎች መገደላቸው ተዘግቧል።

    የእስራኤል የአደጋ ጊዜ አገልግሎት እንዳስታወቀው 21 ሰዎች ቆስለዋል ብሏል።

    ከቴልቪቭ በስተደቡብ በምትገኘው ሪሾን ለዛየን በተሰኘችው ከተማ ከኢራን የተወነጨፉ ሚሳኤሎች ያደረሱት ጉዳት ምስሎች ቀጣዮቹ ናቸው።

  11. ቻይና እስራኤል በኢራን ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት አወገዘች

    እስራኤል “በኢራን ሉዓላዊነት፣ ደህንነት እና የግዛት አንድነት ላይ ጥሰት እየፈጸመች ነው” ስትል ቻይና ጥቃቱን አወገዘች።

    ቻይና የእስራኤልን ጥቃት ያወገዘችው በተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤት በተጠራው የቅዳሜ፣ ሰኔ 7/ 2017 ዓ.ም አስቸኳይ ስብሰባ ላይ በተወካይዋ ፉ ኮንግ በኩል ነው።

    ቻይና የአሁኑ ጥቃት በኢራን የኒውክሌር ድርድር ላይ የሚያሳድረው አሉታዊ ተጽእኖ “ከፍተኛ ስጋት አሳድሮብኛል” ስትል ነገሮች ከዚህ በበለጠ እንዳይከፉ እስራኤል ሁሉንም ወታደራዊ እርምጃዎችን በአስቸኳይ እንድታቆም አሳስባለች።

    የቻይና የተመድ ተወካይ በተጨማሪ ኢራን “የኑክሌር ጦር መሳሪያን ያለመስፋፋት ስምምነት ፈራሚ በመሆኗ የኒውክሌር ኃይልን በሰላማዊ መንገድ የመጠቀም መብቷ ሙሉ በሙሉ ሊከበርላት ይገባል” ብለዋል።

    ቻይና በኃይል እና መሰረተ ልማቶች የኢራን ቁልፍ አጋር ናት።

    ከጥቂት ወራት በፊትም የኢራን እና የሩሲያ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች የተሳተፉበት በኢራን የኒውክሌር ጉዳይ ላይ የመከረ ውይይትን አዘጋጅታ ነበር።

    አገራቱ በኢራን ላይ የተጣለው ማዕቀብ እንዲነሳ አሳስበዋል።

  12. እስራኤል በኢራን ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት መቀጠሏን ጦሯ አስታወቀ

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል በኢራን ኢላማዎች ባላቸው ላይ የአየር ጥቃቱን መቀጠሉን አስታወቀ።

    መከላከያው በቴሌግራም ባወጣው አጭር መግለጫ “የእስራኤል ኃይል በኢራን ውስጥ ያሉ ስጋቶችን ለማስወገድ ኢላማ ባደረጋቸው ይዞታዎች ላይ ጥቃቱን ቀጥሏል” ብሏል።

    መግለጫው የተለጠፈው የአየር ጥቃቶችን ከሚያሳይ ቪዲዮ ጋር ነው።

    እስራኤል በኢራን የኒውክሌር ይዞታዎችን እንዲሁም የጦር አዛዦች ላይ ጥቃት ፈጽማ ሶስት የኢራን ወታደራዊ አዛዦችን ከገደለች በኋላም በጥቃቷ ቀጥላለች።

    ኢራን ቅዳሜ ማለዳ በእስራኤል ላይ ሚሳኤሎችን አስወንጭፋለች።

  13. የቀጠለው የእስራኤል ጥቃት እና የኢራን አጸፋ

    እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት በመክፈት የጀመረችው ፍጥጫ አርብ ለቅዳሜ አጥቢያ ሌሊትም ቀጥሏል።

    በሁለቱም አገራት ውስጥ የአየር ጥቃቶች እና ፍንታዳታዎች መከሰታቸው ተዘግቧል።

    ኢራን የአጸፋ ሚሳዔሎችን ወደ እስራኤል በመተኮሷ በቴል አቪቭ እና ኢሩሳሌም ውስጥ የአየር ጥቃት ማስጠንቀቂያ ደወሎች እና ሲሰሙ ቴህራን ውስጥ ፍንዳታዎች ተሰምተዋል።

    የኢራን የበላይ መሪ አያቶላህ ኻሜኒ እስራኤል በአገራቸው ላይ ለፈጸመችው ጥቃት “ከባድ አጻፋ” እንሚጠብቃት ዝተዋል።

    ኢራን ወደ እስራኤል በተኮሰቻቸው ሚሳዔሎች ተጎድተዋል የተባሉ 40 ያህል ሰዎች ወደ ሆስፒታል መግባታቸው እና ከመካከላቸውም ሁለቱ በጽኑ መጎዳታቸው ተዘግቧል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ እንዳለው በእስራኤል ላይ ባለስቲክ ሚሳዔሎችን ሲተኩስ፣ የእስራኤል ጦር ሠራዊት ደግሞ ሚሳዔሎቹን ማክሸፉን አስታውቋል።

    በተባበሩት መንግሥታት የኢራን መልዕክተኛ በእስራኤል ጥቃት ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዦችን ጨምሮ 78 ሰዎች መገደላቸውን እና ከ320 በላይ የሚሆኑ ደግሞ መቁሰላቸውን አስታውቀዋል።

    አሜሪካ እስራኤልን በመደገፍ ስትቆም፣ ቻይና እና ቱርክ የእስራኤልን ድርጊት በማውገዝ አቋማቸውን ገልጸዋል።

    የተባበሩት መንግሥታት እና ሌሎች አገራት ደግሞ ኢራን እና እስራኤል ግጭቱን ከሚያባብሱ እርምጃዎች እንዲቆጠቡ ጥሪ አቅርበዋል።