የእስራኤል እና ኢራን ግጭት “መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል” ተመድ

ስምንተኛ ቀኑን የያዘው የእስራኤል እና ኢራን ግጭት “መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል” ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አሳሰቡ።ዋና ጸሐፊው በአገራቱ መካከል ያለው ግጭት መቀጠል አለምን ወደ ቀውስ የሚከት ነው ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

  • እስራኤል እና ኢራን ግጭት "መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል" ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አሳሰቡ
  • ኢራን በእስራኤል ያልተጠበቀ ጥቃት የተፈጸመባት "ከአሜሪካ ጋር የኒውክሌር አቅምን አስመልክቶ ተስፋ ሰጪ ዲፕሎማሲያዊ ሂደት ላይ በነበረችበት ወቅት" መሆኑን አስታወቀች።
  • የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ከእስራኤል ጋር ያለውን ግጭት ለማስቆም ፈረንሳይን ጨምሮ አውሮፓውያኑ አገራት ለኢራን የዲፕሎማሲ ፕሮፖዛል እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል።
  • ዶናልድ ትራምፕ በሚቀጥሉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ ዩናይትድ ስቴትስ በኢራን እና በእስራኤል ግጭት ውስጥ በቀጥታ ጣልቃ መግባት አለመግባቷን ይወስናሉ- ዋይት ሐውስ
  • ትራምፕ በመካከለኛው ምሥራቅ ግጭት ላይ ለመወሰን ሁለት ሳምንት ጊዜ ሲሰጡ ዩኬ እና የአውሮፓ ኅብረት ከኢራን ጋር ሊነጋገሩ ነው
  • የኢራን ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ለቢቢሲ አሜሪካ በግጭቱ ውስጥ የምትሳተፍ ከሆነ ቀጠናው "ሲኦል" ይሆናል ሲሉ ተናግረው ነበር
  • ኢራን በትናንትናው ዕለት በፈጸመችው የሚሳኤል ጥቃት ከሆስፒታል አቅራቢያ ያለ ወታደራዊ ስፍራ ማነጣጠሩን ገልጽላች
  • ኢራን ባስወነጨፈቻቸው ሚሳኤሎች በደቡባዊ እስራኤል ባርሺባ ከተማ የሚገኘውና በእስራኤል ትልቁ ከሚባሉት አንዱ ሶሮካ ሆስፒታል መመታቱን እስራኤል አስታወቀች።
  • የተመድ የጸጥታው ምክር ቤት በእስራኤል እና ኢራን ግጭት አስቸኳይ ስብሰባ ሊያካሂድ ነው
  • የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራንን ለማጥቃት ዕቅድ ቢያጸድቁም ነገር ግን የመጨረሻ ውሳኔ ላይ አለመድረሳቸው ተዘገበ።
  • አሜሪካ የጦር ጄቶችን ጨምሮ የጦር መሳሪያዎችን ወደ መካከለኛው ምስራቅ እያንቀሳቀሰች ነው
  • ፑቲን በኻሜኒ ላይ የታቀደውን ግድያ አስመልክቶ "በፍጹም በዚህ ጉዳይ ላይ መወያየት አልፈልግም" አሉ
  • የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ "ኢራናውያን እጃቸውን የሚሰጡ ሕዝቦች አይደለም" ሲሉ ተናገሩ።
  • እስራኤል በኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት እስከ እሁድ ምሽት ድረስ 224 ሰዎች ሲገደሉ 1 ሺህ 277 መጎዳታቸውን ኢራን አስታውቃለች። እስራኤል በበኩሏ በጥቃቶቹ 20 ሰዎች ተገድለውብኛል ብላለች።
  • ትራምፕ ኢራን ላይ ጥቃት መፈጸምን በተመለከተ "ላደርገው ወይም ላላደርገው እችላለሁ" አሉ
  • ፎርዶ ኢራን ካሏት ሁለት ወሳኝ የኒውክሌር ማብላያ ጣቢያዎች መካከል አንዱ ሲሆን የእስራኤል መከላከያ ኃይል የአየር ጥቃት ቢያደርስበትም ጉዳት ሊደርስበት አልቻለም።

የቀጥታ ሽፋን

  1. የእስራኤል ጥቃት ሊጎዳው ያልቻለው የኢራኑ የኒውክሌር ማበልጸጊያ ፎርዶ

    ከሰሞኑ እስራኤል በኢራን ላይ እያካሄደችው ካለው ጥቃት ጋር ተያይዞ ስሙ እየተጠቀሰ ያለው የፎርዶ የኒውክሌር ማብላያ ጣቢያ ነው።

    ፎርዶ ኢራን ካሏት ሁለት ወሳኝ የኒውክሌር ማብላያ ጣቢያዎች መካከል አንዱ ሲሆን የእስራኤል መከላከያ ኃይል የአየር ጥቃት ቢያደርስበትም ጉዳት ሊደርስበት አልቻለም።

    ፎርዶ ከቴህራን በስተደቡብ በ200 ኪሎሜትር ርቀት ላይ ይገኛል።

    የተገነባውም በተራራ ተከቦ ከመሬት በታች ከ80-90 ሜትር ጥልቀት ላይ ሲሆን ለዚህም ዋነኛ ምክንያቱ ከደህንነት እና ከጥበቃ ጋር የተያያዘ ነው።

    ኢራን ዩራኒየም- 235 የተሰኘውን ለማግኘት ከምትጠቀምባቸው ቁልፍ የማበልጸጊያ ጣቢያዎች አንዱ ነው።

    የፎርዶን የኒውክሌር ማብላያን መድረስ የሚችለው የአሜሪካው 14 ሺህ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝነው ‘በንከር በስተር’ የተሰኘው ቦምብ እንደሆነ እየተነገረ ነው።

    ቦምቡ ከመሬት ስር ያሉ ስፍራዎችን እንዲሁም ከፍተኛ ጥበቃ የሚደረግላቸውን የተቀበሩ የጦር መሳሪያዎችን ለማውደም ታልሞ የተሰራ ነው።

    ቦምቡ ከመፈንዳቱ በፊት መሬት፣ አለት ወይም ድንጋይ ሰንጥቆ በመግባት ሳይፈነዳ መቆየት ይችላል።

    ስድስት ሜትር እርዝማኔ እና 14 ሺህ ኪሎግራም ከመመዘኑ አንጻር የአሜሪካው ቢ-2 የተሰኘው መሳሪያ ነው ሊሸከመው የሚችለው።

    እስራኤል ፎርዶን ብቻዋን ማውደም እንደማትችል እየተገለጸ ነው። አሜሪካ 'በንከር በስተር' የተሰኘውን ቦምብ ለእስራኤል ለመስጠት ከልክላለቸ።

  2. ትራምፕ ኢራን ላይ ጥቃት መፈጸምን በተመለከተ “ላደርገው ወይም ላላደርገው እችላለሁ” አሉ

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ አገራቸው በኢራን ጥቃት ትሳተፍ እንደሆነ ተጠይቀው

    “ይህንን ማለት አልችልም። ላደርገው ወይም ላለደርገው እችላለሁ። ማድረግ የምፈልገውን ማንም አያውቅም። ነገር ግን ማለት የምችለው ኢራን ከፍተኛ ችግር ውስጥ ናት እና መደራደር ትፈልጋለች” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል።

    ትራምፕ ይህንን ምላሽ የሰጡት በዛሬው ዕለት በዋይት ሃውስ ሲሆን ከኢራን ጋር በተያያዘ ለሚቀርብላቸው ጥያቄ ብዙም ምላሽ መስጠት አልፈለጉም።

    ሆኖም በቅርብ ቀናት የተናገሩትን አጽንኦት በመስጠት እስራኤል ጥቃት ከመፈጸሟ በፊት ኢራን ለመደራደር ፈቃደኛ መሆን ነበረባት የሚል ምላሽ ሰጥተዋል።

  3. በአንዳንድ የኢራን ከተሞች የምግብ እና የነዳጅ እጥረት መከሰቱን ነዋሪዎች ተናገሩ

    ስድስተኛ ቀኑን ከያዘው የእስራኤል ጥቃት ጋር በተያያዘ በኢራን ውስጥ በሚገኙ ከተሞች የምግብ እና የሌሎች አቅርቦቶች እጥረት መከሰቱ ተዘግቧል።

    ይህንን በተመለከተ የቢቢሲ ፐርሺያ (ፋርስ) ቋንቋ አገልግሎት ኢራናውያን በያሉበት አካባቢዎች ስላለው ሁኔታ የሚመለከቱትን እንዲያጋሩ በጠየቃቸው መሠረት የምግብ አቅርቦት እጥረት እንዳለ ተናግረዋል።

    ካራጅ የተባለው ከዋና ከተማዋ ቴህራን ወጣ ብላ በምትገኝ ከተማ የሚገኝ ግለሰብ እንዳለው “ትናንት [ማክሰኞ] ፍራፍሬ ለመግዛት ወደ ገበያ ማዕከል ሄጄ መደርደሪያዎቹ ከሞላ ጎደል ባዶ ሆነው ነው ያገኘሁት።”

    ጨምሮም "ከነዳጅ፣ ከትራንስፖርት እና ከእስራኤል ጥቃቶች ጋር በተያያዘ ሸቀጦችን ለማሠራጨት ምንም መንገድ የለም። ይህም በጣም አሳሳቢ ችግር ፈጥሮብናል።”

    ሌላ የቴህራን ነዋሪ ደግሞ በአቅራቢያው ባለ መደብር ውስጥ “በቂ ሸቀጦች አሉ፤ ከመደርደሪያዎች ላይ ሲያልቁም ወዲያው ይተካሉ።” “በአሁኑ ወቅት ሰዎች በአብዛኛው የሚሸምቱት የደረቁ ፍራፍሬዎች እና ፓስታ ነው። ዳቦ ቤቶች በጣም ጭር ብለዋል፤ የነዳጅ ማደያዎች ግን በተሽከርካሪዎች እንደተጨናነቁ ናቸው” ብሏል።

    የገንዘብ መክፈያ የባንክ ካርዶች እየሠሩ ስላልሆነ፣ ሰዎች ለክፍያ ጥሬ ገንዘብ እንዲይዙ እየተመከሩ መሆናቸውንም ነዋሪዎች ገልጸዋል።

    ከቴህራን አቅራቢያ በምትገኘው ቃዝቪን በተባለች ከተማ ነዋሪ የሆነው ግለሰብ ደግሞ ከዚህ በፊት ብዙ ጊዜ ጭር ብለው ይውሉ በነበሩት ዳቦ ቤቶች አካባቢ ረጃጅም ሰልፎች እየታዩ መሆኑን ተናግሯል።

  4. በእስራኤል ውስጥ የሚካሄዱ እንቅስቃሴዎች ቀስ በቀስ እየተከፈቱ ነው - የመከላከያ ሚኒስትሩ

    የእስራኤል የመከላከያ ሚኒስትር ኢዝራኤል ካትዝ ከኢራን ጋር በገቡት ግጭት ምክንያት ተዘግተው ከነበሩ የአገሪቱ ክፍሎች ውስጥ አብዛኞቹን መክፈት መቻሉን በመግለጽ፣ ይህም በኢራን ላይ የድል ስለመቀዳጀታቸው የሚያበስር “መልዕክት" ሲሉ ጠርተውታል።

    ካትዝ መንግሥታቸው የእስራኤልን ሕዝብ ከመጠበቅ በተጨማሪ ባለው የፀጥታ ሁኔታ ላይ በመመሥረት "ኢኮኖሚውን እና የተለያዩ ክልሎችን ቀስ በቀስ በመክፈት ሂደት ላይ ናቸው" ብለዋል።

    ይህም መንግሥት ከኢራን በኩል ያለው የጥቃት ስጋት ቀንሷል ብሎ እንደሚያምን ያሳያል።

    የመከላከያ ሚኒስትሩ ጨምረውም ከኢራን ጋር የሚደረገው “ጠንካራ ውጊያ” እስራኤል ተጋርጠውብኛል የምትላቸው “ስጋቶቹ እስኪወገዱ ድረስ” እንደሚቀጥልም ተናግረዋል።

  5. በግጭቱ 224 ኢራናውያን ሲገደሉ ከእስራኤል በኩል 20 ተገድለዋል

    እስራኤል በኢራን ላይ የጀመረችው ጥቃት ስድስተኛ ቀኑን ይዟል። ኢራን በአጸፋው ሚሳኤሎችን ወደ እስራኤል እያስወነጨፈች ትገኛለች።

    በስድስቱ ቀናት ግጭት አንኳር ጉዳዮች፦

    አርብ፦ ሐሙስ ለአርብ አጥቢያ እስራኤል በኢራን የኒውክሌር ይዞታዎች እንዲሀም የመኖሪያ ስፍራዎች ላይ በፈጸመችው ጥቃት የኢራን የጦር አዛዦች፣ ኒውክሌር ሳይንቲስቶች እንዲሁም ህጻናትን ጨምሮ ሰላማዊ ሰዎች ተገድለዋል። ኢራን በአጸፋው የእስራኤን ወታደራዊ ማዕከላትና የጦር ሰፈሮች ላይ ድሮኖች እንዲሁም ሚሳኤሎችን አስወንጭፋለች።

    ቅዳሜ እና እሁድ፦ በሳምንቱ መጨረሻ አገራቱ የሚያደርጉት የአየርና የሚሳኤል ጥቃቶች የቀጠለ ሲሆን በዚህም የነዳጅ መሰረተ ልማቶች ተመትተዋለ። እስራኤል በኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት እስከ እሁድ ምሽት ድረስ 224 ሰዎች ሲገደሉ 1 ሺህ 277 መጎዳታቸውን ኢራን አስታውቃለች። እስራኤል በበኩሏ በጥቃቶቹ 20 ሰዎች ተገድለውብኛል ብላለች።

    ሰኞ፦ እስራኤል የሰሜናዊ ቴህራን ነዋሪዎች አካባቢያቸውን ለቀው እንዲወጡ አስጠንቅቃለች። በዚያው ዕለትም የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ 17 ሚሊዮን ህዝብ በሚኖርባት ቴህራን “ነዋሪዎች በሙሉ ከተማዋን በአስቸኳይ ለቀው መውጣት አለባቸው” ሲሉ በማህበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ አስጠንቅቀዋል።

    ማክሰኞ፦ ማክሰኞ ዕለት ነዋሪዎች ከቴህራን ለመውጣት ሲሞክሩ በከተማዋ ዙሪያ የትራፊክ መጨናነቅ ታይቷል። ትራምፕ በተጨማሪም የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒን “ቀላል ኢላማ ነው። አሁን አንገድለውም” ሲሉ ጽፈዋል።

  6. ትራምፕ በኢራን የገቡበት አጣብቂኝ የሪፐብሊካኖች መከፋፈልን አጋለጠ

    እስራኤል በኢራን ላይ በጀመረችው ጥቃት አሜሪካ በቀጥታ ተሳታፊ ትሁን ወይስ አትግባበት የሚለው ጥያቄ በአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሪፐብሊካን ደጋፊዎች ዘንድ ያለውን መከፋፈል አጋልጧል።

    የሪፐብሊካኑ ፕሬዚዳንት በዋይት ሃውስ፣ ሲቹዌሽን ሩም ውስጥ ትናንትና፣ ሰኔ 10/ 2017 ዓ.ም ከብሔራዊ ደህንነት አማካሪዎቻቸው ጋር ያደረጉትን ውይይት ተከትሎ ኢራንን ማጥቃት ወደሚለው አዘንብሏል።

    ሆኖም ትራምፕ የሚታወቁበት ቅድሚያ ለአሜሪካ (አሜሪካ ፈርስት) የሚለው መፈክራቸው ጋር ተያያዞ አገሪቱ በአፍጋኒስታን፣ እና ኢራቅ ጣልቃ ገብነት በሺዎች ለሚቆጠሩ የአሜሪካ ወታደሮች ሞት እንዲሁም “መውጫ ከሌለው ጦርነት” አገራቸውን ለመታደግ ቃል ገብተው ነበር።

    በፓርቲው ውስጥ ያሉ ሌሎች የጦርነት ደጋፊዎች ትራምፕ ኢራንን እንዲያጠቁ ግፊት እያደረጉ ይገኛሉ።

    የደቡብ ካሮላይና ሴናተር ሊንሴይ ግራሃም ኢራን የኒውክሌር ቦምብ እንዳታገኝ መከልከል ለአሜሪካ ብሔራዊ ደህንነት ጥቅም ነው ብለዋል።

    ኢራን የኒውክሌር መርሃ ግብሯን ለሰላማዊ እንዲሁም ለኃይል ማግኛነት ላሉ የሲቪል ዓላማዎች እንደምትገለገልበት ትገልጻለች።

  7. “ኢራናውያን እጃቸውን የሚሰጡ ሕዝቦች አይደሉም" አያቶላህ አሊ ኻሜኒ

    የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ “ኢራናውያን እጃቸውን የሚሰጡ ሕዝቦች አይደለም” ሲሉ ተናገሩ።

    ኻሜኒ “ሕዝቧን፣ ታሪኳን የሚያውቁ ብልህ ሰዎች ይህችን አገር በዛቻ ቋንቋ በፍጹም አይናገሯትም። ምክንያቱም ኢራናውያን እጃቸውን የሚሰጡ ሕዝቦች አይደሉም” ብለዋል።

    ኻሜኒ ይህንን ያሉት የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለኢራን መሪዎች ባስተላለፉት መልዕክት “ያለምንም ማወላወል እጅ መስጠት” አለባቸው በማለት መናገራቸውን ተከትሎ ነው።

    አያቶላህ ኻሜኒ የአሜሪካ ወታደራዊ እርምጃ “በማይጠገን ጉዳት” ምላሽ እንደሚሰጠውም ነው በዚሁ በቴሌቪዥን በተላለፈው መልዕክታቸው የገለጹት።

    በቴሌቪዥን አቅራቢ አማካይነት በተላለፈ መልዕክታቸው “ማንኛውም ዓይነት የአሜሪካ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት በማይጠገን ጉዳት ምላሽ እንደምንሰጥ ጥርጣሬ አይግባችሁ” ብለዋል።

    ጠቅላይ መሪው ኢራን በግድ የተጫነባትን ሰላምም ሆነ ጦርነት አትቀበልም ሲሉ አጽንኦት ሰጥተዋል።

    ዶናልድ ትራምፕ “‘ጠቅላይ መሪ’ እየተባሉ የሚጠሩት ግለሰብ የት እንደተደበቁ በትክክል እናውቃለን።

    "እሱ ቀላል ዒላማ ነው። ግን እዚያ መሆናቸው መልካም ነው። እሱን አናስወግድም (አንገድለውም!) ቢያንስ ለአሁን” ሲሉ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ አጋርተዋል።

  8. የእስራኤል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር 'ኢራን ላይ ጥቃት መፈፀም የመጨረሻ አማራጫችን ነበር' አሉ

    የእስራኤል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ሳዓር በኤክስ ገጻቸው ላይ ለተባበሩት መንግሥታት የፀጥታ ምክር ቤት እና ለተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ የላኩትን ደብዳቤ አጋርተዋል።

    በዚህ ደብዳቤያቸው ላይ እስራኤል ባለፈው ሳምንት ኢራን ላይ ጥቃት የሰነዘረችበትን ምክንያት ጠቅሰዋል።

    ሚኒስትሩ አገራቸው “ለአስርት ዓመታት” የቴህራን “ድብቅ የሆነ የጠላትነት ተግባር” እና መሪዎቿ እስራኤልን “ለማጥፋት” መዛታቸውን ተከትሎ፣ አገራቸው ምንም ዓይነት ምርጫ እንዳልተሰጣት ጠቅሰዋል።

    "ንግግር ብቻ አይደለም፤ ኢራን እስራኤልን ለማጥፋት ስትራቴጅካዊ ዕቅድ አላት። እዚህ ግብ ላይ ለመድረስ ተጨባጭ ዕቅዶችን እና እርምጃዎችን አካትታለች" ሲሉ ጽፈዋል።

    የወደፊት የኢራንን ጥቃት ለማክሸፍ “የመጨረሻው የዕድል መስኮት” በተገኘበት ወቅት ማጥቃታቸውን ተናግረዋል።

    ሳዓር በኢራን ጥቃት የተገደሉትን 24 ሰዎች በመጥቀስ በሰላማዊ ሰዎች ላይ ሆን ብሎ ያነጣጠረ እና “በዘፈቀደ” የተፈጸመ ሲሉ ገልጸውታል።

    የኢራን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር እሁድ ዕለት በእስራኤል ጥቃት በትንሹ 224 ሰዎች መገደላቸውን ገልጾ አብዛኞቹ ሰላማዊ ዜጎችናቸው ብሏል።

  9. የእስራኤል መከላከያ ኢራን ውስጥ ድሮን ተመትቶ መውደቁን አረጋገጠ

    የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት አንድ ሰው አልባ አውሮፕላኑ በኢራን ተመትቶ መውደቁን አረጋገጠ።

    "በዘመቻ ስምሪት ላይ እያለ ከምድር ወደ አየር የተወነጨፉ ሚሳዔሎች በርቀት በምንቆጣጣረው አውሮፕላን ላይ ተተኩሷል።

    “አውሮፕላኑ በኢራን አየር ክልል ነው የወደቀው። የደረሰ ጉዳት የለም፤ እንዲሁም መረጃ ይሾልካል የሚል ስጋት የለንም” ሲሉ የመከላከያ ቃል አቀባይ ተናግረዋል።

    ዛሬ ማለዳ የኢራን ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣብያ የኢራን አየር ኃይል ዛሬ ማለዳ ላይ በማዕከላዊ ኢስፋሃን ግዛት ዘመናዊ ሄርሜስ ሰው አልባ አውሮፕላን ተኩሶ መጣሉን ገልጿል።

    በእስራኤል መከላከያ እና በኢራን የተጠቀሰው ሰው አልባ አውሮፕላን ተመሳሳይ መሆናቸውን ማረጋገጥ አንችልም፤ ግን ሁለቱም መግለጫዎች ተመሳሳይ ናቸው።

  10. ዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ሁለት የኢራን የዩራኒየም ማብላያዎች መመታታቸውን ገለፀ

    ዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ በኢራን ውስጥ ሁለት የዩራኒየም ማብላያ ተቋማት መጎዳታቸውን መረጃ አለኝ ብሏል።

    እስራኤል ዛሬ ጠዋት ሌሊቱን የዩራኒየም ማብላያዎችን መደብደቧን መግለጿ ይታወሳል።

    ኤጀንሲው በቴህራን የምርምር ማዕከል የላቁ የዩራኒየም ማብላያዎች ተሠርተው የተሞከሩበት አንድ ሕንፃ ተመትቷል ብሏል።

    አክሎም የኢራን የዩራኒየም ማብላያ ቴክኖሎጂ ኩባንያ የተለያዩ የዩራኒየም ማብላያ አካላት የሠራባቸው ሁለት ሕንፃዎች ወድመዋል ብሏል።

    ኤጀንሲው ሁለቱም ጣቢያዎች ቀደም ሲል በኢራን የኒውክሌር ስምምነት መሰረት ክትትል ይደረግባቸው እንደነበር ገልጿል።

    የበለፀገ ዩራኒየም ለኃይል ወይንም ለኒውክሌር መሣርያ ማምረቻነት ሊውል ይችላል።

  11. የትራምፕ “ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እጅ ስጡ” ጥሪ ለኢራን "ውርደት” ሊሆን ይችላል - የፖለቲካ ተንታኝ

    ለኢራን የኒውክሌር ፕሮግራሟን መተው እና "ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እጅ መስጠት"፤ "ውርደት" እንደሚሆን የፖለቲካ ተንታኝ ተናገሩ።

    ለቢቢሲ 5 ሃሳባቸውን ያጋሩት አልበርት ዎልፍ ትራምፕ የኢራኑ መሪ “ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እጅ ስጡ” ማለታቸው እንዲሁም የአገሪቱን የኒውክሌር ፕሮግራም ሙሉ በሙሉ እንዲዘጉ ያቀረቡት ጥያቄ፣ ለኢራን “ውርደት” ሊሆን ይችላል ብለዋል።

    ዎልፍ ፕሬዚደንት ትራምፕ “ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እጅ ስጡ” ማለታቸው ሁሉም የኢራን የኒውክሌር ተቋማት ይወድማሉ እንዲሁም የኒውክሌር ቴክኖሎጂ ይጣላል ማለት ነው ብለዋል።

    “የሚሳዔል ፕሮግራማቸውን ሊተዉ ይችላሉ። እንዲሁም ሌሎች አማፂያንን እንደ ሃማስ እና ሄዝቦላህ ያሉትን መደገፋቸውን ሊያቆሙ ይችላሉ” ብለዋል።

    ዎልፍ አክለውም ይህ ለኢራን ከባድ ሊሆን ይችላል። ምክንያቱም የኒውክሌር ፕሮግራም የአገሪቱ ማዕከላዊ ጉዳይ ነው።

    “ኩራት እና በዓለም ላይ ያላቸው ደረጃ ነው” ካሉ በኋላ ይህንን መተው የመሳርያ ቁጥጥር ስምምነት ብቻ አይሆንም ነገር ግን “ውርደት” ነው ብለዋል።

  12. የፎርዶን የኒውክለር ተቋም ለማውደም ‘አስቸጋሪ’ ሊሆን እንደሚችል የቀድሞው የኒውክሌር ተቆጣጣሪ ተናገሩ

    የኒውክሌር ፊዚክስ ሊቅ እና የቀድሞ የተባበሩት መንግሥታት የኒውክሌር ተቆጣጣሪ ዴቪድ አልብራይት የኢራን የምድር ውስጥ የኒውክሌር ጣቢያን፣ ፎርዶ፣ ከመሬት በታች 80 ሜትር ጥልቀት ላይ የሚገኝ መሆኑን ገልፀው "ለማጥፋት በጣም ከባድ ነው" አሉ።

    ከቢቢሲ ራዲዮ 5 ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ ላይ በኢራቅ ውስጥ ያገኟቸው ተሞክሮዎች፣ የዓለም አቀፍ የአቶሚክ ኢነርጂ ድርጅት ምርመራ ኤጀንሲ “ሚስጥራዊ ፕሮግራሞችን ለመመርመር መንገዶችን” እንዲያዳብር እንደረዳቸው ያስረዳሉ።

    አክለውም “አሁን የእስራኤል ድብደባ፣ ያንን ቦታ ለረጅም ጊዜ ከስራ ውጪ ማድረግ ይችላል ብዬ አምናለሁ። ዩናይትድ ስቴትስ ደግሞ ሙሉ በሙሉ ልታወድመው ትችላለች።"

    በዋሽንግተን የሚገኘው የሳይንስ እና የዓለም አቀፍ ደህንነት ተቋም መስራች የሆኑት አልብራይት ፎርዶ "ከሚያስፈራቸው" የኒውክሌር ተቋማት መካከል አንዱ ነው ብለዋል።

    ብቸኛው ግን አይደለም፤ ካሉ በኋላ ስለዚህ የበለጠ ትኩረት ሊሰጠው አይገባም ሲሉ ይናገራሉ።

    ፎርዶ የተሰራው ከመጀመሪያዎቹ የኢራን የኒውክሌር ጦር መሳሪያ ፕሮግራሞች አካል ሆኖ ነው።

  13. ስለ ኢራኑ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ምን እናውቃለን?

    የኢራንን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ በአውሮፓውያኑ 1939 በኢራን ሁለተኛዋ ትልቅ ከተማ ማሽሃድ ነው የተወለዱት።

    በሃይማኖተኛ ቤተሰብ ውስጥ ከተወለዱት ስምንት ልጆች መካከል ሁለተኛ ልጅ የሆኑት የኻሜኒ አባት በኢራን ዋነኛው የእስልምና ቅርንጫፍ የሆነው የሺዓ እስልምና በመካከለኛ ደረጃ የነበሩ የሃይማኖት መምህር ነበሩ።

    የሕጻኑ ኻሜኒ አብዛኛው የትምህርት ጊዜ ቁርዓንን በማጥናት የተሸፈነ ነበር። በ11 ዓመታቸውም የሃይማኖት መምህር ለመሆን በቅተዋል።

    ነገር ግን በጊዜው እንደነበሩት ብዙዎቹ የሃይማኖት መሪዎች ሁሉ ሥራው ከመንፈሳዊ ባልተናነሰ መልኩ ፖለቲካዊም ነበር።

    አንደበተ ርቱዕ የነበሩት ኻሜኒ በኢራን እስላማዊ አብዮት ከሥልጣን የተወገዱት የኢራን ንጉሥ ሻህ ተቺዎችን ተቀላቀሉ።

    ለዓመታት በህቡዕ ወይም በእስር ቤት አሳልፈዋል። ከስድስት ጊዜ በላይ በኢራን ንጉሣዊ የምሥጢር ፖሊስ ተይዘው ለስቅይት እና አካባቢያቸውን ትተው እንዲሰደዱ ተደርገዋል።

    በአውሮፓውያኑ 1979 የኢራን እስላማዊ አብዮት ከተካሄደ ከአንድ ዓመት በኋላ አያቶላህ ሩሆላህ ኻሜኒ የዋና ከተማይቱ ቴህራን የጁምዓ ሶላት መሪ አድርገው ሾሟቸው።

    በ1989 ደግሞ ኻሜኒ በ86 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት አያቶላ ኾሜኒ ምትክ ሆነው በሃይማኖት መሪዎች ከመመረጣቸው በፊት በ1981 ፕሬዝዳንት ሆነው ተመረጡ።

  14. የጋዛ ነዋሪዎች ስለ ኢራን እና እስራኤል ግጭት ምን ይላሉ?

    በኢራን እና በእስራኤል መካከል የተፈጠረው ግጭት በተመለከተ ከጋዛ ነዋሪዎች የሚሰሙት አስተየየቶች የተደበላለቁ ናቸው።

    በእስራኤል ላይ በደረሰው የሚሳዔል ጥቃት ደስተኞች የሆኑ ነዋሪዎች የመኖራቸውን ያህል የሁለቱ አገራት ቀውስ የረዥም ጊዜ ስቃያቸውን የበለጠ ሊሸፍን ይችላል የሚል ስጋት ያላቸውም አሉ።

    አንዳንድ ፍልስጤማውያን የኢራን የሚሳኤል ጥቃትን ተከትሎ የእስራኤል ሕንጻዎች ሲፈርሱ እና ንፁሀን ዜጎች በፍርስራሹ ውስጥ ተቀብረው በማየታቸው እጅግ በጣም ደስተኛ መሆናቸውን ይናገራሉ።

    ሆኖም ዓለም ትኩረቱን ለ20 ወራት ከዘለቀው ጦርነት፣ የእርዳታ ማዕቀብ እና ሰብዓዊ ውድመት ዓይኑን ማንሳቱ የፍራቻ ስሜት ፈጥሮባቸዋል።

    በእስራኤል የአየር ጥቃት ወንድሙን፣ ሚስቱን እና ሦስት ልጆቹን ያጣው ሐሰን ኦማር ታልባ፣ ኢራን ለጋዛ ድጋፍ ታደርጋለች ተብሎ መታሰቡ ያበሳጨዋል።

    "ኢራን ትምህርት ቤት፣ ሆስፒታል ገንብታ አታውቅም። ወይም አንድ ጭነት መኪና እርዳታ ወደ ጋዛ ልካ አታውቅም" ሲል ተናግሯል።

    "ያደረጉት ነገር ቢኖር ሮኬቶችን ለሐማስ አስታጥቀው ግጭቱን ማባባስ ነው" ይላል።

    ያም ሆኖ፣ “እስራኤልን ዒላማ የሚያደርገውን ሁሉ እደግፋለሁ፤ የእስራኤል ሰላማዊ ዜጎች እኛ ጋዛ ውስጥ ለ20 ወራት ያህል ያየነውን ፍዳ ለአንድ ሌሊት ይዩት።"

    የአምስት ልጆች አባት የሆነው አላ ሳላህ ተመሳሳይ አስተየየት አለው።

    "እዚህ የሚካሄደው ጦርነት አልቆመም። ሞት፣ ረሃብ እና መፈናቀል የዕለት ተዕለት ሕይወታችን አካል ነው። ነገር ግን ዓለም በኢራን እየሆነ ባለው የዓለም ትኩረት ተሰርቋል። መገናኛ ብዙኃን እንኳ በጋዛ እየሆነ ያለውን መዘገብ ትተዋል።"

    አክሎም "ለአስርት ዓመታት በማያቋርጥ ጦርነት ውስጥ የኖርነው እኛ የጦርነትን ዋጋ እናውቀዋለን። ስሜቴ የተደበላለቀ ነው። ኢራን ለሐማስ መሳሪያ አስታጥቃለች። ስቃያችንን ነው ያባሰው። ነገር ግን በኢራን አገዛዝ እና በተጨቆነው ሕዝብ መካከል ልዩነት መኖሩን አያለሁ። ልክ እንደ እኛ የመሪዎቻቸው ሰለባዎች ናቸው።"

  15. የኢራን አየር መከላከያ የእስራኤልን ዘመናዊ ድሮን መትቶ መጣሉ ተዘገበ

    የኢራን የአየር መከላከያ ኃይል በማዕከላዊው ኢስፋሃን ግዛት ውስጥ ጥቃት ለመፈጸም የተሰማራ ሄርሜስ የተባለ ዘመናዊ የእስራኤል ድሮን መትቶ መጣሉን የኢራን መንግሥት ቴሌቪዥን አስታወቀ።

    የጣቢያው ዘጋቢ ድሮኑ ከወደቀበት ስፍራ ካለ ስብርባሪ ጎን ቆሞ ተመትቶ የወደቀው በአገሪቱ ሰዓት አቆጣጠር ዛሬ ንጋት 11 ሰዓት ላይ መሆኑን ገልጿል።

    ዘጋቢው ጨምሮም ድሮኑ ተመትቶ የወደቀው የታጠቀውን መሳሪያ ከመተኮሱ በፊት መሆኑን እና የኢራን አየር መከላከያ ኃይልን ቀድሞ የመለየት እና ምላሽ የመስጠት ብቃትን ገልጿል።

  16. የኢራን ዋና ከተማ ነዋሪዎች የእስራኤልን ጥቃት ለመሸሽ ከቴህራን እየወጡ ነው

    እስራኤል በኢራን ላይ የከፈተችውን ጥቃት ተከትሎ ሁለቱ አገራት አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ የሚሳዔል እና የአየር ጥቃት እየፈጸሙ ሲሆን፣ ነዋሪዎች ጉዳት እንዳይደርስባቸው መኖሪያቸውን ለቀው እንዲወጡ ቅድመ ማስጠንቀቂያ በተደጋጋሚ እየሰጡ ነው።

    በኢራን ዋና ከተማ ላይ ላለፉት ቀናት ተደጋጋሚ ጥቃቶችን እየፈጸመች ያለችው እስራኤል ነዋሪዎች ከተለያዩ የቴህራን ክፍሎች ለቀው እንዲወጡ ስታስጠነቅቅ ቆይታለች።

    በዚህም ምክንያት ነዋሪዎች የቻሉትን ንብረት እየያዙ ከከተማዋ ለመውጣት በሚያደርጉት ጥረት በነዳጅ ማደያዎች እና በጎዳናዎች ላይ ረጃጅም ሰልፎች እና የትራፊክ መጨናነቆች እየታዩ ነው።

  17. ኢራን መጀመርያ አሜሪካን ልታጠቃ እና ወደ ጦርነቱ ልታስገባት ትችላለች- የቀድሞው የእስራኤል አምባሳደር

    የቀድሞው በአሜሪካ የእስራኤል አምባሳደር ኢራን የአሜሪካን መርከብ ወይንም ጦር ሠፈር በማጠቃት ወደ ጦርነቱ ልታስገባት ትችላለች የሚል ፍራቻ እንዳላቸው ገለፁ።

    ማይክል ኦርየን በዋይት ሐውስ አሜሪካ በመካከለኛው ምሥራቅ ወደ ሌላ ጦርነት ገብታ ማየት የማይፈልጉ አሉ ሲሉ ተናግረዋል።

    “[ኢራን መጀመርያ አሜሪካን በማጥቃት] ትራምፕ ላይ በዋይት ሐውስ ጫና በመፍጠር፤ ፕሬዚደንት ትራምፕ እስራኤል ላይ ጫና ሊያደርጉ ይችላሉ” ከዚያም ጦርቱ እንዲያበቃ ድርድር ሊያደርጉ ይፈልጋሉ ሲሉ ለቢቢሲ ሬዲዩ 4 ተናግረዋል።

    “ኢራናውያን የሚያስቡት እንደዚያ ሊሆን ይችላል” ያሉት ኦሪየን “ያ ነው ያለኝ ፍርሃት” ብለዋል።

    ኦርየን እስራኤል ጥቃቷን መቀጠል እንዳለባት ገልፀው፣ በአሜሪካ የሚገኙ አንዳንድ ሰዎች እነደሚሉት አሁን ተኩስ አቁም የሚደረግበት ሰዓት አይደለም ብለዋል።

    “ለምንድን ነው እንድንናቆም የሚፈለገው? ለምንድን ነው ኢራን ተጨባጭ በሆነ ሁኔታ አቅሞ አንሶ ማየት የማይፈልገው?“ ሲሉም ይጠይቃሉ።

  18. እስራኤል የአየር ክልሏን በመዝጋቷ የተነሳ ወደ አገራቸው መግባት ያልቻሉ እስራኤላውያንን ማምጣቷ ተገለፀ

    እስራኤል የአየር ክልሏን በመዝጋቷ ሳቢያ በተለያዩ ውጭ አገራት የሚገኙ እስራኤላውያንን የያዘው የመጀመሪያው አውሮፕላን ቤን ጉሪዮን አውሮፕላን ማረፊያ መድረሱን ባልስልጣናት ገለፁ።

    የእስራኤል የትራንስፖርት ሚኒስቴር በቴሌግራም ገፁ ላይ በለጠፈው ጽሑፍ ላይ "ከጥቂት ደቂቃ በፊት የመጀመሪያው አውሮፕላን በቤን ጉሪዮን አውሮፕላን ማረፊያ [እስራኤላውያንን ጭኖ] አርፏል” ብሏል።

    በኤል አል የሚተዳደረው አውሮፕላን ረቡዕ ማለዳ ላይ በእስራኤል ያረፈው በቆጵሮስ ላርናካ የነበሩ እስራኤላውያንን ጭኖ ነው።

    የትራንስፖርት ሚኒስትር ሚሪቭ ሬጌቭ “ሁሉንም እስራኤላውያን ወደ አገራቸው ለመመለስ” ዓላማ እንዳላቸው ተናግረዋል።

    በትናንትናው ዕለት የፖላንድ እና የቼክ ሪፐብሊክ ዜጎች እስራኤልንን ለቅቀው ወደ ሄዳቸው ተሰምቷል።

  19. ትናንት ሌሊት እስራኤል ቁልፍ ወታደራዊ ስፍራዎችን ስትደበድብ የኢራን ጥቃት ግን ቀንሶ ታይቷል

    በኢራን እና እስራኤል ግጭት ስድስተኛ ቀኑን ሲያስቆጥር ኢራን በእስራኤል ላይ ተጨማሪ ሚሳኤሎችን በማስወንጨፍ ምላሽ ስትሰጥ እስራኤል ደግሞ ተጨማሪ ጥቃቶችን በኢራን ላይ አድርሳለች።

    ዛሬ ማለዳ አካባቢ በቴህራን እና አካባቢው ከባድ ፍንዳታ ተሰምቷል።

    የእስራኤል አየር ኃይል ቁልፍ የሆነውን የሚሳኤል ማምረቻ ቦታ እና ከአብዮታዊ ጥበቃ ጓድ ጋር ግንኙነት ያለው አካዳሚ ላይ ድብደባ ፈጽሟል።

    ከሰዓታት በፊት የእስራኤል ጦር በቴህራን ወታደራዊ ሕንፃዎች እና የመኖሪያ ሰፈሮችን በሚገኙበት አካባቢ ነዋሪዎች ለቅቀው እንዲወጡ ትእዛዝ ሰጥቷል።

    ትናንት ለሊት ኢራን ሃይፐርሶኒክ ሚሳኤል ተጠቅሜአለሁ ስትል ከገለፀች በኋላ ለሊቱን በእስራኤልም የአየር ጥቃት ማንቂያ ደወሎች የተሰሙ ቢሆንም በሰው ሕይወት ላይ የደረሰ ጉዳት የለም።

    የኢራን ጥቃት መጠን ቀንሷል፣ ይህም የእስራኤል የአየር ጥቃት በኢራን ጦር ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖ አመላካች ነው።

  20. እስራኤል ትናንት ሌሊት በኢራን የዩራኒየም ማብላያ ላይ ጥቃት መሰንዘሯን ገለፀች

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል ትናንት ሌሊት በኢራን ዩራኒየም ማብላያ እና የመሣርያ ማምረቻ ተቋማትን መምታቱን ገለፀ።

    ቢቢሲ የእስራኤልን መንግሥት መረጃ ከገለልተኛ ወገን ማጣራት አልቻለም።

    በኢራን ጥቃት መውደማቸው የተገለፀው የዩራኒየም ማብላያዎች ናቸው።

    የበለፀገ ዩራኒየም ለኃይል አቅርቦት ወይንም የኒውክሌር ቦምብ ለማምረትም ይውላል።

    በኢራን ከምድር በታች የሚገኙት የዩራኒየም ማብላያዎች በናታንዝ የሚገኙ ሲሆን እስራኤል አርብ ዕለት በፈጸመችው ጥቃት “ሙሉ በሙሉ ካልወደሙ፤ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸዋል” ሲሉ የዓለም አቀፉ የኒውክሌር ተቆጣጣሪ ባለስልጣን ከፍተኛ ኃላፊ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    በዚህ ጥቃት “ከ50 በላይ የጦር አውሮፕላኖች በላይ” “በቴህራን የሚገኝ የዩራኒየም ማብላያ ተቋምን” ዒላማ አድርገው ደብድበዋል።

    ከዚህም በተጨማሪ “በርካታ ጦር መሣርያ ማምረቻ ተቋማት. . . ጥሬ እቃ የሚያመርቱ እና ምድር ለምድር ለሚምዘገዘጉ ሚሳዔሎች ተገጣጣሚዎችን የሚያመርቱ” ፋብሪካዎች መመታታቸውን መከላከያ በመግለጫው ላይ ጠቅሷል።