የሁለቱ አገራት ግጭት ተባብሶ በእስራኤል እና ኢራን መካከል የአየር ጥቃት ልውውጡ ቀጥሏል።
ትናንት ምሽት ጥቃት ያደረሱት የኢራን ሚሳዔሎች በርካታ ጉዳት ማድረሳቸው ተሰምቷል።
የእስራኤል የአደጋ ጊዜ አገልግሎት በጥቃቱ ቢያንስ 10 ሰዎች ሲገደሉ፤100 የሚሆኑ ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸውን አሳውቋል።
ከጥቂት ቀናት በፊት በመንግሥታቱ ድርጅት የኢራን አምባሳደር በእስራኤል ጥቃት 78 ሰዎች መገደላቸውን ተናግረዋል።
ትናንትና የኢራን ብሔራዊ ቴሌቭዥን በቴህራን በአንድ የመኖሪያ አፓርትመንት ላይ በደረሰ ጥቃት 20 ሕፃናትን ጨምሮ 60 ሰዎች መገደላቸውን ዘግቧል።
የኢራን ነዳጅ ሚኒስቴር በዋና ከተማው የሚገኘው የሳህራን ነዳጅ ማከማቻ በእስራኤል ጥቃት መመታቱን ገልጿል።
የነዳጅ ማቀነባበሪያው በጥቃቱ የእሳት አደጋ ቢደርስበትም አሁን በስራ ላይ መሆኑ ተሰምቷል።
በባትያም እስራኤል የሚገኘው ዘጋቢያችን ባለ 10ኛ ወለል ሕንፃ ፍርራሽ ውስጥ ሰባት ሰዎች መውጫ ማጣታቸውን ዘግቧል።
ከዚህ አስቀድሞ የኢራን ሚሳኤል በአደጋ ዞን ውስጥ የሚገኝን ሕንፃ መምታቱን ተከትሎ ስድስት ሰዎች መገደላቸውን ሰምተናል።
በኢራን የደረሰውን የጉዳት መጠን አናውቅም።
ከእስራኤል የአየር ጥቃት በኋላ ምን ያህል ጉዳት እንደደረሰ የሚያመላክቱ መረጃዎች አልሰማንም።
የአየር ጥቃቶቹ በቴህራን መሰረተ ልማቶች እና የነዳጅ ማከማቻዎች ላይ ያደረሱትን ጉዳትም አናውቅም።
በኢራን መንግሥት እግድ ምክንያት የቢቢሲ ጋዜጠኞች ወደ አካባቢው መግባት አይችሉም።
ይህም በእስራኤል ጥቃት የደረሰውን ጉዳት ለማወቅ ከባድ ያደርገዋል።
የኢራን ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን እስራኤል ላይ የሚደርሰው ጥቃት ላይ በማተኮር በእስራኤል ኢራን ላይ ስላደረሰችው ጥቃት አነስተኛ ሽፋን እየሰጡ መሆኑን የቢቢሲ ሞንተሪንግ ዘጋቢ ሳራ ጃላሊ ገልፃለች።
ይህም ማለት ኢራን በእስራኤል እየፈፀመች ባለችው የአየር ጥቃት ተከታታይ መረጃዎችን እያገኘን ሲሆን፤ በአንፃሩ እስራኤል በኢራን ላይ በምታደርሰው ጥቃት ምን ያህል ጉዳት እየደረሰ እንደሆነ እየተገለፀ አይደለም።