በጋዛ ከተኩስ አቁም ፋታው በኋላ 200 ፍልስጤማውያን በእስራኤል ጥቃት ተገደሉ

ለሰባት ቀናት የቆየውን የጋዛ የተኩስ አቁም ፋታ ተከትሎ 200 ፍልስጤማውያን በእስራኤል ጥቃት መገደላቸውን በሐማስ አስተዳደር ስር ያለው የጋዛ የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል። እስራኤል እየፈጸመችው ባለው ጥቃት ከ15 ሺህ በላይ ፍልስጤማውያን ሲገደሉ 6 ሺህ ህጻናት መሆናቸውን ሚኒስቴሩ ገልጿል።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ባይደን ታጋቾችን ለማስለቀቅ የተደረሰውን ስምምነት አወደሱ

    ባይደን እና ኔታኒያሁ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ጆ ባይደን “ለሳምንታት በእስር እና በቃላት ሊገለጽ የማይችል መከራ” ሲያሳልፉ ከነበሩ ታጋቾች መካከል አንዳንዶቹ ከቤተሰቦቻቸው ጋር ሊቀላቀሉ መሆኑ “በጣም አስደስቶኛል” ብለዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት የኳታር እና የግብጽ መሪዎች ስምምነቱ እንዲደረስ ላሳዩት "ወሳኝ አመራር እና አጋርነት" አመስግነዋቸዋል።

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ለጦርነቱ ፋታ ለመስጠት ላሳዩት “ቁርጠኝነት” አድናቆታቸውን ችረዋቸዋል።

    "የዚህ ስምምነት ሃሳቦች ሙሉ በሙሉ መተግበራቸው አስፈላጊ ነው" ሲል አጽንኦት ሰጥተዋል።

    በስምምነቱ መሠረት በርካታ ሰብዓዊ ድጋፍ ወደ ጋዛ እንዲገባ በማገዛቸውም ኔታንያሁን አመስግነዋቸዋል።

    “ይህም በጋዛ የሚገኙ ንጹሐን ፍልስጤማውያን ቤተሰቦችን ያግዛል” ብለዋል።

    በመቶዎች የሚቆጠሩ መድኃኒት እና ነዳጅ የጫኑ ተሽከርካሪዎች በስምምነቱ መሠረት ጋዛ እንዲገቡ ይፈቀድላቸዋል።

  2. የእስራኤል ካቢኔ የታገቱትን ነጻ ለማውጣት የተደረሰውን ስምምነት አፀደቀ

    የታጋች ቤተሰብ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የእስራኤል ካቢኔ በሐማስ ታግተው የሚገኙ 50 ሰዎችን ነጻ ለማውጣት የተደረሰውን ስምምነት አጸደቀ።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚንስትር ጽህፈት ቤት 50 ታጋቾች በአራት ቀናት ውስጥ እንደሚለቀቁ አስታውቋል።

    በምላሹ እስራኤል የተኩስ አቁም ለማድረግ ተስማምታለች።

    በስምምነቱ መሠረት በመጀመሪያዎቹ አራት ቀናት ከሚለቀቁ 50 ታጋቾች በተጨማሪ “10 ታጋቾች በተለቀቁ ቁጥር አንድ ተጨማሪ የተኩስ አቁም ቀን ይኖራል” ተብሏል።

    ሐማስ መስከረም 26 በእስራኤል ላይ ድንገተኛ ጥቃት ፈጽሞ ከ230 ያላነሱ ሰዎችን አግቶ መውሰዱ ይታወሳል።

    ሐማስ እና እስራኤል በደረሱት ስምምነት መሠረት በቅድሚያ ታግተው የሚገኙ ሴቶች እና ሕጻናት ነጻ ይወጣሉ ተብሏል።

  3. ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ "ታጋቾች ነጻ ይወጣሉ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ" አሉ

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚንስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል ጠቅላይ ሚንስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ ታጋቾችን ለማስለቀቅ በሚደረገው ጥረት በቅርቡ መልካም ዜና እጠብቃለሁ አሉ።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጋዛ የሚገኙ ታጋቾችን በተመለከተ “መልካም ዜና ይኖራል ብዬ ተስፋ አድርጋለሁ” ስለማለታቸው ዘግቧል።

    ሐማስ መስከረም 26/2016 ዓ.ም. በእስራኤል ላይ ድንገተኛ ጥቃት አድርሶ ከ240 ያላሱ ሰዎች አግቶ ወደ ጋዛ መውሰዱን እስራኤል አሳውቃለች።

    ሐማስ እነዚህ ታጋቾች እንዲለቅ፣ እስራኤልም በበኩሏ የተኩስ አቁም እንድታደርግ የባሕረ ሰላጤዋ አገር ኳታር ስታደራድር ቆይታለች።

    ከዚህ ድርድር መልካም ውጤት እንደሚጠብቁ የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ገልጸው ነበር።

    የሐማስ መሪም እንዲሁ ከእስራኤል ጋር ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ለማድረግ ወደ ስምምነት ተቃርበናል ብለዋል።

  4. በሐማስ የታገቱትን ነጻ የማውጣት ድርድር ከጫፍ ድርሷል - የኳታር አደራዳሪ

    ኳታር

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    ሐማስ በእስራኤል ላይ ድንገተኛ ጥቃት አድርሶ ያገታቸውን ሰዎች ለማስለቀቅ እየተደረገ ያለው ድርድር በስምምነት ሊቋጭ ከጫፍ መድረሱን የኳታር አደራዳሪ ገለጹ።

    የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ማጂድ አል-አንሳሪ ከስምምነት ለመድረስ ከጫፍ ደርሰናል ብለዋል።

    ኳታር ሐማስ የያዛቸውን ታጋቾች እንዲለቅ፤ እስራኤልም እየተጠየቀች ላለችው የተኩስ አቁም ስምምነት አዎንታዊ ምላሽ እንድትሰጥ እስራኤል እና ሐማስን ስታደራድር ቆይታለች።

    ቃል አቀባዩ “. . . ስምምነት ላይ ለመድረስ ተቃርበናል” ያሉ ሲሆን ድርድሩ አሁን ያለበትን ድረጃ “ወሳኝ እና የመጨረሻው” ላይ ነው ሲሉ ገልጸውታል።

    ኳታር በጠላትንት የሚተያዩት የእስራኤል እና የሐማስ ‘ወዳጅ’ እንዲሁም በሁለቱ ወገኖች እምነት የሚጣልባት አገር ሆና ብቅ ብላለች።

    ለመሆኑ ኳታር ምዕራባውያን አሸባሪ ያሉትን ሐማስ ለምን አስጠለለች? ማደራደሩስ ይሳካላታል? ዝርዝሩን እዚህ ያንብቡ ኳታር ምዕራባውያን አሸባሪ ያሉትን ሐማስ ለምን አስጠለለች? ማደራደሩስ ይሳካላታል?

  5. ሐማስ የእስራኤል የአየር ጥቃት መቆም የስምምነት አካል እንዲሆን ፍላጎት አለው ተባለ

    ሰው አልባ አውሮፕላን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የእስራኤል መገናኛ ብዙኃን በእስራኤል እና በሐማስ መካከል እየተደረገ ባለው ተኩስ የማቆም ንግግር ውስጥ እስራኤል በጋዛ የአየር ክልል ላይ መብረሯን እንድታቆም ሐማስ መጠየቁን ዘገቡ።

    ዋላ የተሰኘ መገናኛ ብዙኃን በጋዛ የሚገኙት የሐማስ መሪ ያህያ ሲንዋር እስራኤል በጋዛ የአየር ክልል ላይ ሙሉ በሙሉ በረራዋን እንድታቆም ጠይቀዋል ያለ ሲሆን፣ ያኔት የተባለ የዜና ድረ-ገጽ ደግሞ እስራኤል በሰሜን ጋዛ ላይ ብቻ በቀን ለስድስት ሰዓታት ለመብረር እንድትስማማ ሐማስ ጥረት እያደረገ ነው ሲል ዘግቧል።

    እስራኤል በጋዛ ላይ በምድር፣ በአየር እና በባሕር ጥቃቶች እየፈጸመች ሁለት ወራት ሊሞላት የተቃረበች ሲሆን፣ አስካሁን ጋዛ ውስጥ ከፍተኛ ውድመት እያደረሰ ያለው የአገሪቱ አየር ኃይል ጥቃት ነው።

    እስራኤል ከተዋጊ አውሮፕላኖች በተጨማሪ በውል የማይታቁ የስለላ እና ጥቃት አድራሽ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን (ድሮኖች) በጋዛ አሰማርታ ቆይታለች።

  6. እስራኤል በደቡብ አፍሪካ ያሉትን አምባሳደሯን ‘ለምክክር’ ጠራች

  7. በሐማስ እና እስራኤል መካከል ይደረሳል የተባለው የጊዜያዊ ተኩስ አቁም ስምምነት ምንን ይዟል?

    የጋዛ ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, EPA-EFE/REX/Shutterstock

    የሐማስ መሪ ከእስራኤል ጋር ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ለማድረግ ወደ ስምምነት መቃረቡን ባወጡት መግለጫ አስታውቀዋል።

    እስራኤል በጉዳዩ ላይ የሰጠችው አስተያየት የለም። እንደ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ስምምነቱ የሚከተሉትን ሊያካትት ይችላል።

    • ኢስማኢል ሃኒዬ ጊዜያዊ የተኩስ አቁሙ ምን ያህል ጊዜ እንደሚቆይ አልተናገሩም ነገር ግን እየተካሄደ ያለው ድርድር ጊዜያዊ የተኩስ አቁሙ ለምን ያህል ጊዜ እንደሚቆይ፣ እርዳታ ወደ ጋዛ ለማድረስ እና ታጋቾችን በፍልስጤማዊ እስረኞች መለዋወጥ ላይ ያተኮረ እንደሆነ ተናግረዋል። ሁለቱም አካላት ሴቶችን እና ህጻናትን ያካትታሉ ብሏል።
    • የስምምነቱ ዝርዝር ሁኔታ በሃማስ እና በእስራኤል መካከል አሸማጋይ በነበረችው ኳታር ይፋ እንደሚሆንም ተናግረዋል።
    • የእስራኤል ጦር በጋዛ ሰርጥ ያለውን ውጊያ ለአምስት ቀናት እንዲያቆም እንዲሁም በደቡባዊ ጋዛ ላይ የእስራኤል የአየር እንቅስቃሴን የሚገድብ።
    • የፍልስጤም ቡድኖች ከ50-100 ታጋቾችን የሚለቁ ሲሆን እነዚህም የእስራኤል ሰላማዊ ዜጎች፣ የሌላ አገር ተወላጆች የሚሆኑ ሲሆን ነገር ግን ወታደሮች አይሆኑም።
    • በምላሹም እስራኤል ሴቶች እና ህጻናትን ጨምሮ 300 ፍልስጤማውያንን ከእስር ቤቶቿ የምትለቅ ይሆናል። አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ስማቸው ያልጠቀሳቸውን የሐማስ፣ እስላማዊ ጂሃድ ባለስልጣናትን ዋቢ አድርጎም ድርጅቶቹ በስምምነቱ ሐሳብ መስማማታቸውን ዘግቧል።
  8. ሰባተኛ ሳምንቱን በያዘው የጋዛ ጦርነት አዳዲስ ክሰተቶች

    የጋዛ ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    • የሐማስ መሪ ከእስራኤል ጋር ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ለማድረግ ወደ ስምምነት መቃረቡን ባወጡት መግለጫ አስታውቀዋል።
    • ኢስማኢል ሃኒዬ ጊዜያዊ የተኩስ አቁሙ ምን ያህል ጊዜ እንደሚቆይ ባይናገሩም ነገር ግን ለአልጀዚራ እንደተናገሩት ድርድሩ ለምን ያህል ጊዜ እንደሚቆይ፣ እርዳታ ወደ ጋዛ ለማድረስ እና ታጋቾችን በፍልስጤማዊ እስረኞች መለዋወጥ ላይ ያተኮረ እንደሆነ ተናግረዋል።
    • የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት ታጋቾችን ለመልቀቅ ሲደረግ የነበረው ውይይት ወደ ስምምነት መቃረቡን ነው።
    • የቢቢሲ የመካከለኛው ምስራቅ ጋዜጠኛ ቶም ባትማን ታጋቾችን ደረጃ በደረጃ የሚለቁበትን ሁኔታ እንደሚመለከቱም ተናግሯል።
    • እስራኤል በማዕከላዊ ጋዛ በሚገኘው ኑሴራት የስደተኞች ካምፕ ላይ ባደረሰችው የአየር ጥቃት ቢያንስ 17 ሰዎች መገደላቸውን የፍልስጤም የዜና ወኪል ዋፋ ዘግቧል። እስራኤል ጥቃቱን አስመልክቶ ያለችው ነገር የለም።
    • የጦርነቱ ማዕከል የሆነው የጋዛው የኢንዶኔዥያ ሆስፒታል ዳይሬክተር ተኩስ እስከ ምሽቱ ድረስ ቀጥሏል ብለዋል።
  9. ዓለም አቀፉ የወንጀል ፍርድ ቤት ኔታንያሁ ላይ የእስር ትዕዛዝ እንዲያወጣ ደቡብ አፍሪካ ጠየቀች

  10. ሐማስ እና እስራኤል 'ጊዜያዊ የተኩስ አቁም' ለማድረግ ወደ ስምምነት ተቃርበዋል ተባለ

    በጋዛ ቤተሰባቸውን ያጡ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ሐማስ እና እስራኤል ውጊያውን በጊዜያዊነት ለማቆም እና ታጋቾች እንዲለቀቁ ለማመቻት ወደ ስምምነት እንደተቃረቡ ሪፖርቶች እየወጡ ይገኛሉ።

    በኳታር አሸማጋይነት መሰረት ሁለቱ ወገኖች ውይይት ሲያደርጉም ቆይተዋል።

    የሐማስ መሪ እስማኤል ሃኒዬህ እንዳሉት ድርጅታቸው ምላሹን "በኳታር ላሉት ወንድሞቻችን እና ለአሸማጋዮች ሰጥቷል። ውጊያውን ለማቆም ስምምነት ላይ ለማድረስ ተቃርበናል" ሲሉም መናገራቸውን የዜና ወኪሎች እና የፍልስጠም የዜና አውታሮች ዘግበዋል።

    እስራኤል በጉዳዩ ላይ የሰጠችው ምላሽ የለም።

    የአሜሪካ ከፍተኛ ባለስልጣንም በሐማስ የተወሰዱ ታጋቾችን ለማስለቀቅ እየተደረገ ያለው ውይይት ወደ ስምምነት መቃረቡን እንዲሁም በምላሹም ውጊያውም በጊዜያዊነት እንዲገታ ሊደረግ መሆኑምም ሰኞ እለት ገልጸው ነበር።

  11. የጃፓን ዕቃ ጫኝ መርከብ ቀይ ባሕር ላይ በየመን ሁቲ አማጺያን ታገተ

  12. በጋዛ ያለጊዜያቸው ከተወለዱ 31 ጨቅላ ሕጻናት 28ቱ ብቻ ለምን ወደ ግብፅ ተላኩ?

    ያለጊዜያቸው የተወለዱ ጨቅላ ሕጻናት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በሰሜን ጋዛ ከሚገኘው አል ሺፋ ሆስፒታል እንዲወጡ ከተደረጉ 31 ያለጊዜያቸው የተወለዱ ጨቅላ ሕጻናት መካከል 28ቱ ብቻ ወደ ግብፅ ተላኩ።

    እነዚህ ጨቅላ ሕጻናት የእስራኤል ጦር ከተቆጣጠረው እና የሞት ቀጠና ከሆነው የጋዛ ትልቁ ሆስፒታል አል ሺፋ በሕይወት ተርፈው የወጡ ሲሆን፣ ወደ አል አህሊ ኤምሬትስ ሆስፒታል ተወስደው የነበሩ ናቸው።

    ከእነዚህ ሕጻናት መካከል አብዛኞቹ ለሕክምና ወደ ግብፅ የተላኩ ሲሆን፣ ጥቂቶቹ አሁንም ድረስ እዚያው ሆስፒታል ውስጥ ይገኛሉ።

    ይህ ለምን ሆነ ሲል ቢቢሲ በአል አህሊ ኤምሬትስ ሆስፒታል ውስጥ የጨቅላ ሕጻናት ክፍል ኃላፊ የሆኑትን ዶ/ር መሐመድ ሳላማን ጠይቋቸዋል።

    ዶ/ር መሐመድ የተወሰኑት የሕጻናቱ ወላጆች ልጆቻቸውን ለመለየት እሁድ ዕለት አል አህሊ ኤምሬትስ ሆስፒታል መድረሳቸውን ገልጸው፣ ልጆቻቸው ለሕክምና ወደ ግብፅ እንዲሄዱ የፈቃድ ፎርም እንዲሞሉ እንደጠየቋቸው እና ፈቃድ ያገኙትን መላካቸውን ተናግረዋል።

    “አሁን ላይ ማንነቱ ያልተለየ እና ወላጆቹ ያልታወቁ አንድ ሕጻን ይገኛል። ይህ ሕጻን አሁንም ከእኛ ጋር ነው ያለው ። ሕጻኑ በጥሩ የጤንነት ሁኔታ ላይ ስለሚገኝ እና ለሕክምና ወደ ሌላ ቦታ መሄድ ስለማያስፈልገው በጋዛ ጤና ሚኒስቴር ውሳኔ እዚህ እንዲቆይ ተደርጓል” ብለዋል።

    ሁለት ሌሎች ሕጻናት ደግሞ ወላጆቻቸው በግል ጉዳይ ምክንያት ለመላክ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ሳይላኩ የቀሩ መሆናቸውን ገልጸዋል።

    ዶክተር ሳላማ እንዳሉት ሦስቱም ሕጻናት በጥሩ ሁኔታ ላይ ይገኛሉ።

  13. የእስራኤል ታንኮች በሰሜናዊ ጋዛ ወደሚገኘው ሆስፒታል ገቡ

    የእስራኤል ታንኮች በሰሜን ጋዛ ወደሚገኘው የኢንዶኔዥያ ሆስፒታል ገቡ።

    እስራኤል ዛሬ ማለዳ በሆስፒታል ባደረሰችው ጥቃት ወደ 12 የሚጠጉ ሰዎች መገደላቸውም ተዘግቧል።

    ከጥቂት ሰዓታት በፊት የሆስፒታሉ ዳይሬክተር ዶ/ር ማርዋን አል ሱልጣን ለቢቢሲ እንደተናገሩት የእስራኤል ጦር ከሆስፒታሉ ህንጻ 20 ሜትሮች ያህል ርቀት ነበረው።

    በአካባቢው ከፍተኛ የተኩስ ድምጽ ይሰማ እንደነበር እና የቀዶ ጥገና ማገገሚያ ክፍል መመታቱን ተናግረው ነበር።

    የእስራኤል ጦር በቅርቡ በሰጠው መግለጫ በሆስፒታሉ ላይ ስላለው ነገር ምንም አላለም። "የእስራኤል መከላከያ ወታደሮች በጋዛ ሰርጥ የሚያደርጉትን ዘመቻ ቀጥለዋል። አውሮፕላኖቻችን አሸባሪዎች ላይ፣ አሸባሪዎች መሰረተ ልማት ላይ እንዲሁም የጦር መሳሪያዎቻችን እና ወታደራዊ ቁሳቁሶችን በማፈላለግ ስራቸውን ቀጥለዋል" ብሏል።

    የሐማስ ሶስት አዛዦችም ተገድለዋል ተብሏል። የሆስፒታሉ ዳይሬክተር እስራኤል ባደረሰችው የአየር ጥቃት ቢያንስ 10 ሰዎች መገደላቸውን ገልጸዋል።

    ጋዛ የጤና ሚኒስቴር በበኩሉ 12 ሰዎች መገደላቸውን ተናግሯል። የሚኒስቴሩ ቃለ አቀባይ አሽራፍ አል ቁድራ ለአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ የዜና ወኪል ከተገደሉት በተጨማሪም በርካቶች ቆስለዋል ብለዋል።

  14. ቻይና ከአረብ አገራት ሚኒስትሮች ጋር ተወያየች

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዋንግ ዩ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ቻይና ከአረብ አገራት ጋር ባደረገችው ውይይት የሁለት አገራት፣ የፍልስጤምና የእስራኤል መንግሥት ምስረታን እንደምትደግፍ አስታወቀች።

    ቻይና ይህንን ያስታወቀችው ከአረብ እና ሙስሊም አገራት የተወጣጡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ልዑካን በቻይና መደበኛ ጉብኝት እያደረጉ ባለበት ወቅት ነው።

    ሳዑዲ አረቢያ፣ ዮርዳኖስ፣ ግብጽ፣ ኢንዶኔዥያ እና ከፍልስጤም አስተዳደር እና የእስልምና ትብብር ድርጅት መሪን ያካተተ ልዑካን በቻይና ይገኛሉ።

    ጉብኝቱ ቻይና በጋዛ ያለውን ጦርነት ለማርገብ፣ ሰላማዊ ዜጎችን ለመጠበቅ እና የፍልስጤም ጥያቄ ፍትሃዊ በሆነ መንገድ የሚፈታበትን ሁኔታም ላይ ለመምከርም እንደሆነ የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዋንግ ዩ በቅርቡ በሪያድ በተካሄደው የአረብ እና ሙስሊም አገራት መሪዎች ጉባዔ ላይ የቀረበውን ጥሪ በመደገፍ አገራቸው የሁለት አገራት ምስረታን እንደ መፍትሄ እንደምታየው ተናግረዋል።

    አለም አቀፉ ማህበረሰብ 'በአፋጣኝ እርምጃ መውሰድ እንዳለበት እና የሰብዓዊ ጥፋቱም እንዲያከትም ውጤታማ እርምጃዎች መውሰድ አለበት' ሲሉም ተደምጠዋል።

    ሚኒስትሩ በመክፈቻ ንግግራቸውም " በጋዛ ያለውን ጦርነት ለማርገብ እና የመካከለኛውን ምስራቅ ሰላምንም በተቻለ ፍጥነት ለመመለስ በጋራ እንስራ" ሲሉም ለሚኒስትሮቹ ተናግረዋል።

    ቻይና በጋዛ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረግ በቀዳሚነት ጥሪ ካቀረቡ አገራት መካከል ስትሆን ቀደም ሲልም ውይይትን ለማበረታት እና ሰላምንም ለማስፈን አስፈላጊውን ሁሉ ለማድረግ ፈቃደኛ መሆኗንም ስትናገር ቆይታለች።

  15. ሰባተኛ ሳምንቱን በያዘው የጋዛ ጦርነት የተከሰቱ የቅርብ ጉዳዮች

    የጋዛ ጦርነት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    • 31 ያለጊዜያቸው የተወለዱ ጨቅላዎች ከአልሺፋ ሆስፒታል እሁድ ዕለት እንዲወጡ ተደርገው በደቡባዊ ራፋህ ከተማ ወደሚገኘው ኤምሬትስ ሆስፒታል ተወስደዋል።
    • የዓለም ጤና ድርጅት ኃላፊ ዶክተር ቴድሮስ አድኃኖም ገብረእየሱስ ጨቅላዎቹ "በጣም እንደታመሙ" እና በጣም በአስቸጋሪ እና በከፋ የጸጥታ ሁኔታ ውስጥ መወሰዳቸውንም ነው የተናገሩት።
    • በአልሺፋ ሆስፒታል የቀሩ ህሙማንን እና ሰራተኞችን ሙሉ በሙሉ ለማስወጣት የያዘውንም እቅድ በማጠናቀቅ ላይ መሆኑንም የዓለም ጤና ድርጅት አስታውቋል። ይህም በርካታ ቀናትን እንደሚፈጅ አስታውቆ በመጀመሪያውም የኩላሊት እጥበት እየተደረገላቸው ያሉ እና የአከርካሪ አጥንት ጉዳት ያለባቸውንም ማዛወር ይሆናል።
    • የእስራኤል ጦር በአልሺፋ ሆስፒታል ስር '55 ሜትር እርዝመት ያለው የሽብር ዋሻ" ያሳያል ያለችውን ቪዲዮ ለቋል። ጦሩ አግኜቻዋለሁ ያለውም ዋሻ በሆስፒታሉ ግቢ ውስጥ የሚገኙ በርካታ ህንጻዎች ሐማስ "ለሽብር ተግባር ሽፋንንት እንደሚጠቀምባቸው ያረጋግጣል" ብሏል። ሐማስም ሆነ የሆስፒታሉ ባለሙያዎች ይህንን ክስ አይቀበሉትም።
    • የእስራኤል መከላከያ ኃይል ሐማስ መስከረም 26 ካደረሰው ጥቃት በኋላ የወሰዳቸው ታጋቾች ወደ ጋዛ ትልቁ ሆስፒታል መወሰዳቸውን የሚያሳይ ነው ያለውን ከስፍራው የተቀረጸ ቪዲዮ (ሲሲቲቪ) አሳይቷል።
    • በኢራን የሚደገፉት የየመን ሁቲ አማጽያን የእስራኤልን የጭነት መርከብ በቀይ ባህር መያዛቸውን ያስታወቁ ሲሆን የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ "ሌላ የኢራን የሽብር ተግባር" ሲሉ ጠርተውታል። እስራኤል በጋዛ ላይ የምታደርሰውን የአየር ጥቃት ተከትሎ የሁቲ አማጽያን ወደ እስራኤል በርካታ ሚሳኤሎችን እና ድሮኖችን አስወንጭፈዋል።
  16. ታጋቾች ወደ ጋዛ ሆስፒታል መወሰዳቸውን ከስፍራው የተገኘ ቪዲዮ ማሳየቱን እስራኤል አስታወቀች

  17. ተመድ በጋዛ ያሉ ትምህርት ቤቶቹ ላይ የደረሰው ጥቃት በከፍተኛ ሁኔታ አስደንግጦኛል አለ

    የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሓፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሓፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ በጋዛ ሰርጥ 24 ሰዓት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ሁለት የመንግሥታቱ ድርጅት ትምህርት ቤቶች ላይ ጥቃት መፈጸሙ 'በከፍተኛ ሁኔታ እንዳስደነገጣቸው' ተናገሩ።

    "በርካቶች፣ አብዛኛዎቹ ህጻናት እና ሴቶች ተገድለዋል። በተባበሩት መንግሥታት ግቢ ውስጥ ደህንነትን ሽተው የተጠለሉ ነበሩ" ሲሉም ጉቴሬዝ በመግለጫቸው አክለዋል።

    "ተጠናክሮ በቀጠለው ውጊያ ምክንያት በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ፍልስጤማውያን በተባበሩት መንግሥታት ማዕከላት ተጠልለው ይገኛሉ። ግቢያችን መጣስ እንደማይገባው በድጋሚ አረጋግጣለሁ" ሲሉም ተናግረዋል።

    ጦርነቱ አስከፊ መሆኑን የገለጹት ዋና ጸሓፊው የሰላማዊ ሰዎች ግድያም ከፍተኛ መሆኑን ተከትሎም "ተቀባይነት የሌለው" ሲሉ ገልጸውታል። አፋጣኝ የሆነ ሰብዓዊ የተኩስ አቁምም እንዲደረግም ጥሪያቸውን አቅርበዋል።

  18. በጋዛ የተገደሉ ፍልስጤማውያን ቁጥር 13 ሺህ ደረሰ- የጋዛ ጤና ሚኒስቴር

    በጋዛ የተገደሉ ፍልስጤማውያን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ሰባተኛ ሳምንቱን በያዘው የጋዛው ጦርነት በእስራኤል የተቀናጁ ጥቃቶች የተገደሉ ፍልስጤማውያን ቁጥር 13 ሺህ መድረሱን የጋዛ ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።

    ከነዚህም ውስጥ 70 በመቶዎቹ ህጻናት እና ሴቶች መሆናቸውን የተባበሩት መንግሥታት እንዲሁም በሐማስ አስተዳደር ስር ያለው ሚኒስቴሩ ገልጿል።

    ሐማስ መስከረም መጨረሻ ላይ ባደረሰው ጥቃት 1 ሺህ 200 ሰዎች ሲገደሉ፤ 200 ታጋቾች ተወስደዋል።

    እስራኤል ምላሽ ነው ባለችው የማያባራ ጥቃት እየፈጸመች ሲሆን የጋዛ ሰርጥንም በሙሉ ከበባ ውስጥ አስገብታታለች። መብራት፣ ውሃ እና መሰረታዊ አገልግሎቶች ተቋርጠዋል።