በኢትዮጵያ ተጨማሪ 142 ሰዎች በኮቪድ-19 ሲያዙ 3 ደግሞ ሕይወታቸው አልፏል
የጤና ጥበቃና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ዛሬ ባወጡት ዕለታዊ ሪፖርት ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ ምርመራ ከተደረገላቸው 4120 ሰዎች ውስጥ 142ቱ ኮቪድ-19 እንዳለባቸው ተራጋግጧል።
ዛሬ ኮሮናቫይረስ የተገኘባቸው ሰዎች 84ቱ ወንዶች 57ቱ ደግሞ ሴቶች ሲሆኑ እድሜያቸውም ከ7 ዓመት አስከ 78 ባለው ውስጥ የሚገኙ ናቸው።
140ዎቹ ኢትዮጵያዊያን ሲሆኑ አንድ ሰው ከፖርቹጋል፤ አንድ ሰው ደግሞ ከጅቡቲ መሆናቸው ታውቋል።
ባለፉት 24 ሰዓታት ቫይረሱ እንዳለባቸው ከተረጋገጠ 142 ሰዎች መካከል 126 ከመዲናዋ አዲስ አበባ ናቸው።
ከቫይረሱ ጋር በተያያዘ ተጨማሪ ሦስት ሰዎች ሕይወታቸው ማለፉም ተሰምቷል። አጠቃላይ የሟቾች ቁጥርም 17 ደርሷል።
እስከ ዛሬ በተደረገው ከ120 ሺህ 429 የኮሮናቫይረስ ምርመራ 1486 ሰዎች ላይ የኮቪድ-19 ቫይረስ ተገኝቷል።












