በኢትዮጵያ 150 ሰዎች ኮሮናቫይረስ ሲገኝባቸው የአንድ ሰው ህይወት አለፈ

በኢትዮጵያ ቫይረሱ የሚገኝባቸው ሰዎች ቁትር ከዕለት ዕለት በፍጥነት እየጨመረ ነው። በተለይ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ያለው የቫይረሱ መስፋፋት በጣም ከፍተኛ እንደሆነ በየዕለቱ የሚወጣው መረጃ ያመለክታል። በዚህም በአገሪቱ እስካሁን ከተመዘገበው 1637 የህሙማን ቁጥር ውስጥ ከአንድ ሺህ የሚበልጡት ከአዲስ አበባ የተገኙ ናቸው። አሁንም የቫይረሱ ስርጭት ባለበት እንዲቆም እጅን በሚገባ መታጠብ፣ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ፣ አካላዊ ርቀትን መጠበቅ በባለሙያዎችና በመንግሥት የሚመከሩ መከላከያዎች ናቸው። ከኮሮናቫይረስ ጋር የተያያዙ የቀጥታ ዘገባዎቻችንን እዚህ ገጽ ላይ ይከታተሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በግብጽ ኮሮናቫይረስን ተገን አድርጎ ልጆቹን ያስገረዘው አባት ተከሰሰ

    ግርዛት

    የግብጽ አቃቤ ሕግ አንድ አባት ሶስት ሴት ልጆቹን የኮሮናቫይረስ ሕክምና እየተከታተሉ ነው በሚል ሽፋን በማስገረዙ ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ተጠየቀ።

    አባትና ግርዛቱን የፈፀመው ዶክተር ጉዳያቸው ወደ ወንጀል ችሎት ተመርቷል።

    የልጆቹን መገረዝ ለፖሊስ ያመለከተችው እናታቸው ናት።

    እናትየው ከአባታቸው ጋር የተፋታች ሲሆን፣ አባት ልጆቹን "የኮሮናቫይረስ መከላከያ ክትባት ትከተባላችሁ" በሚል ወደ ክሊኒኩ እንደወሰዳቸው ተናግራለች።

    በክሊኒኩ ውስጥ ማደንዘዣ ከተወጉ በኋላ መገረዛቸው ተገልጿል።

    በግብጽ ከጎርጎሳውያኑ 2008 ጀምሮ የሴት ልጅ ግርዛት ቢከለከልም አሁንም ግን በሰፊው ይተገበራል።

  2. በሴኔጋል ተቃውሞን ተከትሎ የሰዓት እላፊ አዋጁ ተሻሻለ

    በሴኔጋል የነበረው ተቃውሞ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በሴኔጋል ለሁለት ቀናት ያህል የተደረገውን ተቃውሞ ተከትሎ የሰዓት እላፊ አዋጁና በከተሞች ውስጥ የተጣለው የጉዞ እገዳ እንደሚሻሻል ተገልጿል።

    ለተቃውሞ ከወጡት መካከል 200 የሚሆኑት በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለዋል።

    የተቃውሞ ሰልፉ በሴኔጋላውያን ዘንድ ቅድስት ተብላ በምትጠራው ቱልባ ከተማ ተጀምሮ ወደሌሎች ከተሞች ተስፋፍቷል።

    የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት በሚል አገሪቷ ከመጋቢት ወር ጀምሮ የሰዓት እላፊ መመሪያን ደንግጋለች።

    የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር አሊ ንጉሊ ንዳየ በዛሬው እለት እንዳሳወቁት የሰዓት እላፊው በሁለት ሰዓት ተገፍቷል። በዚህም መሰረት ከምሽቱ ሶስት ሰአት የነበረው ወደ አምስት ሰዓት የተገፋ ሲሆን እስከ አስራ አንድ ሰዓትም መንቀሳቀስ የተከለከለ ነው።

    ከዚህም በተጨማሪ በትራንስፖርት ዘርፉም ተጥሎ የነበረው መመሪያም ተሻሽሏል። ሬስቶራንቶች፣ የስፖርት ማዘውተሪያዎችና አንዳንድ የንግድ ቦታዎችም የሚከፈቱ ይሆናል።

    ሴኔጋል ትምህርት ቤቶችን በተወሰነ መልኩ ለመክፈት አቅዳ የነበረ ቢሆንም አንዳንድ መምህራን በኮሮናቫይረስ መያዛቸው በመረጋገጡ ላልተወሰነ ጊዜ ተራዝሟል።

  3. ከሰመመን ሲነቃ ፈረንሳይኛን አቀላጥፎ መናገር የቻለው የማንችስተር ተጫዋች

  4. በአዲስ አበባ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች 1,205 ደረሱ

    ጭምብል ያጠለቁ ሰዎች በአዲስ አበባ ጎዳናዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በአዲስ አበባ ከተማ እስከ ዛሬ ግንቦት 27 2012 ዓ.ም ድረስ በተደረጉ የላብራቶሪ ምርመራዎች 1,205 ሰዎች የኮሮናቫይረስ እንደተገኘባቸው የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ አስታወቀ።

    ባለፉት 24 ሰዓታት ቫይረሱ የተገኘባቸው 123 ሰዎች ሲሆኑ ከእነዚህ መካከል ስምንት ሰዎች የውጭ አገር የጉዞ ታሪክ ያላቸው፣ 12 ሰዎች በቫይረሱ ከተያዙ ሰዎች ጋር ግንኙነት ያላቸው የተቀሩት 103 ሰዎች ደግሞ የውጭ አገር ጉዞ ታሪክም ሆነ በቫይረሱ ከተያዘ ሰው ጋር ግንኙነት የሌላቸው መሆናቸውን ቢሮው አስታውቋል።

    በአጠቃላይ በቫይረሱ ከተያዙ 1,205 ሰዎች መካከል 355 ሰዎች የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ነዋሪ ሲሆኑ፣ ልደ 180፣ ጉለሌ 157 ሰዎች ኮቪድ-19 እንደተገኘባቸው የጤና ቢሮው መረጃ ያሳያል።

  5. በፕሪሚየር ሊጉ ጨዋታዎች ላይ አምስት ተቀያሪ ተጫዋቾች እንዲገቡ ተፈቀደ

    ተጫዋች ቅያሪ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በዚህ አመት በሚደረጉ ቀሪ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታዎች ላይ ቡድኖች ሌላ ሕግ እስኪያወጡ ድረስ ከዚህ በፊት የነበረው ሶስት ተቀያሪ ተጫዋቾችን ማስገባት ቀርቶ አምስት እንዲሆን ተወሰነ።

    ቡድኖች ከዚህ በፊት ሰባት ተቀያሪ ተጫዋቾችን ማሳወቅ የነበረባቸው ሲሆን አሁን ግን ዘጠኝ እንዲያሳውቁ ተፈቅዷል።

    የዓለም አቀፍ እግር ኳስ ሕግ አውጪዎች ተቀያሪዎችን የመጨመር አማራጭ የሰጡ ሲሆን ይህም የተጫዋቾቹን ደህንነት ለመጠበቅ ነው ተብሏል።

    የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ከሶስት ወር በኋላ ሰኔ 10 ይጀመራል ተብሏል።

    ቡድኖቹ ምንም እንኳ አምስት ተቀያሪዎችን እንዲያደርጉ ቢፈቀድም ሁሉም ቡድኖች በጨዋታዎቹ ወቅት የተቀያሪዎቻቸውን ዝርዝር ለመቀየር ሶስት እድል ብቻ ይኖራቸዋል።

    ቡድኖች ጨዋታ ለማድረግ አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ገለልተኛ ሜዳን ለመጠቀም የተስማሙ ሲሆን ነገር ግን በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት አብዛኛዎቹ ጨዋታዎች በሜዳቸው እንደሚካሄድ ተገልጿል።

    እያንዳንዱ ጨዋታ ሲካሄድ በስታዲየም ውስጥ የሚገኙት ሰዎች ብዛት ከ300 እንደማይበልጥ ስምምነት ላይ ተደርሷል።

  6. የሊባኖስ መንግሥት ለኢትዮጵያውያን ሰራተኞች መጠለያ አሰጣለሁ አለ

    ሊባኖስ

    የፎቶው ባለመብት, This is Lebanon/FB page

    የሊባኖስ ሠራተኛ ሚኒስቴር አሰሪዎቻቸው ደሞዛቸውን ሳይከፍሏቸው ላባረሯቸው ኢትዮጵያውያን የቤት ሠራተኞች መጠለያ ሊሰጥ ነው።

    35 ኢትዮጵያውያን ቤሩት በሚገኘው የኢትዮጵያ ቆንስላ ፊት ለፊት ተቃውሟቸውን ሲያሰሙ ከሕዝቡ የቀረበውን ስሞታ ተከትሎ የሊባኖስ ባለሰልጣናት ሆቴል ውስጥ እንዲጠለሉ አድርገው ነበር።

    ከዚያ በኋላ ግን የሊባኖስ ምጣኔ ሃብት በመጎዳቱ ምክንያት ችግር ሲበረታ፣ በርካታ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በቆንስላው በር ላይ መሰብሰብ መጀመራቸው ተዘግቧል።

    የሊባኖስ ባለስልጣናት ደሞዛቸውን በማይከፍሉ ቀጣሪዎች ላይ እርምጃ ለመውሰድ ቃል ገብተዋል።

    ባለፈው ወር በርካታ ኢትዮጵያውያን ወደ አገራቸው ተመልሰዋል።

    በሊባኖስ ከ400 ሺህ በላይ ኢትዮጵያውያን የቤት ሠራተኞች መኖራቸው ሲገለጽ ከእነዚህ መካከል 300 ሺህ ያህሎቹ በሕገወጥ መልኩ የሚሰሩ ናቸው።

    በሊባኖስ በኮሮናቫይረስ ከተያዙ ሰዎች መካከል ኢትዮጵያውያን ይገኙበታል።

  7. የአፍሪካ ሕብረት የሚመረመሩ ሰዎችን 10 ሚሊዮን የማድረስ እቅድ ይዟል

    የኮቪድ-19 ምርመራ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የአፍሪካ ሕብረት በመላ አህጉሪቱ ኮቪድ-19 የሚመረመሩ ሰዎችን ቁጥር ለመጨመር እቅድ ይዟል።

    ዓላማው በሚቀጥሉት ሁለትና ሶስት ወራት የሚመረመሩ ሰዎች ቁጥርን 10 ሚሊዮን ማድረስ ነው።

    የአፍሪካ በሽታ መቆጣጠር እና መከላከል እስካሁን ድረስ 2.4 ሚሊዮን ምርመራዎች መካሄዳቸውን ጠቅሷል።

    በአፍሪካ አስካሁን ድረስ 160 ሺህ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን ከእነዚህም መካከል 4ሺህ 600 ሰዎች ሞተዋል።

    ነገር ግን ባለሙያዎች በአፍሪካ ያለውን አነስተኛ ምርመራ በመጥቀስ በርካታ ቫይረሱ ያለባቸው ሰዎች ሳይመረመሩ እንዳይቀሩ ይሰጋሉ።

    በቀጣዮቹ ሳምንታት ይህንን ቁጥር በሶስት እጥፍ የማሳደግ እቅድ ያለ ሲሆን ይህም ማለት ከመላው የአፍሪካ ሕዝብ አንድ በመቶ ያህሉ ይመረመራል ማለት ነው።

    ይህም የአፍሪካ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ስርጭት አጠቃላይ ምስል ያሳያል ተብሏል።

    በተለያዩ የአፍሪካ አገራት የምርመራ የተደናቀፈው በቂ መመርመሪያ መሳሪያ ባለመኖሩ ነው።

    አሁን ግን የአፍሪካ ሕብረት ለሁሉም አገራት እኩል የመመርመሪያ መሳሪያ ለመስጠት እቅድ ይዟል።

    የሕብረቱ እቅድ 100 ሺህ ኮሮናቫይረስን የሚያክሙ የጤና ባለሙያዎች ማሰልጠንና ሚሊዮኖችን ንክኪ መለየት እንዲችሉ ወደ ማህበረሰቡ ውስጥ ለማሰማራት እቅድ ይዟል።

  8. ላይቤርያ የሰዓት እላፊውን የጣሱ ዜጎቿን ኮሮና ልትመረምር ነው

    ላይቤርያ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የላይቤርያ ባለስልጣናት የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመከላከል የወጣውን ሰዓት እላፊ የጣሱ ግለሰቦች አስገዳጅ የኮቪድ-19 ምርመራ ሊደረግላቸው ነው።

    የሰዓት እላፊው የተጣለው ከምሽቱ 1 ሰዓት እስከ ንጋቱ 12 ሰዓት ድረስ ነው።

    የአገሪቱ ጤና ሚኒስትር ለሬዲዮ ጣብያ በሰጡት ቃለ ምልልስ ላይ እንዳሉት ደንቡን ተላልፈው ከሚገኙ ሰዎች " ናሙና እንወስዳለን የጤንነት ሁኔታቸውን እንመረምራለን" ብለዋል።

    አክለውም የመንጃ ፈቃዳቸው እንደሚታገድ ገልፀዋል።

    የላይቤርያ መንግሥት በርካታ የምርመራ ጣብያዎችን እንዳቋቋመ ቢናገርም በርካቶች ግን ለመመርመር ፈቃደኞች አይደሉም ተብሏል።

    ላይቤርያ እስካሁን ድረስ 300 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን በምርመራ ስታረጋግጥ ከእነዚህም መካከል 28 ሰዎች ሞተዋል።

  9. በቻይና 12 ሺህ ሲኒማ ቤቶች የመዘጋት ስጋት ተጋርጦባቸዋል

  10. በኢትዮጵያ ሚሊዮኖች ሥራ ሊያጡ እና የአገር ውስጥ ምርት እድገት 11.2 በመቶ ሊቀንስ ይችላል

  11. የዛሬው አለም አቀፉ የክትባት ጉባኤ ምንን ሰንቋል?

    ክትባት የሚሰጠው ህፃን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በዩናይትድ ኪንግደም አዘጋጅነት አለም አቀፍ የክትባት ጉባኤ እየተካሄደ ነው።

    ከአምሳ በላይ ሃገራት መሪዎች እንዲሁም አለም አቀፍ ኩባንያዎችና የናጠጡ ሃብታሞች እየተሳተፉበት ነው ።

    አላማው ምን ይሆን ?

    • ጋቪ ለተባለው የክትባት ጥምረት 7.4 ቢሊዮን ዶላር ለማሰባሰብ ታቅዷል። ጥምረቱ በአለም ላይ ያሉ ደሃ ሃገራት ላይ የክትባት አቅርቦት የሚሰራ ነው።
    • ከሶስት መቶ ሚሊዮን በላይ ህፃናት ተቅማጥ፣ ታይፎይድና ፖሊዮ ባሉ ተላላፊ በሽታዎች እንዳይጠቁ ለማድረግ በክትባት መልኩ የሰውነት የበሽታ የመከላከል አቅምን ለመጨመርም የሚሰራ ነው።
    • የኮሮናቫይረስ ክትባትም ከተሳካ ወደነዚህ ሃገራትም ለማሰራጨት ፈንድ የማሰባሰብ ስራ ለመስራትም ታቅዷል።
    • በአለም ላይ መድሃኒቶችን የሚያመርቱ ኩባንያዎችና የአለም መሪዎች ኮቪድ-19ን ለመከላከል ምን መስራት አለባቸው የሚለውንም እየመከረ ነው።

    ምንም እንኳን የኮሮናቫይረስ የአለም ስጋት ቢሆንም በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ህፃናት በተላላፊ በሽታዎች ሊሞቱ እንደሚችሉም ተገምቷል። በኮሮናቫይረስ ጫና ምክንያት በርካታ የክትባት ፕሮግራሞች ተቋርጠዋል።

    • የላቲን አሜሪካ ሃገራት ኮሮናቫይረስን እንዴት እየታገሉት ነው?

      በብራዚል ጭምብል ያጠለቀ ግለሰብ

      የፎቶው ባለመብት, Getty Images

      ሜክሲኮና ብራዚል በየእለቱ የሚመዘገበው የሟች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ ሲሆን ሌሎቹስ የላቲን አሜሪካ ሃገራትስ ኮሮናቫይረስ እንዴት እያደረጋቸው ነው?

      • በአርጀንቲና የኮሮናቫይረስን መዛመት ለመግታት ያስችል ዘንድ አሳልፋው የነበረውን አስገዳጅ የቤት መቀመጥ መመሪያ ለተጨማሪ ሁለት ሳምነት እንዲራዘም ተወስኗል። በዛሬው ዕለትም የሃገሪቱ ፕሬዚዳንት አልበርቶ ፈርናንዴዝ ያውጃሉ ተብሎ ይጠበቃል። ክፉኛ በቫይረሱ የተጠቁት መዲናዋ ቦነስ አይረስና አካባቢዋ ያሉት ከተሞች ናቸው። በትናንትናው ዕለት ከተመዘገቡት 949 በቫይረሱ ከተያዙት ሰዎችም ውስጥ አብዛኛዎቹ ከዚሁ አካባቢዎች ናቸው ተብሏል።
      • በፔሩ አስደሳች ዜና የተሰማ ሲሆን በኮሮናቫይረስ የተጠቃች የአምሳ አመት ሴት ጤነኛ መንታ ልጆችን በሰላም ተገላግላለች። በአጠቃላይ በሃገሪቱ ግን የህሙማን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን ሆስፒታሎችም የኦክስጅን እጥረት አጋጥሟቸዋል።
      • በፓራጉዋይ አንድ የምክር ቤት አባል በፓርላማ ጉባኤ ወቅት ሃገሪቷ ከብራዚል ጋር ያላትን ድንበር መዝጋቷን ለመቃወም ልብሳቸውን አውልቀዋል። የፓርላማ አባሉ ጆርጅ አንቶኒዮ ብሪቴዝ እንዳሉትም እሳቸው የሚወክሉት አካባቢ ከብራዚል ጋር ፅኑ ቁርኝት ያለውና በርካቶችም የእለት ጉርሳቸውን የሚያገኙት ከብራዚል ጋር በሚደረግ የንግድ ልውውጥ ነው።
      • ብራዚል በላቲን አሜሪካ ካሉ ሃገራት በቫይረሱ ክፉኛ የተጠቃች ሲሆን ጎረቤቷ ፓራጉዋይም ወደ ግዛቷ ቫይረሱ እንዳይዛመት በሚል ድንበሯን ከዘጋች ሁለት ወራት አልፏታል።
    • የጉዞ እቀባ የተነሳላቸው ጣሊያናዊያን በደስታ እየተቃቀፉ ነው

    • በኢትዮጵያ 150 ሰዎች ቫይረሱ ሲገኝባቸው የአንድ ሰው ህይወት አለፈ

      ሁለት ጭምብል ያጠለቁ ሰዎች በአዲስ አበባ ጎዳና

      የፎቶው ባለመብት, Getty Images

      በባለፉት ሃያ አራት ሰአታት ውስጥ በተደረገው 5141 የላብራቶሪ ምርመራ 150 ተጨማሪ ሰዎች የኮሮና ቫይረስ ተገኝቶባቸዋል።

      ከዚህ በተጨማሪም በዛሬው ዕለትም አንድ በፅኑ ህክምና ላይ የነበረ የ30 ዓመት ኢትዮጵያዊም ህይወቱ አልፏል። ከዚህ ቀደም ተጓዳኝ ህመም የነበረበትና በኤካ ኮተቤ ሆስፒታልም ህክምና ሲደረግለት እንደነበር የጤና ሚኒስትርና የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በጋራ የሚያወጡት እለታዊ መግለጫ ጠቁሟል።

      ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው ሰዎች 94 ወንዶች እና 56 ሴቶች መሆናቸውንም መግለጫው አመላክቷል።

      በቫይረሱ የተያዙት ግለሰቦች በአብዛኛው የስርጭት ማዕከል እየሆነች በመጣችው አዲስ አበባ ሲሆን በዛሬው ዕለትም 123ቱ ከአዲስ አበባ መሆናቸቸው ተገልጿል።

      ቀሪዎቹም አንድ ሰው ከአፋር፣ ሁለት ከትግራይ፣ ሶስት ከደቡብ፣ ሁለት ከኦሮሚያ፣ አስራ ሶስት ከአማራ እንዲሁም ስድስቱ ደግሞ ከሶማሌ ክልል ናቸው።

      በአጠቃላይ በሃገሪቱ ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው ሰዎች 1637 የደረሰ ሲሆን ከነዚህም ውስጥ 250ዎቹ አገግመዋል። ሃገሪቱ በኮሮና ያጣቻቸው ዜጎችም ቁጥር 18 ደርሷል።

      መግለጫ

      የፎቶው ባለመብት, Ethiopian Public Health Institute

      መግለጫ

      የፎቶው ባለመብት, Ethiopian Public Health Institute

    • የእስራኤል ፓርላማ አባል በቫይረሱ መያዙን ተከትሎ ምክር ቤቱ ተዘጋ

      ሰንደቅ አላማ የያዘ ግለሰብ

      የፎቶው ባለመብት, Getty Images

      አንድ የፓርላማ አባል በቫይረሱ መያዙን ተከትሎ እስራኤል በርካታ የምክር ቤት ስብሰባዎችን እንዳይካሄዱ አግዳለች። የምክር ቤት አባላቱም በአስገዳጅ ምክንያት ካልሆነ እንዳይመጡ እንዲሁም ጉባኤዎችም ላልተወሰነ ጊዜ ተራዝመዋል።

      በቫይረሱ የተያዙት ሳሚ አቡ ሻዴህ የተባለው የፖርላማ አባል አሽከርካሪያቸው በቫይረሱ መያዛቸውን ተከትሎ ራሳቸውን አግልለው ተቀምጠው ነበር። ነገር ግን በባለፉት ሁለት ሳምንታት በብዙ ሺዎች ከሚቆጠሩ ሰዎች ጋር መገናኘታቸውንም ካን የተባለው ሚዲያ የፖርላማ አባሉን ዋቢ አድርጎ ዘግቧል።

      በተለያዩ ዝግጅቶች፣ ለቅሶዎች እንዲሁም ጉባኤዎች ላይ መሳተፋቸውንም ታይምስ ኦፍ እሰራኤል ዘግቧል።

      ከሳቸው ጋር ግንኙነት የነበራቸው ሰዎችም ራሳቸውን እንዲያገልሉና እንደሚመረመሩም ጥሪ አድርገዋል።

      "ቫይረሱ በመሃከላችን ውስጥ ነው ያለው። ዝም ብለን በኑሯችንም መቀጠል ቫይረሱን እንዲዛመት ያደርገዋል" በማለት በትዊተር ገፃቸው አስፍረዋል።

      ካን የተባለው ሚዲያ ባወጣው ፎቶ ላይም የፓርላማ አባሉ በቅርቡ በእስራኤል ፖሊስ የተገደለው ፍልስጥኤማዊው ኢያድ ሃላክ ቤተሰቦችን ለማፅናናት በሄዱበት ወቅትም የፊት ጭምብል ሳያደርጉ ነበር።

    • ስዊድንን ጎረቤቶቿ ለምን አገለሏት?

    • በኬንያ የፖሊስ ኃላፊዎች በግድያ ሊከሰሱ ነው

      ሁለት የኬንያ የፖሊስ ኃላፊዎች በግድያ ሊከሰሱ መሆኑን ዘ ኢንዲፔንደንት ፖሊሲንግ ኦቨርሳይት አውቶሪቲ በመግለጫ አስታወቀ።

      በመግለጫው፤ የአገሪቱ የፖሊስ ተቆጣጣሪ ሁለቱ ፓሊሶች ላይ ምርመራ ማካሄዱ ተመልክቷል።

      ደንከን ንድዬማ ንድዋ፤ ናይሮቢ ውስጥ፤ የ13 ዓመቱ ያሲን ሁሴን ማዮ ቤቱ በረንዳ ላይ ሳለ ተኩሶ በመግደል ነው የተከሰሰው።

      ግድያው የተፈጸመው ፓሊሶች የሰዓት እላፊ ገደብን ለማስፈጸም ሲንቀሳቀሱ ነበር። የቫይረሱን ሥርጭት ለመግታት ኬንያ የሰዓት እላፊ መጣሏ ይታወሳል።

      ሉቱህ አንግሪታ፤ ሲያያ በተባለች ግዛት የዝርፊያ ጥቆማ እየተከታታለ ሳለ ኮሊታ አሞንዲ ኦዱአ የተባሉ መምህር ገድሏል።

      ጋሪሳ በተባለ ግዛት አንድ ግለሰብን ያንገላቱ አራት የፖሊስ ኃላፊዎች ላይ ክስ እንደሚመሰረትም ተገልጿል።

      የፖሊስ ተቆጣጣሪው እንዳለው፤ ኮሮናቫይረስ በኬንያ ሪፖርት ከተደረገ ወዲህ 15 ሰዎች በፖሊስ ተገድለዋል። 31 ሰዎች ደግሞ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

      ዘ ኢንዲፔንደንት ፖሊሲንግ ኦቨርሳይት አውቶሪቲ፤ 87 ቅሬታዎች እንደቀረቡለት ይፋ አድርጓል። ከፍተኛ አካላዊ ጉዳት፣ ወሲባዊ ጥቃት፣ ዝርፊያና እንግልት ይገኙበታል።

      የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ጭካኔ ስለተሞላው የፖሊስ እርምጃ እንዲሁም የፖሊስ ኃላፊዎች አለመቀጣታቸው ላይ በተደጋጋሚ ቅሬታ ያሰማሉ።

    • “ክትባት ከመቼውም ጊዜ በላይ ያስፈልገናል” ቢል ጌትስ

      ቢል

      የፎቶው ባለመብት, Getty Images

      አሜሪካዊው ቢሊየነር ቢል ጌትስ ለኮሮናቫይረስ ክትባት ሲገኝ በመላው ዓለም መከፋፈል አለበት አሉ።

      የዓለም መሪዎች፣ ሀብታም ድርጅቶችና ግለሰቦች ክትባትን በተመለከተ በበይነ መረብ ውይይት ያደርጋሉ። ለክትባት ምርት የሚውል 7.4 ቢሊዮን ዶላር ያሰባስባሉ ተብሎም ይጠበቃል።

      ቢል ከቢቢሲ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ “ለክትባት የሚደረግ ድጋፍ ከመቼውም በላይ አሁን ያስፈልገናል” ብለው እያንዳንዱ እርዳታ ሕይወት እንደሚያተርፍ አስረግጠዋል።

      የሚሰባሰበው ገንዘብ ውጤታማ የሆነ የኮሮናቫይረስ ክትባትን ለድሃ አገራት ለማከፋፈል ይውላል። እንደ ፖሊዮ፣ ታይፎይድ እና ኩፍኝ ያሉ ገዳይ በሽታዎችን ለመከላከልም ይውላል።

      የወረርሽኙ ሥርጭት በመላው ዓለም ለክትባት የሚደረገውን ድጋፍ አደናቅፏል። በዚህ ምክንያት ወደ 80 ሚሊዮን ሕፃናት መደበኛ ክትባት ሳያገኙ ቀርተዋል።

      ቢልየነሩ እንዳሉት፤ ስለ ክትባቲ የሚናፈሰው ሐሰተኛ ወሬ የበሽታውን ሥርጭት ለመግታት የሚደረገውን ጥረት ላይ አጥልቷል።

      “ክትባቱን ስናገኝ ከ80 በመቶ በላይ ሕዝቡ እንዲወስደው በማድረግ ማኅበረሰባዊ በሽታውን የመከላከል አቅም (herd immunity) ማዳበር እንፈልጋለን” ብለዋል።

      “ክትባቱ መጥፎ ነው። ከጀርባው ሴራ አለ ከተባለ ግን ሰዎች ክትባቱን ለመውሰድ ፍቃደኛ አይሆኑም። በሽታው ሰዎችን መቅጠፉንም ይቀጥላል” ሲሉም አክለዋል።

    • በአውሮፓ ምን ውሳኔ ተላለፈ?

      መርክል

      የፎቶው ባለመብት, EPA

      ጀርመን፡ ምጣኔ ሀብቷን የሚያነቃቁ ውሳኔዎች አሳልፋለች። መራሔተ መንግሥት አንጌላ መርክል የ146 ቢሊዮን ዶላር ምጣኔ ሀብት ማነቃቂያ ገንዘብ መመደቡን አስታውቀዋል። ተጨማሪ እሴት ታክስ በመቀነስ የሸማቾችን አቅም ለማጎልበትም ታስቧል። ለአቅመ ደካማ ቤተሰቦች በአንድ ልጅ 335 ዶላር እንደሚሰጥም ተገልጿል።

      አውስትራሊያ፡ ከጣልያን ውጪ ኬሎች አገራት ጋር የሚያዋስኗትን ድንበሮች ከፍታለች። የውጪ ጉዳይ ሚንስትሩ አሌክሳንደር ሻልንበርግ ከኮሮናቫይረስ በፊት ወደነበረው ሕይወት እየተመለስን ነው ብለዋል።

      አውስትራሊያ ከጣልያን ጋር የሚያዋስናትን ድንበር ባትከፍትም፤ ጣልያን ግን ድንበሮቿን ባጠቃላይ ከፍታለች። የውጪ ጉዳይ ሚንስትሩ ሊዊጂ ዲ ማዎ፤ የተናጠል እርምጃዎች የአውሮፓ ሕብረትን ይጎዳል ብለዋል።

      ስፔን፡ የባለሪክ አይላንድ ፕሬዘዳንት ፍራንሲስካ አርሜንጎል፤ ወደ ግዛታቸው የሚሄዱ ቱሪስቶችቀድሞ ከለመዱት በተለየ ሁኔታ የእረፍት ጊዜያቸውን እንደሚያሳልፉ ተናግረዋል። ምክንያቱም ኮቪድ-19 የወትሮውን የአኗኗር ዘዬ ለውጧልና።

      ሰሜን መቄዶንያ፡ ጥብቅ የሰዓት እላፊ ገደብ በአንዳንድ ከተሞቿ ደንግጋለች። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በበሽታው የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ጨምሯል።

    • ኮሮናቫይረስ ስፓርቱን እንዴት እያደረገው ነው?

      ዛሬ የፕሪሚየር ሊግ ክለቦች ይወያያሉ ተብሎ ይጠበቃል። የዘንድሮው የውድድር ዘመን የማይገባደድ ከሆነ ምን እንደሚደረግ ይመክራሉ።

      ሁሉም ክለቦች የሊግ ሰንጠረዡ እንዴት ይጠናቀቅ? በሚለው ዙርያ አስተያየት እንዲሰጡ ይደረጋል። ወደታች የሚወርዱ ቡድኖች መኖራቸው ግን አይቀርም።

      እንደ አዲስ ለሚጀምረው ሊግ የመጀመሪያዎቹ ጥቂት ዙሮች መርሃ ግብር ይወጣል ተብሎ ይጠበቃል። ጨዋታዎቹ የሚካሄዱበት ሰዓትና የሚሰራጩበት ጣቢያም ይፋ እንደሚሆን ይጠበቃል።

      የአየርላንድ እግር ኳስ ክለብ ቦሄሚኒያስ፤ ደብሊን በሚገኝ አንድ ሜዳ ሦስት ተጫዋቾችና አሰልጣኝን ያካተቱ ሁለት ቡድኖች ልምምድ ማድረጋቸው ስህተት ነው ብሏል።

      ተጫዋቾቹ ልምምድ ሲያደርጉ የሚያሳይ ቪድዮ በማኅበራዊ ሚድያ ተሰራጭቶ ነበር።

      በሌላ በኩል የሀንጋሪ ካፕ የፍጻሜ ውድድር ሲካሄድ፤ አንዳንድ ደጋፊዎች አካላዊ ርቀት ሳይጠብቁ ተስተውለዋል።

      የፑስካስ ሜዳ ክፍት የተደረገው በከፊል ሆኖ፤ ደጋፊዎች ተራርቀው እንዲቀመጡ ተነግሯቸው ነበር። ሆንቨድስ ሜዞኮቨስድ-ዝስሪን 2 ለ 1 ባሸነፈበት ጨዋታ ተቀናቃኝ ጎራዎች ግብ በገባ ቁጥር ተሰባስበው ታይተዋል።

      ሀንጋሪ ደጋፊዎች ሜዳ ገብተው እግር ኳስ እንዲመለከቱ የፈቀደች የመጀመሪያ የአውሮፓ አገር ናት።