በኢትዮጵያ 150 ሰዎች ኮሮናቫይረስ ሲገኝባቸው የአንድ ሰው ህይወት አለፈ

በኢትዮጵያ ቫይረሱ የሚገኝባቸው ሰዎች ቁትር ከዕለት ዕለት በፍጥነት እየጨመረ ነው። በተለይ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ያለው የቫይረሱ መስፋፋት በጣም ከፍተኛ እንደሆነ በየዕለቱ የሚወጣው መረጃ ያመለክታል። በዚህም በአገሪቱ እስካሁን ከተመዘገበው 1637 የህሙማን ቁጥር ውስጥ ከአንድ ሺህ የሚበልጡት ከአዲስ አበባ የተገኙ ናቸው። አሁንም የቫይረሱ ስርጭት ባለበት እንዲቆም እጅን በሚገባ መታጠብ፣ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ፣ አካላዊ ርቀትን መጠበቅ በባለሙያዎችና በመንግሥት የሚመከሩ መከላከያዎች ናቸው። ከኮሮናቫይረስ ጋር የተያያዙ የቀጥታ ዘገባዎቻችንን እዚህ ገጽ ላይ ይከታተሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. የደቡብ አፍሪካዋ ግዛት አረጋውያንን ብቻ ልትመረምር ነው

    የደቡብ አፍሪካዋ ዌስተርን ኬፕ ግዛት ከ55 ዓመት በላይ የሆኑ አረጋውያንን ብቻ መመርመር ልትጀምር ነው።

    የወደብ ከተማዋ ኬፕ ታውን መገኛ በሆነችው ዌስተርን ኬፕ ግዛት በርካታ ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል። ቁጥሩ ከመላው አገሪቱ ከፍተኛው እንደሆነም ተነግሯል።

    የግዛቲቱ የጤና ተቋም እንዳለው፤ አረጋውያን ለበሽታው የበለጠ ተጋላጭ ናቸው። ከአረጋውያን በተጨማሪ የጤና ባለሙያዎችም ምርመራ እንደሚደረግላቸው ተገልጿል።

    ለበሽታው ተጋላጭ የሆኑ ሰዎች ውጤታቸው በአፋጣኝ እንዲታወቅ ለምርመራ ቅድሚያ ይሰጣቸዋል።

    በደቡብ አፍሪካ በኮሮናቫይረስ ከተያዙ 37,525 ሰዎች በዌስት ኬፕ የሚኖሩት 24,657 ያህሉ ናቸው።

    ምርመራ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

  2. አጥኚዎች የሀይድሮክሎርክዊን ውጤታማነት ላይ ጥያቄ አነሱ

    በሚኒሶታ የሚገኝ የህክምና ዩኒቨርስቲ ውስጥ 821 ሰዎች በኮሮናቫይረስ ለተያዙ ሰዎች እንዲጋለጡ ተደርጎ ነበር። ጥናቱ እንደሚያሳየው፤ ሀይድሮክሎርክዊን 821ዱን ሰዎች ከኮቪድ-19ኝን አልተከላከለም።

    በኒው ኢንግላንድ የሕክምና መጽሔት የታተመው ጥናት፤ በአወዛጋቢው ሀይድሮክሎርክዊን ላይ የተሠራ ምርምርን የመጀመሪያ ደረጃ ግኝት ያሳያል።

    በጥናቱ የተሳተፉ ሰዎች ሀይድሮክሎርክዊን ወይም ፕላሲቦ [ጉዳት የሌለው መድኃኒት] ለሁለት ሳምንት እንዲወስዱ ተደርጓል። ከነዚህ መካከል ለኮቪድ-19 በተጋለጡት መካከል አምብዛም ልዩነት እንዳልታየ ጥናቱ ጠቁሟል።

    ኒው ዮርክ ታይምስ የሚኒሶታ ዩኒቨርስቲው ዶ/ር ዴቪድ አር ቡልዌርን ጠቅሶ እንደዘገበው፤ “ኮቪድ-19 ከያዘው ጋር ንክኪ ያለው ሰው ሀይድሮክሎርክዊን ለቅድመ ጥንቅቃቄ ቢወስድ ውጤታማ እንደማይሆን ማኅበረሰቡ እንዲደዳ እንፈልጋለን” ብለዋል ዶክተሩ።

    የወባ መከላከያ የሆነው መድኃኒቱ በተለይም በአሜሪካው ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ ብዙ ተብሎለታል። ትራምፕ ሀይድሮክሎርክዊን እንደወሰዱ መናገራቸውም አይዘነጋም።

    እንክብል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

  3. ጆርጅ ፍሎይድ ኮሮናቫይረስ ነበረበት ተባለ

    በፖሊስ መገደሉ በመላው አሜሪካ ተቃውሞ የቀሰቀሰው ጥቁር አሜሪካዊው ጆርጅ ፍሎይድ ከመሞቱ ከሳምንታት በፊት ኮሮናቫይረስ ተገኝቶበት ነበር ተባለ።

    20 ገፅ የሚሆነውና ስለ አሟሟቱ የሚገልጸው ሪፖርት እንደሚያሳየው፤ ጆርጅ ሚያዝያ 3 ኮሮናቫይረስ ይዞት እንደነበር ያሳያል።

    ነገር ግን የቫይረሱ ዘረ መል በአንድ ሰው ሰውነት ውስጥ ለሳምንታት ሊቆይ ስለሚችል፤ ጆርጅም የበሽታው ምልክት ሳይታይበት ሊቀር እንደቻለ ተገልጿል። ሪፖርቱ ጆርጅ “ቀደም ሲል ይዞት የነበረ በሽታ ያሳደረው ጉዳት” ይታያል ይላል።

    የጆርጅ ፍሎይድን አስክሬን በግል ከመረመሩት ሁለት ሀኪሞች አንዱ የሆኑት ዶ/ር ማይክል ባደን፤ ለኒው ዮርክ ታይምስ እንደተናገሩት፤ ጆርጅ በኮቪድ-19 መያዙ አልተነገራቸውም ነበር ።

    “የአስክሬን ምርመራ ሲደረግ ሟቹ ኮሮናቫይረስ እንደነበረበት ከታወቀ፤ አስክሬኑን ለሚነኩ ሰዎች ባጠቃላይ ማሳወቅ ይገባል። [ቢታወቅ] ጥንቃቄ ይደረግ ነበር” ብለዋል ዶ/ር ማይክል።

  4. የኬንያ ተመራማሪዎች የቫይረሱን ቅንጣት ለዩ

    የኬንያ ተመራማሪዎች ቢያንስ ዘጠኝ የሚሆኑ የኮቪድ-19 ቅንጣቶችን (strains) መለየታቸው ተገለጸ። ቅንጣቶቹ በአገሪቱ እየተዘዋወሩ የሚገኙ ሲሆን፤ ግኝቱ የቫይረሱን የዘረ መል ለውጥ (mutations) ለመከታተል ይረዳል።

    እነዚህ ዘጠኝ ቅንጣቶች በመላው ዓለም እየተዘዋወሩ ካሉት የቫይረሱ ቅንጣቶች የተለዩ አይደሉም።

    የተመራማሪዎቹ ቡድን፤ የበሽታውን ምልክት ከሚያሳዩና ከማያሳዩ 122 ህሙማን የዘረ መል ናሙና (genomes) ወስዷል። ህሙማኑ የሚኖሩት በናይሮቢና በሞምባሳ ነው።

    የኬንያ የህክምና ጥናት ተቋም (ኬምሪ) ባወጣው ሪፓርት መሠረት፤ በመጋቢት ወር በሽታው የተሰራጨው ከውጪ አገራት በገቡ ሰዎች አማካይነት መሆኑን ጥናታቸው ጠቁሟል።

    ተመራማሪዎቹ ናሙና የሰበሰቡት እአአ ከመጋቢት 12 እስከ ግንቦት 25 ነው።

    የተቋሙ መሪ ፕሮፌሰር የሪ ኮምቤ፤ “ግኝቱ በኬንያ የቫይረሱን ሥርጭት ለመግታት የሚደረገውን ጥረት ያግዛል። የቫይረሱን የዘረ መል ለውጥ (mutations) ለመከታተል እንዲሁም የወረርሽኙን ማኅበረሰባዊ ሥርጭት ምንጭ ለማግኘትም ይረዳል” ብለዋል።

    የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ክንፍ ኃላፊ ዶ/ር ማቲድሶሞየቲ እንዳሉት፤ በመላው ዓለም ተመራማሪዎች 103 ናሙና መርምረዋል። ከነዚህም ኤል እና ኤስ የተባሉ ቅንጣቶችን ማግኘት ችለዋል። ኤል የተባለው የቅንጣት አይነት እጅግ አደገኛው መሆኑን ተመልክቷል።

    ምርመራ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

  5. ቻይና የውጪ አገራት አየር መንገዶችን ልትቀበል ነው

    አውሮፕላን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የቻይና የበረራ ቁጥጥር ዘርፍ ወደ አገሪቱ እንዳይገቡ ተከልክለው የነበሩ የውጪ አገራት አየር መንገዶችን መቀበል ሊጀምር መሆኑን አስታወቀ።

    አየር መንገዶቹ ከሰኔ ስምንት ጀምሮ በሳምንት አንድ ቀን ወደ ቻይና በረራ እንዲያደርጉ ውሳኔ መተላለፉን የአገሪቱ ብሔራዊ ጣቢያ ዘግቧል።

    መስፈርቱን የሚያሟሉ አየር መንገዶች መዳረሻቸው ማድረግ የሚፈልጉትን አንድ ግዛት አስታውቀው ሥራ መጀመር እንደሚችሉ ተገልጿል።

    አሜሪካ የቻይና አየር መንገዶች ወደ አገሯ እንዳይገቡ አገዳ መጣሏን ተከትሎ ነው ይህ ውሳኔ የተላለፈው። ቻይናም የአሜሪካ አየር መንገዶች ወደ ግዛቷ ጎዞ እንዳያደርጉ አግዳለች።

  6. ሜክሲኮ ከፍተኛውን እለታዊ ሞት መዘገበች

    ሜክሲኮ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    በሜክሲኮ በአንድ ቀን 1,092 ሰዎች በኮቪድ-19 የሞቱ ሲሆን፤ ይህም ከእስካሁኑ ከፍተኛው ነው። የሟቾችን ቁጥርም 11,729 አድርሶታል።

    በየቀኑ በበሽታው የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ካለፉት ሳምንታት በእጅጉ ጨምሮ 3,912 ደርሷለል። በሽታው የተገኘባቸው ሰዎች በአጠቃላይ 101,238 ናቸው።

    ኃላፊዎች እንደሚሉት ከሆነ የበሽታው ሥርጭት አሁን ካለው በላይ ሊሆንም ይችላል። ባለፉት ጥቂት ቀናት የአገሪቱ መንግሥት አንዳንድ አካባቢዎች ወደ እንቅስቃሴ እንዲመለሱ መወሰኑ እያስተቸው ነው።

    መኪና አምራቾች፣ የግንባታ ዘርፍ ተቀጣሪዎችም ወደ ሥራ ተመልሰዋል። የፓን አሜሪካ የጤና ድርጅት አገሪቱ በቶሎ ሥራ እንዲጀመር ከፈቀደች በሽታው በስፋት እንደሚሰራጭ አስጠንቅቆ ነበር።

  7. ናይጄርያ የአገር ውስጥ በረራ ልትጀምር ነው

    ናይጄርያ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ናይጄሪያ አምስት አውሮፕላን ማረፊያዎችን እንደምትከፍትና የአገር ውስጥ በረራ እንደሚጀመር ተገለጸ።

    በመዲናዋ አቡጃ፣ በንግድ ማዕከሏ ሌጎስ፣ በደቡባዊቷ የወደብ ከተማ ፖርት ሀርኮርት፣ በሰሜናዊቷ ካኖ እና በደቡብ ምሥራቃዊቷ ላሞ ግዛት የሚገኙ አምስት አውሮፕላን ማረፊያዎች ሰኔ 21 የሚከፈቱ ሲሆን፤ ይህ ውሳኔ እንቅስቃሴ ላይ ተጥሎ የነበረውን ገደብ የማላላት አንድ አካል ነው።

    የበረራ ዘርፍ ኃላፊው ሙሳ ኑሁ እንዳሉት፤ በቀጣይ ሌሎች አውሮፕላን ማረፊያዎችም ሥራ እንዲጀምሩ ይደረጋል።

    “ዓለም አቀፍ በረራ የሚጀመርበትን ቀን እስከምናሳውቅ ድረስ ከአገር ውስጥ በረራዎች ውጪ ሌሎች በረራዎች አይካሄዱም” ብለዋል።

    ወደ አገሪቱ መግባት የሚችሉት፤ ናይጄርያውያንን ከተለያየ አገር የጫኑ አውሮፕላኖችና ሰብዓዊ እርዳታ የሚያጓጉዙ በረራዎች ብቻ ናቸው። እነዚህም ጥብቅ የጥንቃቄ መመሪያን ይከተላሉ።

  8. የኮሮና ወረርሽኝ ስጋት ያጠላበት የኢትዮ-ሱዳን ድንበር

  9. ኢራን በወረርሽኙ በድጋሚ እንዳትመታ ተሰግቷል

    ኢራን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በኢራን በኮሮናቫይረስ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እንደ አዲስ እየናረ መጥቷል።

    ለሁለት ተከታታይ ቀናት ከ3 ሺህ በላይ ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን፤ በወረርሽኙ የተያዙ ሰዎች አጠቃላይ ቁጥር 160 ሺህ መድረሱም በአገሪቱ የጤና ኃላፊዎች ተገልጿል።

    በኢራን ተጨማሪ 70 ሰዎች በቫይረሱ ሳቢያ ሕይወታቸውን አጥተዋል። ይህም የሟቾችን ቁጥር 8,012 አድርሶታል።

    እንቅስቃሴ ላይ ተጥሎ የነበረው ገደብ እየላላ ቢሆንም፤ በሽታው በሁለተኛ ዙር ሥርጭቱ ከጨመረ ገደቦቹ እንደሚመለሱ መንግሥት አስጠንቅቋል።

    “በየትኛውም የአገሪቱ ክፍል ማስጠንቀቂያዎች ችላ ከተባሉ ወይም ፈጣሪ አይበለውና በወረርሽኙ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ከጨመረ በድጋሚ የእንቅስቃሴ ገደብ እንጥላለን” ብለዋል ፕሬዘዳንት ሀሰን ሮሐኒ።

    ወረርሽኙ ወደ አውሮፓና ከዚያም ወደ አሜሪካ ከመዛመቱ በፊት ከቻይና ቀጥሎ ክፉኛ ከተጎዱ አገሮች አንዷ ኢራን ናት። ባለፈው ወር በበሽታው የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ቢቀንስም በዚህ ወር ግን እየጨመረ መጥቷል።

    “ሰዎች ስለ በሽታው ግድ የለሽ እየሆኑ መጥተዋል” ብለዋል የአገሪቱ ጤና ሚንስትር።

  10. ቻይና ስለኮሮናቫይረስ መረጃ ለመልቀቅ አልዘገየሁም አለች

    ምርመራ በቻይና

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚንስትር፤ አገሪቱ ኮሮናቫይረስን የተመለከተ መረጃ ለዓለም የጤና ድርጅት ሳትሰጥ አዘግይታለች መባሉን አስተባበለ።

    የተባለው ነገር “እውነታውን የሚጸረር” ነውም ብሏል።

    ትላንት አሶሼትድ ፕሬስ፤ የዓለም ጤና ድርጅት ኃላፊዎች የሚፈልጉትን መረጃ ከቻይና ማግኘት አለመቻላቸውን ዘግቦ ነበር።

    ድርጅቱ ቻይናን በአደባባይ የማይወቅሰው፤ አገሪቱን አባብሎ ተጨማሪ መረጃ ከመንግሥት ለማግኘት ነው ይላል የትላንቱ ሪፓርት።

    የውጪ ጉዳይ ቃል አቀባዩ ዛሆ ሊጃን በምላሹ፤ “በሪፖርቱ የተካተቱት አንዳንድ ነጥቦች እውነታውን የሚጻረሩ መሆናቸውን ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ” ብለዋል።

    ቃል አቀባዩ ለመገናኛ ብዙሃን የሰጡትን መግለጫ ጠቅሶ ግሎባል ታይምስ እንደዘገበው፤ “ቻይና ስለ ኮሮናቫይረስ ያላትን መረጃ ለዓለም አሳውቃለች። መረጃዎችና እውነታው በግልጽ ተቀምጧል። ይህንንም ጊዜና ታሪክ ይፈርዳል” ብለዋል።

  11. የሐሙስ ግንቦት 27/2012 ዓ.ም የቢቢሲ አማርኛ የቀጥታ ዘገባ ገጽ

    እንደምን አደራችሁ!

    ቢቢሲ አማርኛ እንደተለመደው ከኢትዮጵያና ከዓለም ዙሪያ ትኩስ ዜናና ታሪኮችን ዛሬም ማቅረቡን ይቀጥላል።

    በተለይ ደግሞ በዚህ የቀጥታ ዘገባ ገጻችን የወቅቱ የዓለማችን አንገብጋቢ የጤና ስጋት ስለሆነው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የተለያዩ ዜናና መረጃዎችን በቀጥታ እናቀርባለን።

    ባገኛችሁት አጋጣሚዎች ሁሉ የቢቢሲን ድረ ገጽና ይህንን የቀጥታ ዘገባ ገጽ እንዲሁም የፌስቡክ ገጻችንን እንድትጎበኙ እንጋብዛለን።

    እራሳችሁን ጠብቁ፤ መልካም ቀን!

    ቢቢሲ አማርኛ
  12. በኤርትራ ከሚያዚያ 10 በኋላ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሁለት ሰዎች ተገኙ

    አስመራ ከተማ

    ከአንድ ወር ለሚበልጥ ጊዜ በኮሮናቫይረስ የተያዘ ሰው ሳትመዘግብ የቆየችው ጎረቤት አገር ኤርትራ፤ በቫይረሱ የተያዙ ሁለት ሰዎች መገኘታቸውን የኮቪድ -19 ከፍተኛ ግብረ ኃይል ዛሬ በሰጠው መግለጫ አስታወቋል፡፡

    ባለፈው የፈረንጆቹ ግንቦት ወር አጋማሽ ላይ የአገሪቷ መንግሥት ሰፊ ምርመራ እንደሚያካሂድ አስታውቆ ነበር፡፡

    በዚህም መሰረት በአስመራ ከተማ የተለያዩ አካባቢዎች የተካሄደው የመጀመሪያው ዙር ባጋጣሚ የተሰበሰቡ ናሙናዎች ምርመራ ትናንት ተጠናቋል፡፡

    የናሙና አሰባሰብ ሂደቱ እና ምርመራው የተካሄደው በጤና ሳይንስ ኮሌጅና በብሄራዊ ላብራቶሪ ቅንጅት ነው ተብሏል፡፡

    በአጋጣሚ ከማህበረሰቡ የተወሰዱት ናሙናዎችም የጾታ፣ የአኗኗር ሁኔታ፣ የከተማ፣ የገጠር በሚል የተለያዩ መስፈርቶችን ያሟሉና ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል ያማከሉ እንደነበሩ ተገልጿል፡፡

    በምርመራው 4659 ቤቶችን ማዳረስ የተቻለ ሲሆን ከአንድ ቤት አንድ ሰው እንዲመረመር ተደርጓል፡፡

    በዚህም 4658 ሰዎች ከቫይረሱ ነጻ መሆናቸው የተረጋገጠ ሲሆን አንዲት ሴት ቫይረሱ እንደተገኘባቸው ተገልጿል፡፡

    ይህን ተከትሎም በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ከግለሰቧ ጋር ንክኪ ያላቸው 13 ግለሰቦች ተለይተው ወደ ለይቶ ማቆያ እንዲገቡ ተደርጓል፡፡

    ከእነዚህ ግለሰቦች መካከል አንዱ የሴትዮዋ ባለቤት ሲሆኑ በኋላ ላይ ቫይረሱ እንደተገኘባቸው ተረጋግጧል፡፡

    የተደረገው ሰፊ ምርመራ ውጤት አበረታች መሆኑን የገለጸው ግብረ ኃይሉ፤ አሁንም ግን የወረርሽኙ ሥርጭት ገና የመጀመሪያው ደረጃ ላይ ነው ሲል አስጠንቅቋል፡፡

    ኤርትራ ኮቪድ -19 ወረርሽኝ ከጀመረ አንስቶ ወደ አገሪቷም ሆነ ከአገሪቷ የሚደረጉ በረራዎች እንዲቆሙ ያደረገች ቢሆንም፤ በየብስና በባህር የሚደረጉ ጉዞዎች ግን አልቆሙም፡፡

    ባለፉት ጊዜያት 5ሺህ 270 ሰዎች በ81 የለይቶ ማቆያ ማዕከላት እንዲገቡ የተደረገ ሲሆን፤ 3ሺህ 477 ሰዎች አስፈላጊው ክትትል ተደርጎላቸው ከማዕከላቱ ወጥተዋል፡፡

    ይሁን እንጅ 1793 ሰዎች አሁንም በ45 የለይቶ ማቆያ ማዕከላት ውስጥ እንደሚገኙ ግብረ ኃይሉ አስታውቋል፡፡

  13. ቶተንሃም አንድ ተጫዋች በቫይረሱ እንደተያዘበት አሳወቀ

    Tottenham

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የእንግሊዙ እግር ኳስ ክለብ ቶተንሃም ሆትስፐርስ አንድ ተጫዋች በኮቪድ-19 እንደተያዘ ይፋ አድርጓል።

    ተጨዋቹ ለሚቀጥሉት 7 ቀናት ራሱን አግልሎ ይቆያል።

    የተጫዋቹ ማንነት ይፋ እንደማይሆን ክለቡ ዛሬ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

    የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ሊጀምር ሁለት ሳምንታት ቀርተውታል። ከዚያ በፊት ግን ተጨዋቾችና ባለሙያዎች በየጊዜው ምርመራ ይደርግላቸዋል።

    ለመጨረሻ ጊዜ በተደረገ 1197 የላቦራቶሪ ምርመራ አንድ ሰው ብቻ ቫይረሱ እንዳለበት ተረጋግጧል። ይህም የቶተንሃሙ ተጫዋች ነው።

    ሊጉ ይመለሳል ተብሎ ከተነገረ ወዲህ ተጫዋቾችና ባለሙያዎች አምስት ጊዜ ምርመራ ተደርጎላቸዋል።

    የፕሪሚዬር ሊጉ ተጫዋቾችና ባለሙያዎች ምርምራ የሚደርግላቸው በሳምንት ሁለት ጊዜ ነው።

  14. የባርሴሎና የኮሮናቫይረስ ህሙማን የባህር ዳርቻ ጉዞ

    የኮሮናቫይረስ ህመምተኛ ከጤና ባለሙያዎች ጋር በባህር ዳርቻ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በስፔን እያገገሙ ያሉ የኮሮናቫይረስ ህሙማን የህክምናቸው አንዱ አካል ነው የተባለውን የባህር ዳርቻ ጉዞ አድርገዋል።

    የጽኑ ህሙማን ክፍሉን ለማሻሻል የተቀረጸው ፕሮግራም አካል በሆነው በዚህ ጉዞ፤ በባርሴሎና የሚገኘው ዴል ማር ሆስፒታል የህክምና ቡድኖች ህሙማኑ በተኙበት አልጋ ላይ ሆነው ወደ ባህር ዳርቻዎቹ ሲወስዱ ፎቶግራፎችን ተነስተዋል።

    በስፔን በአጠቃላይ 239 ሺህ 932 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን 27 ሺህ 127 ሰዎች ደግሞ በቫይረሱ ሕይወታቸው አልፏል።

    ወረርሽኙን ለመቆጣጠር ከአውሮፓ ጥብቅ የተባለውን የእንቅስቃሴ ገደብ የጣለችው ስፔን፤ ቀስ በቀስ ገደቦቿን ማላላት ጀምራለች።

    ከዚህ ቀደም ለአካላዊ እንቅስቃሴ ሰዎች ከቤት መውጣት አይችሉም ነበር፤ ሕጻናትም በምንም ምክንያት ቢሆን ከቤት መውጣት አይፈቀድላቸውም ነበር።

    ይሁን እንጂ ስፔን በቅርብ ሳምንታት ወረርሽኙን መቆጣጠር ችላለች።

    ማክሰኞ ዕለት ለሁለተኛ ቀን በ24 ሰዓታት ውስጥ አንድም በቫይረሱ የሞተ ሰው አልመዘገበችም።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ፔድሮ ሳንቼዝ ረቡዕ ዕለት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ለሁለት ሳምንታት ለማራዘም ምክር ቤቱን ጠይቀዋል።

    የኮሮናቫይረስ ህመምተኛ ከጤና ባለሙያዎች ጋር በባህር ዳርቻ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በቫይረሱ ክፉኛ በተመታችው ስፔን በቅርቡ ጎብኝዎች ይመለሳሉ የሚል ተስፋ አለ
    የኮሮናቫይረስ ህመምተኛ ከጤና ባለሙያዎች ጋር በባህር ዳርቻ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የኮቪድ-19 ታማሚው ሆስፒታል ከገቡ ሁለት ወር ገደማ ሆኗቸዋል
  15. ቢል ጌትስ ለምንድን ነው ሚሞሪ ዲስክ ክንዳችን ላይ ማስቀመጥ የፈለጉት?

    ቢል ጌትስ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ይህን ለመመለስ ኮቪድ-19 ቫይረስ እንዴት ሊፈጠር ቻለ? የሚለውን በሴራ ነዳፊዎች መነጽር ማየት ይኖርብናል።

    በሴራ ነዳፊዎች እሳቤ ቫይረሱን የፈጠረው የማይክሮሶፍት ፈጣሪ ቢል ጌትስ ነው። የዚህ አንድ ማረጋገጫ አድርገው የሚወስዱት ደግሞ ቢልጌትስ ከዚህ ቀደምም ይህ ቫይረስ ሊከሰት እንደሚችል ያውቅ የነበረ መሆኑን ነው።

    ቢሊየነሩ ቢልጌትስ ዓላማው የዓለምን ሕዝብ ሁለመናውን መቆጣጠር ስለሆነ መጀመርያ ቫይረስን ፈጠረ፣ ቀጥሎ ደግሞ ክትባቱን ይፈጥራል ይላሉ። ክትባቱ ውስጥ ደግሞ በዓይን የማይታይ ረቂቅ ዲጂታል ሚሞሪ (microchip) ይቀብርብናል በማለት ያስባሉ።

    ቢቢሲ ይህ ነገር እውነት ነው ወይ? ሲል የቢልጌትስ ፋውንዴሽንን ጠይቆ "ቅጥፈት ነው" የሚል ምላሽ አግኝቷል።

    ይህ የሴራ ትንታኔ በአሜሪካ ውስጥ ብቻ የሚያጠነጥን አይደለም። ዝርዝሩን ከዚህ ያንብቡ ቢል ጌትስ በክትባት ስም ክንዳችን ውስጥ ሊቀብሩት ያሰቡት ነገር አለ?

  16. በኮሮናቫይረስ ዘመን መሄጃ የጠፋቸውና አስታዋሽ ያጡት በወሲብ ንግድ ላይ የተሰማሩ ሴቶች

  17. በኢትዮጵያ 65 የጤና ተቋማት ሠራተኞች ኮሮናቫይረስ ተገኘባቸው

    ዶ/ር ሊያ ታደሰ

    የፎቶው ባለመብት, ENA

    በኢትዮጵያ እስካሁን 49 የጤና ባለሙያዎችና 16 ድጋፍ ሰጭ ሠራተኞች ኮሮናቫይረስ እንደተገኘባቸው የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር ሊያ ታደሰ ማስታወቃቸውን ኢዜአ ዘገበ።

    ባለሙያዎቹ በአብዛኛው በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኙ ተቋማት ውስጥ እያገለገሉ የነበሩ ናቸው ተብሏል።

    ሚኒስትሯ መንግሥት የጤና ተቋማት ሠራተኞች ለቫይረሱ ያላቸውን ተጋላጭነት ለመቀነስ ከሚያደርገው ጥረት በተጨማሪ ሕብረተሰቡ ራሱን በመጠበቅ በጤና ባለሙያዎቹ ላይ የሚደርሰውን ጫና እንዲቀንስም ጥሪ አቅርበዋል።

    ዶ/ር ሊያ የጤና ተቋማት ሠራተኞች የወረርሽኙን ሥርጭት ለመግታት እያደረጉ ያለውን ጥረት አመስግነዋል።

    ትናንት የጤና ሚኒስትሯ በሚቀጥሉት 4 ወራት ለጤና ተቋማት ብቻ 131 ሚሊየን የአፍና አፍንጫ መሸፈኛዎች (ማስኮች) እንደሚያስፈልጉ ተናግረው ነበር።፡

    በዓለም አቀፍ ደረጃ የእነዚህ የህክምና ግብዓቶች እጥረት መኖራቸውን የጠቀሱት ዶ/ር ሊያ፤ እንደ አገርም በርካታ ክፍተቶች መኖራቸውን ጠቁመዋል።

    ቢቢሲ ከዚህ ቀደም ያነጋገራቸው የተለያዩ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተሮች በሆስፒታሎች ውስጥ በቂ የቫይረሱ መከላከያ የህክምና ግብዓቶች እንደሌለ መግለጻቸው ይታወሳል።

  18. እስራኤል 7ሺህ ተማሪዎችን ለይቶ ማቆያ አስገባች

    የጤና ባለሙያ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    በእስራኤል የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በትምህርት ቤቶች መቀስቀሱን ተከትሎ 7ሺህ የሚጠጉ ተማሪዎችንና መምህራን ለይቶ ማቆያ እንዲገቡ መደረጉን ባለሥልጣናት አስታወቁ፡፡

    ከ40 በላይ ትምህርት ቤቶችም ተዘግተዋል፡፡

    ሆኖም መንግሥት አጠቃላይ መዋለ ህጻናትና ሌሎች ትምህርት ቤቶች ተከፍተው እንዲቆዩ ወስኗል፡፡

    በቅርቡ በእየሩሳሌም ጂምናሺያ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አዲስ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች በስፋት የታዩ ሲሆን 130 የሚሆኑት ቫይረሱ ተገኝቶባቸዋል፡፡

    የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ቫይረሱን ያዛመተው አንድ የኮቪድ -19 ታማሚ መምህር እንደሆኑ ዘግበዋል፡፡

    በትምህርት ቤቶችና በሌሎች ተቋማት ወረርሽኙ መቀስቀሱም በአገሪቷ ሁለተኛ ዙር ወረርሽኝ እንዳይቀሰቀስ ስጋት ፈጥሯል፡፡

    ማክሰኞ እለት የጤና ሚኒስቴር 116 አዲስ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች መገኘታቸውን ያስታወቀ ሲሆን፤ ይህም በአንድ ወር ውስጥ የታየ ከፍተኛ ጭማሬ ነው ተብሏል፡፡

    በእስራኤል እስካሁን 17ሺህ 342 ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን 290 ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸው አልፏል፡፡

    በአገሪቷ ወረርሽኙን ለመቆጣጠር ቤት ውስጥ የመቀመጥ ገደብ የተጣለው ቀደም ብሎ ሲሆን ባለፈው ወር አጋማሽ ጀምሮ ግን ቀስ በቀስ ገደቦቿን እያላላች ነው፡፡

    በዚህም መሰረት ትምህርት ቤቶች፣ ቢሮዎች፣ ሱቆች፣ ምግብ ቤቶች እና የባህር ዳርቻዎች እንዲከፈቱ ፈቅዳለች፡፡

  19. በናይጄሪያ በመቶዎች የሚቆጠሩ የጤና ባለሙያዎች ኮሮናቫይረስ ተገኘባቸው

    የጤና ባለሙያ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በናይጄሪያ ቢያንስ 812 የጤና ባለሙያዎች በኮሮናቫይረስ እንደተያዙ የአገሪቷ የበሽታ መከላከያና መቆጣጠሪያ ማዕከል አስታወቀ፡፡

    የማዕከሉ ዋና ኃላፊ ቺክዌ ኢሄክዌዙ እንዳሉት በቫይረሱ መያዛቸው ከተረጋገጠው የጤና ባለሙያዎች መካከል 29ኙ የኤጀንሲው ባልደረቦች እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡

    ከሁለት ወር በፊት የናይጄሪያ የህክምና ማህበር ፊት ለፊት የሚጋፈጡ የጤና ባለሙያዎች በቫይረሱ የተያዙት በቂ የመከላከያ የህክምና ግብዓቶች ባለመኖራቸው እንደሆነ ገልጾ ነበር፡፡

    ይሁን እንጅ ኃላፊው፤ ማዕከሉ 400 ሺህ የመከላከያ የህክምና ግብዓቶችን አሰራጭቷል ብለዋል፡፡

    በአንዳንድ የአገሪቷ ግዛቶች ያሉ የጤና ባለሙያዎች ህብረትም በህክምና መሳሪያዎች ግብዓት እጥረት ሳቢያ አድማ እንደሚመቱም ሲያስጠነቅቁ ነበር፡፡

    ይህ በእንዲህ እንዳለ መንግሥት የግል ሆስፒታሎች የኮቪድ-19 ህሙማንን እንዳያክሙ ጥሎት የነበረውን እገዳ በመሻር፤ የግል ሆስፒታሎች አገልግሎቱን ለመስጠት በያሉበት ግዛት እንዲመዘገቡና ሰራተኞቻቸውም በቂ ሥልጠና ማግኘታቸውን እንዲያረጋግጡ ጠይቋል፡፡

    ናይጄሪያ እስካሁን 10ሺህ 819 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን 314 ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸው አልፏል፡፡

  20. በኬንያ የወሲብ አዳኞች በበይነ መረብ የሚማሩ ተማሪዎችን ኢላማ አድርገዋል ተባለ

    ኮምፒዩተር የያዘ ህጻን ምስል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዓለምን እያስጨነቀ ያለው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ዘርፈ ብዙ ችግሮችን እያስከተለ ነው፡፡

    ታዲያ የቫይረሱን ሥርጭት ለመግታት ሲባል አገራት የተለያዩ እርምጃዎችን ወስደዋል፡፡ ከእነዚህ መካከል ትምህርት ቤቶች እንዲዘጉ ማድረግ አንዱ ነው፡፡

    የትምህርት ቤቶችን መዘጋት ተከትሎም አንዳንድ አገራት ተማሪዎች በቤታቸው ሆነው የሚማሩበትን ሁኔታዎች አመቻችተዋል፡፡

    ኬንያም የበይነ መረብ አገልግሎት ያላቸው ተማሪዎች ትምህርታቸውን በዚሁ መንገድ እየተከታተሉ ይገኛሉ፡፡

    ይሁን እንጅ በአገሪቷ በወረርሽኙ ሳቢያ ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸውን ተከትሎ በበይነ መረብ ትምህርታቸውን የሚከታተሉ ተማሪዎች የወሲብ ጥቃት ኢላማ ሆነዋል ሲል ፖሊስ አስጠነቅቋል፡፡

    ፖሊስ እንዳስታወቀው በበይነ መረብ የሚመጡ የወሲብ አዳኞች ቁጥርም እየጨመረ ነው ብሏል፡፡

    የአገሪቷ የወንጀል ምርመራ መሥሪያ ቤት፤ እነዚህ የወሲብ አዳኞች ህጻናቱ የራቁት ፎቶ እንዲልኩላቸው ከመጠየቃቸው በፊት በውስጥ መስመር መልዕክት በመላክ ሲያታልሏቸው እንደነበር ደርሸበታለሁ ብሏል፡፡

    ኤጀንሲው በርካታ ጉዳዮች ላይ ምርመራ እያደረገ መሆኑን ጠቅሶ፤ እነዚህ ወንጀለኞች ልጆቻቸው ጋር ግንኙነት ካላቸው የሚያውቁትን መረጃ እንዲሰጧቸው ወላጆቻቸውን ጠይቋል፡፡

    በተጨማሪም ወላጆች ልጆቻቸው በበይነ መረብ አማካኝነት የሚያከናውኗቸውን ተግባራት እንዲቆጣጠሩና ወንጀለኞች ልጆቻቸውን በአካል ለማግኘት ሊሞክሩ ስለሚችሉም የልጆቻቸውን እንቅስቃሴ መከታተል እንዳለባቸው ኤጀንሲው አሳስቧል፡፡