በኢትዮጵያ የተደረገው የላብራቶሪ ምርመራ ከ62 ሺህ በላይ ሆነ

በኢትዮጵያ በባለፉት ሃያ አራት ሰአታት 3271 የላብራቶሪ ምርመራ መደረጉን ተከትሎ፣ በአጠቃላይ በሃገሪቷ የተደረገውን ምርመራ 62 ሺህ 300 አድርሶታል። ሃገሪቷ የመመርመር አቅሟንም በመጨመር በቀን ውስጥ 10ሺህ ሰዎችንም የመመርመር እቅድ እንዳላትም የጤና ሚኒስትሯ ማሳወቃቸው የሚታወስ ነው። በሃገሪቷም በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 365 የደረሰ ሲሆን፣ ከነዚህም መካከል 238ቱ በህክምና ላይ ይገኛሉ፤120ዎቹም አገግመዋል። ከዚህም በተጨማሪ ሃገሪቷ በኮሮናቫይረስ አምስት ዜጎቿን በሞት የተነጠቀች ሲሆን፤ ሁለቱም ወደመጡበት ሃገራት ተመልሰዋል። ስለወረርሽኙ የተለያዩ መረጃዎችን ለማግኘት የቢቢሲ አማርኛን የቀጥታ ዘገባ ከእዚህ ገጽ ይከታተሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በኮሮናቫይረስ ምክንያት ሽያጩ የደራው የካሜሮኑ የኮክቴል መጠጥ

    መጠጦቹን እየቀላቀለ

    በካሜሮኗ የንግድ ማዕከል ዱዋላ የሚገኝ አንድ መጠጥ ቤት የኮክቴል መጠጦቹን በዚህ ቤት መቀመጥ አስገዳጅ በሆነበት ጊዜ እንዴት መሸጥ እንደሚችል መላ ዘይዷል።

    በርካታ የንግድ እንቅስቃሴዎች መውጫው ጠፍቷቸው ቀጥ ባሉበት ወቅት ይህ ጄጄ ኩዌስት የተባለው መጠጥ ቤት (ባር) በየቤቱ የኮክቴል መጠጦቹን የማድረስ ስራን ጀምሯል።

    "የመጀመሪያዎቹ ቀኖች ላይ ምን እያደረግን እንደነበር ግራ ተጋብተን ነበር" ብሏል የመጠጥ ቤቱ ስራ አስኪያጅ አሌክሳንደር ኩዌስት።

    ከጥቂት ቀናት በኋላም መጠጥ የሚፈልጉ ሰዎች ይደውሉላቸው ጀመር።

    ልክ በተደወላላቸው አንድ ሰአት ውስጥ ቤቱ (አፓርትመንቱ) ውስጥ ሆኖ የተለያዩ መጠጦችን አቀላቅሎ በሞተር ሳይክል ቤታቸው እንዲደርስ ያደርጋል።

    መጠጦች ሲቀላቀሉ

    አንድ ሊትር የኮክቴል መጠጥ ወደ 640 ብርም ያወጣል።

    ምንም እንኳን በኮሮናቫይረስ ምከንያት ጫና ቢደርስባቸውም በአሁኑ ወቅት ካለው ሁኔታ ጋር ራሳቸውን በማላመድ መጠጣቸውንም እየሸጡ ይገኛሉ።

    "በኔ አስተያየት ጥሩ ንግድ የሚባለው በየትኛውም ሁኔታ ደንበኞችን ማገልገል ሲቻል ነው። በአሁኑ ሰአት ደንበኞቻችን በአስቸጋረ ሁኔታ ውስጥ ናቸው። እኛም አለንላችሁ እያልን ነው" ብሏል።

    ከዚህም በተጨማሪ "ፍሪጃችሁ ውስጥ ምንድን ነው ያለው?" የሚል አገልግሎት ጀምሯል። ደንበኞች ፍሪጃቸው ውስጥ ያለውን የመጠጥ አይነቶች ያሳዩታል እሱም እነዚህን መጠጦች ደባልቀው ምን መስራት እንደሚችሉ ምክሩን ይለግሳል።

    መጠጦቹን በሞተር ሳይክል ለደንበኞቹ ሲልክ
  2. የአውሮፓ ቡድኖች እስከ 4.2 ቢሊየን ዶላር ኪሳራ ሊያጋጥማቸው ይችላል ተባለ

    ስታዲየም

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በአውሮፓ ትልለቅ ሊጎች የሚጫወቱ የእግር ኳስ ቡድኖችን እስከ 4.2 ቢሊየን ዶላር ድረስ ሊያሳጣቸው እንደሚችል ተገምቷል።

    ነገሮችን ለቡድኖቹ ይበልጥ አሳሳቢ የሚያደርገው ደግሞ ሊጎቹ እንደምንም ተብሎ ቢጠናቀቁ እንኳ ይህን ኪሳራ ማስቀረት አለመቻላቸው ነው።

    ሊጎቹ በታሰበላቸው ጊዜ መጠናቀቅ የማይችሉ ከሆነ ደግሞ ኪሳራው እስከ 7.5 ቢሊየን ዶላር ከፍ ሊልም ይችላል።

    የጀርመን ቡንደስሊጋ ትናንት የተጀመረ ሲሆን የእንግሊዝ ፕሪምየር ሊግ ደግሞ በሚቀጥለው ወር አጋማሽ አካባቢ እንደሚጀመር ይጠበቃል።

    ፈረንሳይ ደግሞ ሊጓን ያቋረጠች ሲሆን የደረጃ ሰንጠረዡን ሲመራ የነበረው ፓሪስ ሴይንት ጀርሜይን አሸናፊ ተብሎ ዋንጫውን አንስቷል።

    በመላው አውሮፓ የሚገኙ ሊጎችም ይህን ያክል ገንዘብ ላለማጣት ሲሉ ሊጎቻቸውን በተቻለ መጠን ለማስጀመር እየተሯሯጡ ይገኛሉ።

    ነገር ግን በዚህ መሀል የተጫዋቾች ደህንነት እንዳይረሳ የሚያሳስቡም አልጠፉም።

  3. "አባቴ ለምን ቤቱ ሄደን እንደማንጠይቀው አይረዳም"

    ጆን

    የፎቶው ባለመብት, Donna Duffy

    የዶና ደፊ አባት 70 አመታቸውን በህዳር ወር ላይ ይደፍናሉ። ለባለፉት 16 ዓመታትም በመርሳት በሽታ (ዲሜንሺያ) ሲሰቃዩ ነበር።

    ባለፉት ሁለት ዓመታትም በአረጋውያን የመንከባከቢያ ማዕከል መኖሪያቸውን ያደረጉት ጆንን፣ ዶና እና እህቷም ሆነ ባለቤታቸው በየቀኑ ይጠይቋቸው ነበር። አንዳንድ ጊዜም በቀን ሁለት ጊዜ።

    ይህ ሁሉ ግን መጋቢት 3፣ 2012 ዓ.ም ቀጥ አለ።

    በዛን ቀን የአየርላንድ የጤና ሚኒስቴር የኮሮናቫይረስን መዛመት ለመግታት ብሎ ካሳለፋቸው ውሳኔዎች መካከል ሰዎችን መጠየቅ መከልክል ነበር።

    ጆን የሚገኙበት ብሩክላንድ የአረጋውያን እንክብካቤ ማዕከል ጥየቃ መከልከሉን ተከትሎ ባወጣው መግለጫ " የምትወዷቸውን ቤተሰቦች አትጠይቁ መባል ምን ያህል ከባድ እንደሆነ እንረዳለን፤ ነገር ግን የቫይረሱን መዛመት ለመከላከል መወሰድ ያለበት እርምጃ ነው" ብሏል።

    በመርሳት ህመም ለሚሰቃዩት ጆን ግን ቤተሰቦቻቸው ለምን መጥተው እንደማይጠይቋቸውም ሆነ እንደማያጫውቷቸው ግልፅ አይደለም።

    ዶና እንደምትለው በቪዲዮ በሚደውሉላቸው ወቅት ከሐዘናቸው ብዛት እንባቸው ኮለል ይላል፤ ፊታቸውንም ያርሰዋል።

    "የመዘንጋት ህመም (ዲመንሺያ) አለበት እናም ውጭ ላይ የሚካሄደውን ነገር ማገናዘብም ሆነ ማስታወስ አይችልም" ትላለች

    "የመንከባከቢያ ማዕከሉ እንደሚዘጋ እናውቅ ነበር እናም አባታችንን የምናዘጋጅበት ጊዜ ብናገኝ ጥሩ ነበር" ብላለች።

  4. በኢትዮጵያ ተጨማሪ 11 ሰዎች ቫይረሱ ተገኘባቸው

    ምርመራ እያደረጉ ያሉ የጤና ባለሙያዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰአታት 4225 ሰዎች ላይ በተደረገ ምርመራ አስራ አንድ ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸው መረጋገጡን ተገልጿል።

    በዚህም በመላው አገሪቱ በአጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ወደ 317 ከፍ ብሏል። ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው ሰዎች 5 ወንድና 6 ሴቶች ናቸው።

    ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች የዕድሜ ክልል ከ 17 እስከ 45 ባለው ውስጥ ሲሆን ሁሉም ኢትዮጵያውያን መሆናቸውም የጤና ሚኒስቴርና የኢትዮጰያ የህብረተሰብ ጤና ተቋም በሚያወጡት መግለጫ ተጠቅሷል።

    ከነዚህም መካከል አራቱ ከአዲስ አበባ፣ስድስት ከሶማሌ ክልል ጂግጂጋ ለይቶ ማቆያና አንድ ሰው ገድሞ ከአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ናቸው።

    ከነዚህም መካከል 7ቱ የውጭ ሃገር የጉዞ ታሪክ ያላቸው፣ ሶስቱ በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር ግንኙነት ያላቸው፣ አንዱ የውጭ ሃገር የጉዞ ታሪክም ሆነ በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር ግንኙነት አለመኖሩ ተገልጿል።

    በኢትዮጵያ እስካሁን በአጠቃላይ 57 ሺ 254 ሰዎች የኮሮናቫይረስ ምርመራ ተደርጎላቸዋል።

    መግለጫ

    የፎቶው ባለመብት, Ministry of Health

    መግለጫ

    የፎቶው ባለመብት, Ministry Of Health

  5. በስፔን በቀን የሚመዘገበው የሟቾች ቁጥር ከመቶ በታች ሆነ

    ስፔን ቀብር ላይ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በኮሮናቫይረስ ክፉኛ ከተጠቁት መካከል አንዷ በሆነችው ስፔን በቀን ውስጥ የሚመዘገበው የሟቾች ቁጥር ከመቶ በታች መሆኑ ተገልጿል።

    ይህም ሁኔታ በሁለት ወራት ውስጥ የመጀመሪያው ነው ተብሏል።

    በዛሬው ዕለት የተመዘገበው የሟቾች ቁጥር 87 መሆኑን የገለፁት የጤና ሚኒስትሩ በአጠቃላይም የሟቾችን ቁጥር 27 ሺህ 650 አድርሶታል ብለዋል።

    በቫይረሱ የተያዙት ሰዎችም ቁጥር ከ230 ሺህ 698 ወደ 231 ሺህ 350 አድጓል።

  6. ኬንያ የታንዛንያ እና ሶማሊያ ድንበሮቿን ዘጋች

    ምርመራ እየጠበቁ ያሉ አሽከርካሪዎች

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የኬንያው ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ የታንዛንያና ሶማሊያ ድንበሮች እንዲዘጉ ውሳኔ አስተላልፈዋል። የሚፈቀደውም የካርጎ አገልግሎት ብቻ ነው።

    ውሳኔው የተላለፈው በትናንትናው ዕለት ሲሆን ኬንያን በሚያዋስኗት የትኛውም ድንበሮችም ላይ አሽከርካሪዎች መመርመር ግዴታ ነው።

    ባለፈው ሳምንት 78 የጭነት መኪና አሽከርካሪዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸውን ተከትሎ ወደ ሃገሪቷ እንዳይገቡ ተከልክለዋል።

    በቅርብ ሳምንታት በኡጋንዳና በኬንያ ድንበር መካከል በርካታ የጭነት መኪና አሽከርካሪዎች ለመመርመር ረዥም ሰልፍ ይዘው ታይተዋል።

    ከዚህ ቀደምም ከኤች አይ ቪ ኤድስ ጋር በተያያዘ ድንበርን የሚያቋርጡ የጭነት መኪና አሽከርካሪዎች ተጋላጭ ማህበረሰብ ተብለው የተለዩ ሲሆን፤ የዛን ጊዜ የተገኘውን ልምድ በመጠቀም በቀጠናው የሚገኙ ሃገራት ከኮሮናቫይረስም ጋር በተያያዘ ይህንኑ አካሄድ እየተጠቀሙ ይገኛሉ።

    830 ሰዎች በቫይረሱ የተያዙባት እንዲሁም 50 ዜጎቿን ያጣችው ኬንያ የሰአት እላፊንም ሆነ ከመዲናዋ ናይሮቢ ወደ ሌሎች ከተሞች የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን የሚያግደውን ሕግ ለሃያ አንድ ቀናት አራዝማለች።

  7. "ጭምብል አድርጉ፤ ካለበለዚያ እስር ይጠብቃችኋል"- ኳታር

    በኳታር ጭምብል ያጠለቀ ግለሰብ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የኮሮናቫይረስን መዛመት ለመግታት ጭምበል ማድረግ አስገዳጅ ያደረገችው ኳታር ይህንን ጥሰው የሚገኙ ግን የሶስት ዓመት እስር ወይም የ55 ሺህ ዶላር ቅጣት ይጠብቃቸዋል በማለት አሰጠንቅቃለች።

    በተለይም ይህ ተፈፃሚ የሚሆነው በተደጋጋሚ ጭምብል ባለመልበስ መመሪያውን የጣሱትን ነው ተብሏል።

    ከህዝብ ቁጥሯ ጋር ሲነፃፀር በከፍተኛ ሁኔታ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ያሉባት ኳታር ከሶስት ሚሊዮን በታች ከሆነው ህዝቧም ውስጥ 30 ሺዎቹ በቫይረሱ ተይዘዋል ተብሏል።

    በዓለም ሃብታም ከሚባሉ ሃገራት በምትመደበው ኳታር መስጊዶች፣ ትምህርት ቤቶች እንዲሁም የመገበያያ መደብሮች ዝግ ሆነው ይቆያሉ።

    አንዳንድ ህንፃዎች አካላዊ ርቀትን በጠበቀ መልኩ እንዲከፈቱ የፈቀደች ሲሆን፤ ይህም በጎርጎሳውያኑ 2022 ሊካሄድ ለታቀደው የዓለም ዋንጫ ዝግጅት እንዲያደርጉ የተለዩ ናቸው ተብሏል።

  8. የአትሌቲክስ ውድድሮች በባዶ ሜዳዎች ሊመለሱ ይችላል እየተባለ ነው

    የአለም አቀፉ አትሌቲክስ ፕሬዚዳንት ሎርድ ኮዬ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የዓለም አቀፉ አትሌቲክስ ፕሬዚዳንት ሎርድ ኮዬ የአትሌቲክስ ስፖርት ሲመለስ በባዶ ሜዳዎች ሊካሄድ እንደሚችል አስጠንቅቀዋል።

    ዓመታዊው የዳይመንድ ሊግ እንዲሁም የተለያዩ የአትሌቲክስ ውድድሮች ሁኔታዎች ከተገመገሙ በኋላ በመጪው ነሐሴ አጋማሽ እንዲካሄዱ እቅድ ተይዟል።

    ፕሬዚዳንቱ በነሃሴ እንዲካሄዱ እቅድ የተያዘላቸው አስራ አንዱ የተለያዩ የአትሌቲክስ ውድድሮች በዝግ ሜዳ እንደሚሆኑ ጠቁመዋል።

    "በመጪዎቹ ቅርብ ጊዜያት የሚካሄዱ ውድድሮች ላይ ለደህንነት ስንል ልንደራደርባቸው የማይገቡ ጉዳዮች አሉ። በተደጋጋሚ በጤና ባለሙያዎችም ሆነ በአካባቢው ማህበረሰብ የተነገረንን ሁኔታዎች ከግምት ውስጥ ያስገባና ችላ የማንላቸውም ናቸው" በማለት ጌምስ ለተባለው ድረገፅ ተናግረዋል።

    "ሁላችንም ቢሆን ይህ የረዥም ጊዜ መፍትሄ ነው ብለን አናስብም። ስፖርታዊ ውድድሮች ያለታዳሚ ይጠፋሉ" ብለዋል ፕሬዚዳንቱ።

    አክለውም "ሆኖም በአሁኑ ወቅት የአትሌቲክስ ውድድሮችን ለመመለስ መክፈል ያለብን መስዋዕትነት ይሄ ነው" ብለዋል።

  9. ታይዋን የአለም አቀፉ ጤና ድርጅት ወሳኝ ጉባኤ ላይ እንዳትሳተፍ ለምን ተደረገች?

  10. ባራክ ኦባማ የትራምፕ አስተዳደር ቫይረሱን ለመቆጣጠር የወሰደውን እርምጃ ተቹ

    ዶናልድ ትራምፕና ባራክ ኦባማ

    የፎቶው ባለመብት, GETTY IMAGES

    የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ዶናልድ ትራምፕ የኮሮናቫይረስ ወወርሽኝን ለመቆጣጠር የወሰዱትን እርምጃ ወቅሰዋል።

    ለተመራቂ ተማሪዎች በበይነ መረብ ባስተላለፉት መልእክት ላይ "ይህ ወረርሽኝ ኃላፊዎች በመሪነት ቦታ ላይ ለመቆም ፍላጎት እንኳን እንደሌላቸው አሳይቶናል" ብለዋል።

    በቅርብ ቀናት ውስጥ ኦባማ ከኮሮናቫየረስ ጋር በተያያዘ የትራምፕ አስተዳደርን ሲወርፉ ይህ ሁለተኛቸው ነው።

    ታዋቂው የቅርጫት ኳስ ተጫዋች ሌብሮን ጄምስ ለተመራቂዎቹ ባዘጋጀው ፕሮግራም ላይ ከባራክ ኦባማ በተጨማሪ ከሙዚቀኞቹ ጆናስ ብራዘርስ እና ፋረል ዊሊያምስ እንዲሁም የትምሀርት ጉዳዮች አቀንቃኟ ማላላ ዩሳፍዛይ ተገኝዋል።

    ‘’የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የአገሪቱ መሪዎች ምን ያክል አቅም እንደሌላቸው አሳይቶናል’’ ብለዋል የቀድሞው ፕሬዝዳንት።

    በአሜሪካ ባለፉት 24 ሰአታት ብቻ 1200 ሰዎች በቫይረሱ ሕይወታቸው ያለፈ ሲሆን አጠቃላይ የሟቾች ቁጥር ደግሞ 89 ሺ ደርሷል።

  11. ናይጄሪያ የማዳጋስካሩን የኮቪድ-19 ‘’መድሀኒት’’ ተቀበለች

    የማዳጋስካር ፕሬዚዳንት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የናይጄሪያው ፕሬዝዳንት ሞሃመዱ ቡሀሪ በማዳጋስካር እጽዋትን በመቀመም የተሰራውን የኮቪድ-19 ‘’መድሀኒት ለሙከራ ተቀብለዋል።

    በፈሳሽ መልክ የቀረበው ይህ ‘’መድሀኒት’’ አሪቲ (አርትሚዝያ) ተክል እንዲሁም ሌሎች ዕፅዋትን በመጠቀም የተሰራ ሲሆን፤ አሪቲ በዋነኛነት የወባ በሽታትን ለማከም ጥቅም ላይ የሚውል ነው።

    የጊኒ ቢሳው ፕሬዝዳንት ኡማሮ ሲሶኮ ኢምባሎ ከናይጄሪያው መሪ ጋር ውይይት ሲያደርጉ ይህንኑ የማዳጋስካር ምርት በስብሰባው ላይ ይዘው ተገኝተው ነበር።

    ነገር ግን በአፍሪካ ትልቅ የሕዝብ ቁጥር ያላት አገር መሪው በሳይንሳዊ መንገድ ለሚገኙ መድሃኒቶች ትንሽ እድል እንስጥ የሚል አቋም ቢያንጸባርቁም ከጊኒው ፕሬዝደንት የቀረበላቸውን ‘’መድሃኒት'' ግን ተቀብለዋል።

    የዓለም ጤና ድርጅት መድሃኒቱ አሁንም ቢሆን ፈውስ ሊሆን እንደሚችል ምንም ማረጋጋጫ የለም እያለ ነው።

  12. የስደተኞችን ፈተና ኮሮናቫይረስ አባብሶታል

    ስደተኞች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በሺዎች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን ስደተኞች መሄድ የፈለጉት አገር ሳይደርሱ በኮሮናቫይረስ ምክንያት መንገድ ላይ ይገኛሉ።

    የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ጉዳይ ክንፍ ‘አይኦኤም’ እንዳስታወቀው ወደ አውሮፓ አገራት የሚገቡ ስደተኞች ቁጥር በእጅጉ ቀንሷል። .

    በሚያዝያ ወር1725 ስደተኞች ብቻ የመን የገቡ ሲሆን ባለፉት ተከታታይ ወራት ግን ለምሳሌ በመጋቢት 7223፣ የካቲት 9624 እና ጥር ላይ ደግሞ ከ 11 ሺ በላይ ስደተኞች ነበሩ ወደ አገሪቱ የገቡት።

    ባለፈው ዓመት ደግሞ በአጠቃላይ 138 ሺ ሰዎች ትንንሽ ጀልባዎችን በመጠቀም በየመን በኩል አድርገው ሳዑዲ አረቢያ ገብተዋል። ከነዚህም መካከል አብዛኛዎቹ ኢትዮጵያውያን ናቸው።

    ስራ ፍለጋ በሚለው ወደ መካከለኛው ምስራቅ ለመሄድ ጉዞ የጀመሩ በርካታ ስደተኞች መንቀሳቀስ ባለመቻላቸው በአሁኑ ሰአት በሶማሊያዋ ቦሳሶ ወደብ ከተማ ይገኛሉ።

    አይኦኤም እንደሚለው ሁሉም ስደተኞች ከዚህ በፊት ሲጓዙ ስለነበረ በቫይረሱ ተይዘው ሊሆን ይችላል የሚለው ጥርጣሬ ሰዎች እንዳይረዷቸው እንኳን እያደረገ ነው።

    የአውሮፓ አገራት የእንቅስቃሴ ገደባቸውን ማንሳት ሲጀምሩ ደግሞ የስደተኞች ቁጥር በእጅጉ ከፍ እንደሚል ይጠበቃል። በቫይረሱ ምክንያት ኢኮኖሚያቸው የደቀቁ በተለይ የአፍሪካ አገራት ዜጎች ስራ ፍለጋ ሕገወጥ መንገዶችን በመጠቀም እንደሚንቀሳቀሱ ይገመታል።

  13. "ለሃያ ዓመታት ለኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ስዘጋጅ ነበር" የንፅህና ሱሰኛው

  14. በኮሮናቫይረስና በነዳጅ ዋጋ መውደቅ ስጋት የተደቀነባት ሳዑዲ አረቢያ

  15. ከኮሮናቫይረስ ለመዳን ምን ያክል ጊዜ ይወስዳል?

  16. እንደምን አደራችሁ

    በቤት ስራ ላይ የተሰማራች ወጣት

    የፎቶው ባለመብት, This is Lebanon/FB page

    ከጥቂት ወራት በፊት የተከሰተው የኮሮናቫይረስ ስጋት ሃገራት የተለያዩ እርምጃዎችን እንዲወስዱ አድርጓቸዋል።

    ከነዚህም መካከል አስገዳጅ የቤት ውስጥ መቀመጥን ጨምሮ፣ እንቅስቃሴን መገደብ፣ ድንበሮቻቸውን መዝጋትና ሌሎችም በዚህም የተነሳ የሰው ልጅ ለመቶና ከዚያ አመታት በላይ ያሳደጋቸውን፣ የተቀበላቸውን ትውፊቶች፣ የአኗኗር ዘዬ፣ ባህል ላይ ስር ነቀል ለውጥ በማምጣቱ በአለም ላይ ላሉ ህዝቦች ግራ አጋቢ ሆኗል።

    በተለይም ብዙዎቸ የነገውን ሲያስቡ እርግጠኛ የአለመሆን ስሜት ብዙ አስደሳች አልሆነም። በተለይም የኮሮናቫይረስ መከሰትን ተከትሎ በርካቶች ስራቸውን አጥተዋል፤ የበርካታ ሃገራት ምጣኔ ኃብትም ወድቋል።

    በዚህም መካከል ለንግድ፣ ለአጭር እንዲሁም ለረዥም ጊዜ ከሃገራቸው ውጭ ኑሯቸውን ያደረጉ ሰዎች ወደ ሃገራችን መልሱን ጥሪ እየተሰማ ነው።

    በዚህም ናይጄሪያ፣ ደቡብ አፍሪካና ኬንያ የመሳሰሉ ሃገራት ዜጎቻቸውን አስወጥተዋል። በሊባኖስ የሚኖሩ በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንም ኑሯችን የከፋ ሁኔታ ላይ ስለሆነ ወደ ሃገራችን መልሱን እያሉ ነው።

    በቤት ሰራተኝነት የሚሰሩት ያለ ደመወዝ፣ ደመወዛቸውን በግማሽ ቀንሰው የሚሰሩ እንዲሁም በሃገሪቱ ውስጥ ስራ የሌላቸው ኢትዮጵያውን በሺዎች ይቆጠራሉ። ብዙዎቹም ስራ የሌላቸው ስደተኞች ህገወጥ ናችሁ ተብለው በእስር ቤት የሚማቅቁ፣ በሆስፒታል እንዲሁም አስከሬናቸው ማቆያ ውስጥ ያሉ መኖራቸውንም ቢቢሲ ከሊባኖስ ያነጋገራቸው ስደተኞች ገልፀዋል። የዛሬውም የቀጥታ ዘገባችንም ጀምረናል፤ ተከታተሉን

    መልካም ቀን እንዲሆንላችሁ ተመኘን

  17. ጀርመን የሊግ የእግር ኳስ ውድድሮችን መልሶ በማስጀመር የመጀመሪያዋ ሆነች

    የመጀመሪያው ጨዋታ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    መጋቢት 02/2012 ዓ.ም፡ በኮሮናቫይረስ ምክንያት ሁሉም ጨዋታዎች እንዳይካሄዱ ከመደረጉ በፊት የቡንደስ ሊጋው የመጨረሻ ጨዋታ በቦሪሲያ ሞንቼግላድባህ እና በኮለን መካከል በዝግ ስታዲየም ነበር የተደረገው።

    ግንቦት 08/2012 ዓ.ም፡ የቡንደስ ሊጋ ውድድር ተጀምሯል። በወረርሽኙ ምክንያት የእግር ኳስ ውድድሮች በመላው ዓለም እንዲቋረጡ ከተደረጉ በኋላ፤ ጀርመን የሊግ ጨዋታዎችን መልሳ በመጀመር በአውሮፓ የመጀመሪያዋ አገር ሆናለች።

    ቦሩሲያ ዶርትመንድ ከሻልከ የሚያደርጉት የደርቢ ጨዋታ የውድድሩን መጀመር ያበስራል ተብሏል።

    ዛሬ በተጀመረው ጨዋታ ጥብቅ የጤና ጥበቃ ቁጥጥር ተደርጓል ተብሏል። ተመልካቾች ስታዲየም የማይገቡ ሲሆን፤ ተጫዋቾችም ጭምብል እንዲያደርጉ ታዘዋል።

    ደጋፊዎች ወደ ስታዲየም እንዳይገቡ ለመከላከልና ለሳምንታት የተጣለውን የእንቅስቃሴ ገደብ በመቃወም ሰልፍ ይደረጋል የሚል ስጋት ስላለ ፖሊስ እንዲሰማራ ተደርጓል።

    በርሊን ከተማ ውስጥ የግራ ዘመሙ ፓርቲ ደጋፊዎች በታዋቂው የብራንደንበርግ መግቢያ ላይ ተሰብስበው መንግሥት የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን በተመለከተ የወሰዳቸውን እርምጃዎች ለመቃወም እየተሰባሰቡ እንደሆነ ተነግሯል።

    ተጫዋቾች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

  18. በኢትዮጵያ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ300 በላይ ሆነ

    Ethiopia

    በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓታት 4044 ሰዎች የኮሮናቫይረስ ምርመራ ተደርጎላቸው 19 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋገጠ።

    የጤና ሚኒስቴርና የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ተቋም በጋራ ባወጡት መግለጫ ነው ይህን ያሳወቁት።

    ከ19 ሰዎች መካከል 15ቱ ወንዶች ሲሆኑ 4 ደግሞ ሴቶች ናቸው ተብሏል። ሁሉም ኢትዮጵያውያን እንደሆኑና ዕድሜያቸው ደግሞ ከ16-55 እንደሆነ መግለጫውን ያሳያል።

    2 ሰዎች ከአዲስ አበባ፣ 2 ከኦሮሚያ፣ 3 ሰዎች ከትግራይ፣ 1 ሰው ከአማራ እንደሁም የተቀሩት 11 ሰዎች ከሶማሊ ክልል መሆናቸው ታውቋል።

    15 ግሰለቦች የጉዞ ታሪክ ያላቸው ናቸው፤ ሁለቱ ደግሞ ኮሮናቫይረስ ከያዘው ሰው ጋር ንክኪ እንዳላቸው ታውቋል። የተቀሩት ሁለቱ ሰዎች የጉዞ ታሪክም ሆነ ንክኪ የሌላቸው ናቸው።

    ኢትዮጵያ እስከዛሬ ካደረገቻቸው ምርመራዎች ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሰው የመረመረችው ባለፉት 24 ሰዓታት ነው።

  19. የኮሮናቫይረስ ክትባት በነጻ እንዲቀርብ ግፊት እየተደረገ ነው

  20. የጀርመን ቡንደስሊጋ ዛሬ ይጀምራል

    ቡንደስሊጋ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት የተቋረጠው የጀርመን ቡንደስሊጋ ያለተመልካች ዛሬ ይጀምራል።

    ቡንደስሊጋው አውሮፓ ውስጥ ካሉ ታላላቅ የእግር ኳስ ሊጎች ቀድሞ ውድድሩን የቀጠለ ሆኗል።

    ዛፌ ስድስት ፍልሚያዎች ይደረጋሉ። ከእነዚህ መካከል ቦሩሲያ ዶርትመንድ ከሻልከ የሚያደርጉት የደርቢ ጨዋታ ተጠባቂ ነው።

    ነገ [እሁድ] ከሚደረጉ ጨዋታዎች ደግሞ መሪው ባየርን ሚዩኒክ ከዩኒየን በርሊን ጋር ከሜዳው ውጭ የሚያደርገው ፍልሚያ ተጠባቂ ነው።

    አብዛኛዎቹ የቡንደስሊጋ ቡድኖች ሊጉን ለማጠናቀቅ ዘጠኝ ጨዋታ ይቀራቸዋል።

    ደጋፊዎች ወደ ሜዳ ለመግባት እንዳይሞክሩ ሁሉም ጨዋታዎች በፖሊስ እንደሚጠበቁ ተነግሯል።

    ምንም እንኳ ደጋፊዎች ወደ ኳስ ሜዳ ዝር እንዳይሉ ቢታገዱም ቦሩሲያ ሞንቼንግላድባክ የደጋፊዎቹን ፎቶዎች በትልቁ አትሞ መቀመጫዎች ላይ እንደሚሰቅል አስታውቋል።

    ተጨዋቾች፣ ሙያተኞችና ዳኞችን ጨምሮ በስታድየም ውስጥ 300 ያክል ሰዎች ይኖራሉ። ተጫዋቾች ሁሉም የኮቪድ-19 ምርመራ ተደርጎላቸዋል። አልፎም ከሜዳ ውጭ ማሕበራዊ ርቀታቸውን እንዲጠብቁ ታዘዋል።

    የቡንደስሊጋ ክለቦች ተጫዎቻቸው በጋራ ልምምድ እንዲያደርጉ ያዘዙት ባለፈው ወር አጋማሽ ነበር።

    ሁሉም ተጫዎቾችና ባለሙያዎች ከሚያርፉበትና ሆቴልና የልምምድ ሥፍራ ውጭ ወዴትም መሄድ አይፈቀድላቸውም።